Friday, October 31, 2014

ማዕከላዊ የሚታሰሩት የጋምቤላ ክልል ነዋሪዎች ቁጥር አሻቅቧል * በርካታ የጋምቤላ ክልል ነዋሪዎች ዛሬ ፍርድ ቤት ቀርበዋል

October 31,2014
የህወሓት/ኢህአዴግ ባለስልጣናት በኢንቨስትመንት ስም የጋምቤላን ክልል ነዋሪዎች እያፈናቀሉ በያዙት መሬት ምክንያት እንደተቀሰቀሰ የሚነገርለትና ለወራት በዘለቀው ግጭት ተሳታፊ ናቸው የተባሉ በርካታ የጋምቤላ ክልል ነዋሪዎች ዛሬ ጥቅምት 20/2007 ዓ.ም በአራዳ ምድብ ችሎት መቅረባቸው ታወቀ፡፡
ነዋሪዎቹ ከጋምቤላ ክልል ወደ ማዕከላዊ ከመጡ በኋላ ዛሬ ከቀኑ 8 ሰዓት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበዋል፡፡ ዜጎች ወደ ችሎቱ በሁለት የፖሊስ አውቶቡሶች የመጡ ሲሆን በቁጥር ቢያንስ 50 እንደሚደርሱ ምንጮች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ችሎቱ በዝግ እንደተካሄደም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከጋምቤላ ክልል የመጡት ዜጎች በአራዳ ምድብ ችሎት በቀረቡበት ተመሳሳይ ሰዓት የሸዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺና አብርሃ ደስታ የሚቀርቡ በመሆኑ በዚህ ችሎት ለመታደም የሄደው ህዝብ ከጋምቤላ የመጡት ዜጎች ላይ በተደረገው ጥብቅ ጥበቃ ምክንያት ከፍተኛ ፍተሻ እንደተደረገበት በቦታው የተገኘው የነገረ ኢትዮጵያ ዘጋቢ አረጋግጧል፡፡ በቦታውም ለጥበቃ የፌደራል ፖሊስ፣ የአዲስ አበባ ፖሊስና የማረሚያ ቤት ፖሊስ እንደተገኙም ታውቋል፡፡ ዛሬ አራዳ ምድብ ችሎት የቀረቡት የጋምቤላ ክልል ነዋሪች መቼ ወደማዕከላዊ እንደመጡ የታወቀ ነገር የለም፡፡
በሌላ በኩል ትናንት ጥቅምት 19/ 2007 ዓ.ም ወደ ማታ አካባቢ ጋምቤላ ክልል ውስጥ በተፈጠረውና ለወራትም የበርካታ ሰው ህይወት ከጠፋበት ግጭት ጋር በተያያዘ በርካታ ዜጎች በአውቶቡስ ተጭነው ወደ ማዕከላዊ መግባታቸውን የአይን እማኞች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ወደ ማዕከላዊ ከመጡት መካከል የአካባቢው ባለስልጣናትም እንደሚገኙበት የነገረ ኢትዮጵያ ምንጮች አክለው ገልጸዋል፡፡
በዛሬው ዕለት ችሎት የቀረቡትንና በትናንትናው ዕለት ወደ ማዕከላዊ የመጡን ጨምሮ ጋምቤላ ክልል ውስጥ በተፈጠረው ግጭት ምክንያት ማዕከላዊ የሚታሰሩት ዜጎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሸቀበ መሆኑም ተገልጾአል፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ ለአንባቢዎቿ ተጨማሪ መረጃዎችን ለማቅረብ ጥረት ታደርጋለች፡፡

No comments: