Tuesday, October 14, 2014

ተመስገን ደሳለኝንም አሰሩት

October 14,2014
(ኢ.ኤም.ኤፍ) ታዋቂው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ታሰረ። ተመስገን ደሳለኝ ከትላንት ጀምሮ፤ የጥፋተኝነት ውሳኔ ተሰጥቶበት የታሰረ መሆኑን ለማወቅ ችለናል። ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከዚህ በፊት በተከሰሰበት እና ፍርድ ቤት ሲመላለስባቸው በነበሩት ክሶች ነው አሁን ለእስር የበቃው።
Temesegen Desalegn
Temesegen Desalegn
ጋዜጠኛ ተመስገንን ለክስ ካበቁት ጽሁፎች መካከል፤ “መጅሊሱ፣ ሲኖዶሱና የአብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ማጥመቂያዎች”፣ “የፈራ ይመለስ” እና “የብሄረሰቦች መብት እስከ መጨፈር” በሚል ርእስ የጻፋቸው ጽሁፎች ናቸው። ሁሉም ጽሁፎች አሁን እንዳይታተም በታገደው ፍትህ ጋዜጣ ላይ የወጡ ነበሩ።  በነዚህ ጽሁፎች ምክንያት አቃቤ ህጉ የክሱን ጭብጥ የመሰረተው፤ መንግስትን በአመፅ ለመናድ ቀስቅሷል፣ የመንግስትን ስም አጥፍቷል፣ የህዝብን አስተሳሰብ አናውጧል፤ በሚል ሲሆን ጽሁፎቹም ሆኑ ክሱ ሁለት አመታትን አስቆጥሯል።
በእነዚህ ክሶች ምክንያት ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ፍርድ ቤት በቀጠሮ ሲመላለስ ቆይቶ፤ ትላንትና ግን ፍርድ ቤቱ በተመስገን ላይ የጥፋተኝነት ውሳኔ አሳልፏል። በመሆኑም ጋዜጠኛ ተመስገን በ እስር ላይ ቆይቶ የቅጣት ውሳኔውን ከ2 ሳምንታት በኋላ ማለትም ጥቅምት 17፣ 2007 በፍርድ ቤት ተገኝቶ እንዲያዳምጥ ውሳኔ ተሰጥቷል። በመሆኑም ጥቅምት 17 ቀን ከታሰረበት መጥቶ፤ ለምን ያህል ተጨማሪ አመታት እንደሚታሰር በንባብ ተነግሮት ወደ ወህኒ እንዲወርድ ይደረጋል ማለት ነው።
በማጠቃላያችን ላይ አንድ ነገር ማከል ፈለግን። ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ከታሰረ በኋላ በቅርብ ምስክርነታቸውን ከሰጡት ውስጥ በፋክት መጽሄት ላይ አብሮት የሰራው ቴዎድሮስ ተክለአረጋይ አንዱ ነው። የቴዎድሮስን ጽሁፍ ከዚህ ቀጥሎ በማቅረብ ዘገባችንን እናበቃለን።
ስለ ተመስገን ደሳለኝ (ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ)
(ቀደም ብዬ መፃፍ የነበረብኝ ሀሳብ)
ዛሬ ከደቂቃዎች በፊት የተመስገንን መታሰር ስሰማ አዘንኩ ። “በምንና እንዴት ታሰረ? መታሰሩ አግባብ ነው? ” የሚለውን አላነሳም ። ምክንያቱም ከግምት የተሻለ እውቀት የለኝም ። አሁንም በቀጠሮው ቀን ምን እንደሚል አላውቅም ። ይህ ሀሳቤም አሁን ተመስገን ካለበት ሁኔታ ጋር አይገናኝም ። ይሁንና ቀደም ሲል መፃፍ የነበረብኝን ሀሳብ ላንሳ ።
ተመስገን ፋክት መጽሔት ላይ እንድጽፍ ሲያነጋግረኝና ከዚያ በፊት ለእሱ የነበረኝ ግምት የተለያየ ነው ። አራት ኪሎ አግኝቼ ያናገርኩትና ፋክት እስክትቆም ያየሁት ተመስገን ለእኔ እንዲህ ነው ።
የሚጮህ ጽሁፍ የሚጽፈው ተመስገን በጣም ጸጥተኛ ነው ። ደፋሩን ጸሀፊ የትህትና ፍርሀት ያለበት ሆኖ ነው ያገኘሁት ። ለስላሳነቱ የውስጥ ባህሪው ነው ። ከሁሉም በላይ በግል እንደራሴም ይሁን እንደ ሙያውን ወዳድ ጋዜጠኛ ፍጹም ነጻነት የሰጠኝ ከሁሉም በላይ ተመስገን ደሳለኝ ነው ። አብረን ለመስራት ተስማምተን ስለጽሁፍ ይዘት ስናወራ “ምን አይነት ይዘት ያለው ጽሁፍ እንድጽፍ ነው የምትፈልገው?” ስለው የሰጠኝ መልስ መቼም የማልረሳውና በአንዱ የመጽሔቱ እትም ላይ የጻፍኩት ነው ። ” እንዲህ ጻፍ አልልህም ። የፈለከውን ጻፍ ። ኢህአዴግ በአለም ላይ ታይቶ የማይታው ዲሞክራሲ አምጥቷል ብለህ ካመንክ የመጻፍ መብት አለህ ። አንተ ስም ስላለህ ድጋፉንም ተቃውሞውንም የምትቀበለው ራስህ ነህ ” አለኝ ። ይህ ለአንድ ጋዜጠኛ ፍፁማዊ ነጻነት ነው ። ተመስገን ደሳለኝ ከጥሩ የብር ክፍያው ጎን ይህን ከፍሎኛል ። የትም ብሄድ ይህን ነጻነት አላገኘውም ። በፋክት መጽሔት ቆይታዬም ከቃለመጠይቅ ጀምሮ እስከ መጣጥፎች በዚህ ነጻነት ነው የሰራሁት ። አንድም ቀን በዚህ ርዕስ ላይ ብትፅፍ ያላለኝና በሀሳቤ ጣልቃ ያልገባ ሰው ይህ ሰው ነው ። መጻፍ ሲገባኝ ያልጻፍኩት ወይም ያልተገባ ሀሳብ ጽፌ ከተገኘሁ በራሴ ግፊትና ሀሳብ ነው ። ለጻፍኩት ሁሉ ሀላፊነቱን የምወስደው እኔ ብቻ ነኝ ። ማንም ሌላ የለም ። ይህን የጋዜጠኛ ነጻነት ሌላ ቦታ አገኘዋለሁ ብዬ አላምንም ። በዚህ ተመስገንን ሁሌም አከብረዋለሁ ። እውነት ለመናገር መቼም ወደ ፕሬስ ስራ ቢመለስ አብሬው ለመስራት የማላመነታው አንድ ሰው ይህ ዛሬ ታሰረ የተባለው ተመስገን ደሳለኝ ነው ። ለእኔ ለጋዜጠኛው ከመጽሔቱ ሰውየው ተመስገን ይበልጥብኛል ። እጄን ይዞ ሊያጽፈኝ የማይሞክር የነጻነት አለቃዬ ነው ። አክባሪዬም ነው ተመስገን ። ለእኔ ግን ከማክበሩም በላይ ነጻነቱ ይበልጥብኛል ። አሁንም ልድገመውና ተመስገን ነፃ ወጥቶ ወደ ፕሬስ ስራ ቢመለስ እስከ ነጻ ባለ ክፍያ አብሬው ለመስራት የምፈልገው ሰው ነው ። ነጻነት በራሱ ክፍያ ነው ። ተመስገን ደግሞ ይህን እንደሚከፍለኝ አምናለሁ ።
አምላክ በድጋሚ በስራ እንደሚያገናኘን ፀሎቴ ነው ።

No comments: