Tuesday, May 13, 2014

አቶ አሥራት አብርሃ ለምን አንድነት ፓርቲን ተቀላቀሉ? – በዘሪሁን ሙሉጌታ

May 13/2014

ቀደም ሲል በአረና ትግራይ ለዲሞክራሲና ለሉአላዊነት ፓርቲ (አረና) ውስጥ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩትና በኋላ ከፓርቲው ጋር በተፈጠረ “የስትራቴጂክ ልዩነት” ከአረና ፓርቲ ወጥተው በግል ሲንቀሳቀሱ የነበሩት አቶ አሥራት አብርሃም ከሰሞኑ ወደ አንድነት ፓርቲ ገብተዋል። አቶ አሥራት በቋንቋና ስነ-ፅሁፍ ከዲላ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው ሲሆን በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፍልስፍና ትምህርት የሁለተኛ ዲግሪአቸውን በማጠናቀቅ ላይ ናቸው። አቶ አስራት ወደ አንድነት ፓርቲ ስለተቀላቀሉበት ምክንያት ለሰንደቅ ጋዜጣ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
አቶ አሥራት ወደፓርቲው ስለገቡበት ምክንያት ተጠይቀው፤ ሲመልሱ ከአንድ ዓመት በፊት ከአረና ወጥተው ከቆዩ በኋላ ከፖለቲካ ስሜት ውጪ ሆነው አለመቆየታቸውን፣ በጋዜጣና በመፅሔት ከሚያቀርቡት መጣጥፍ ባሻገር ወደፓርቲዎች አካባቢ ጎራ በማለት የራሳቸውን ኃሳብ ሲያቀርቡ ከቆዩ በኋላ በግል ከመንቀሳቀስ በፓርቲ ታቅፈው መታገል ስለመረጡ፣ በአንድነት አካባቢ ያሉ ጓደኞቻቸው ባደረጉባቸው ገንቢ ግፊት አንድነት ፓርቲንም በቅርብ ስለሚያውቁት መሆኑን አስረድተዋል።
አቶ አሥራት ወደ አንድነት ፓርቲ የተቀላቀሉት በጓደኞቻቸው ግፊት ብቻ ሳይሆን ፕሮግራሙንም በማየት እንደሆነ ተናግረዋል። በተለይም አቶ ስዬ አብርሃ ጋር በትግራይ ክልል ተምቤን ወረዳ ሲወዳደሩ በትግርኛ ቋንቋ የተተረጎመውን የአንድነት ፓርቲ ፕሮግራም ቅጂ በማንበባቸውና በመድረክ ፓርቲ ውስጥ በነበራቸው ተሳትፎ ወቅት ከአንድነት ፕሮግራም ጋር በመተዋወቃቸው እንደሆነ ገልጸዋል። በተጨማሪም ቀደም ሲል ከነበሩበት የአረና ፓርቲ ፕሮግራም በብዙ መልኩ ተቀራራቢ ሆኖ ስላገኙትም እንደሆነ ይናገራሉ።
በአቶ አሥራት እምነት የአንድነት ፓርቲ ፕሮግራም በሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ሲያዩት ለእኛ ሀገር ሁሉንም አስተሳሰቦችና ድምፅ ሊያሰባስብ የሚችል ፕሮግራም ስለሆነ ወደ ፓርቲው መግባታቸውን የሚያስረዱት አቶ አሥራት የአንድነት ፕሮግራም የግለሰብንና የቡድንን (Group) መብት መኖርን የተቀበለ፣ ከአማርኛ በተጨማሪ ኦሮምኛም የሀገሪቱ ተጨማሪ የፌዴራል መንግስት የስራ ቋንቋ እንዲሆን በፕሮግራሙ ያስቀመጠና በብዙ መንገድ ተራማጅ ሊባል የሚችል ፕሮግራም በመሆኑ ነው ብለዋል። ፓርቲው ባዘጋጀው የአምስት ዓመት የስትራቴጂ እቅድ ዘጠና በመቶ ስለሚስማሙ ፓርቲው ታግሎ ስለሚያታገል እንደሆነም ያስረዳሉ።
“በእኔ እምነት መካከለኛ በሆነው የፖለቲካ አስተሳሰብ እስማማለሁ። ቀኝና ግራ ጠርዝ ያልያዘ ፖለቲካ በሀገራችን ስለሚያስኬድ በዚህ ምክንያት ነው የገባሁት” ሲሉ አቶ አሥራት ያስረዳሉ።
የአንድነት ፕሮግራምና የአረና ፕሮግራም ተቀራራቢ ከሆነ ለምን ከአረና ወጥተው ወደ አንድነት እንደገቡም አቶ አስራት ተጠይቀው ሲመልሱ፤ “ከአረና ወጥቼ ወደ አንድነት አልገባሁም። ከአረና ወጥቼ ወደ ልጄና ሚስቴ ነው የተመለስኩት። ከአረና እንደወጣሁ ወደ አንድነት እገባለሁ ብዬ አላሰብኩም። ከአረና የወጣሁትም በአንዳንድ የስትራቴጂ አካሄድ ላይ መግባባት ባለመኖሩ፣ አዳዲስ ባህሪያትን በፓርቲው በመመልከትና የዛ ችግር አካል ላለመሆን ነው የወጣሁት። ከወጣሁም በኋላ የግል ስራ ስሰራ ቆየው እንጂ አንድነት ከአረና ስለሚሻል አይደለም ወደ አንድነት የገባሁት” ሲሉ መልሰዋል። በተጨማሪም ሰው እንደመሆናቸው በሂደት አቋማቸውን በመቀየራቸው እንዲሁም በቀጣይ አረና እና አንድነት ይዋሃዳሉ ከሚል ተስፋ በመነሳት ጭምር እንደሆነ ገልጸዋል።
የእሳቸው ወደ አንድነት መግባት አረና እና አንድነትን በማዋሃድ ረገድ ስለሚፈጥረው የፖለቲካ አቅም የተጠየቁት አቶ አሥራት፤ ቀደም ሲል ከአረና ጋር ያላቸው ግንኙነት የተሻለ በመሆኑ የእሳቸውን አስተዋፅኦ እንደሚያደርጉ፣ እንዲሁም የአረና ፓርቲ አባላት የእሳቸውን ወደ አንድነት ፓርቲ መቀላቀል በቴሌፎን በመደወል እንዳበረታታቸው ጭምር ተናግረዋል። ሁለቱን ፓርቲዎች እንዲዋሃዱም የተሻለ ነገር ሊፈጠር እንደሚችል ተስፋ እንዳላቸው ነው የጠቀሱት። የእሳቸውም አገባብ “ከአንድ ጢስ ወደ አንድ ጢስ” የመቀያየር ካልሆነ በስተቀር አንድነትና አረና ያንያህል ልዩነትና እርቀት አለን ብለን አናስብም ብለዋል።
ይሁን እንጂ አረና በክልል የተደራጀ የብሔር ፓርቲ ከመሆኑ አንጻር ከአንድነት ጋር ስለሚያቀራርባቸው ጉዳይ የተጠየቁት አቶ አሥራት ሁለት ነገር ጠቅሰዋል። የመጀመሪያው አረና የክልል ፓርቲ የሚያስብለውና የብሔር ፓርቲ የሚያስብለውን ልዩነት አስቀምጠዋል። አረና የአንድ ብሔር ሳይሆን የአንድ ክልል ፓርቲ ነው። አብዛኛዎቹ የፖለቲካ አቋሞቹ ላይ በተለይም የመድረክ ሁለተኛው ጉባኤው ላይ የመድረክን ፕሮግራም ሲቀበል በመድረክ ደረጃ የተቀበልነውን በተወሰነ ደረጃ በአረና በሚስማማ መልኩ ነው የወሰደው። እና ብዙ ከአንድነት የሚራራቅ ነገር የለውም” ሲሉ የገለፁት።
የእሳቸው ወደ አንድነት መግባት በመጠኑ የአለመተማመን ስሜት የሚንፀባረቅበትን የሰሜን ፖለቲካና የመሀል ሀገር ፖለቲካ በማቀራረብ ረገድ ስለሚያኖራቸው ሚና ተጠይቀውም ሁኔታው የበለጠ ወደፊት የሚታይ ቢሆንም አንድነት ከዚህ ቀደም ከሚታወቁ የመሃል ሀገር የፖለቲካ ፓርቲዎች በተወሰነ መጠን ለየት የሚልበት የራሱ አሳታፊ (accommodate) ባህሪ አለው። ፓርቲው የተለያየ ብሔርና አስተሳሰብ በአንድ ዓላማ ዙሪያ ለማሰባሰብ የሚጥር ፓርቲ ሆኖ የአስተሳሰብና የሰዎች ብዙህነት የሚንፀባረቅበት ፓርቲ ነው። አንድነት ፓርቲ ስትገባ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ የምታገኝበት የተለያዩ ቋንቋዎች የሚነገርበት ሰፋ ያለ የብሔር ስብጥርና አይነት ያለው ፓርቲ ስለሆነ ከሌሎች የመሃል ሀገር ፖለቲካ ፓርቲዎች ይለያል ብለዋል። ችግሩ ያለው ከአንድነት ፓርቲ አደረጃጀት አንጻር ሳይሆን ከገዢው ፓርቲ መሆኑን የሚጠቅሱት ገዢው ፓርቲ በህብረብሔር የተደራጁ ፓርቲዎችን አንድ አይነት ቀለም እንዲኖራቸው ከመፈለጉም በላይ ወደ አንድ ጥግ ሊያሲዛቸው እንደሚፈልግ ጠቅሰዋል። በዚያው መጠን አንድነት ፓርቲንም የአንድ ብሔር ፓርቲ አድርጎ የመፈረጅ ዝንባሌና ፍላጎት እንዳለ ጠቅሰዋል። በአንፃሩ አንድነት የሚለይበት የራሱ የሆነ ብዙ ቀለማት ያሉት ፓርቲ ነው ብለዋል።
ቀደም ሲል በአንድነት ፓርቲ ውስጥ “የአማራ ብሔር የበላይነት አለው” የሚለው የአንዳንድ ልሂቃንን አስተያየት በተጨማሪ የቀድሞ የአንድነት ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ መድረክን በተመለከተ በአንድነት ፓርቲ ውስጥ የነበራቸው አቋም በሌሎች የፓርቲው አመራሮች የሃሳብ የበላይነት ከመሸነፋቸው አንጻር እሳቸው (አቶ አሥራት) ወደአንድነት የመግባታቸው እንደምታም ምን እንደሆነ ተጠይቀው፤ አንድነት ፓርቲ የአማራ ብሔር የበላይነት አለው ብለው የሚያስቡ ልሂቃን በቁጥር ምንያህል ብዙ ስለመሆናቸው ጥርጣሬ እንዳላቸው ገልፀዋል። ይልቁኑ ይህ አመለካከት ከኢህአዴግ አካባቢ የሚደመጥ መሆኑን ጠቅሰው ዋናው ነገር ግን የፓርቲው ፕሮግራም ነው ብለዋል።
ከዚህ በተጨማሪ ወደ ፖለቲካ ትግል የሚገባ ሰው የእገሌ ብሔር ስለበዛና ስላነሰ እያለ ወደ ትግል መግባት የለበትም። ዋናው ነገር በፕሮግራሙና በሕገ ደንቡ ይመራል የሚለው ነው። በተጨባጭ አሁን ባለው ሁኔታ የአንድነት የስራ አስፈፃሚ አባላት ስብጥር ከአብዛኛዎቹ የኢትዮጵያ ክፍሎች የተውጣጡ ናቸው። በፓርቲው የአማራ የበላይነት አለ ቢባል እንኳ ጫፍ ይዞ ውጪ መቅረት ሳይሆን ገብቶ ተመጣጣኝ ውክልና እንዲኖርና የሁሉንም ኢትዮጵያዊ የሚወክል አመራርና አባል እንዲኖር መታገል ነው ብለዋል።
አቶ አሥራት ከአረና ፓርቲ ከወጡ በኋላ በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው ወቅት የኀሳብ አመንጪ ምሁራን (Think thank) ለማቋቋም ጥረት ሲያደርጉ እንደነበር ይታወቃል። ጥረቱ ስላልተሳካ ወደ ፓርቲ ፖለቲካ ተመልሰው እንደሆነም ተጠይቀው ነበር። እሳቸውም የተባለው ሃሳብ አመንጪ አካል በተፈለገው መጠን ባይሄድም በቅርቡ ግን ፍልስፍና የሚያጠኑ ምሁራን ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ጭምር ያሉበት “Think Ethiopia” የሚል ቡድን መቋቋሙን ገልጸዋል። ቡድኑ በአመዛኙ ፍልስፍና ላይ እንዲያተኩር መደረጉንም አስረድተዋል። ወደ አንድነትም የገቡት ታስቦ የነበረው ሰፋያለ ፖለቲካ ሃሳብ አመንጪ ቡድን ባለመሳካቱም እንደሆነም ጠቅሰዋል።
በምርጫ ዋዜማ ወደ ፖለቲካ ፓርቲ መግባታቸው ከስልጣን ፍለጋ ጋር ስለመያያዙም አቶ አሥራት ተጠይቀው ማንኛውም ፖለቲከኛ ትክክለኛ ስልጣን እንደማይጠላ ጠቅሰው፣ ነገርግን ስልጣን ያለው ኢህአዴግ ጋር መሆኑን አስረድተዋል። በእሳቸው እምነት በአረና ፓርቲ ውስጥ እያሉ ትልቅ ስልጣን እንደነበራቸው አስታውሰው ነገር ግን ፓርቲዎቹ ውስጥ ከስልጣን ይልቅ ትግል ወይም የስራ ክፍፍል ብቻ ነው ያለው ሲሉ መልሰዋል። በፓርቲው ውስጥ ለታችኛውም ሆነ ለላይኛው የአመራር አካል ኀሳብ በመስጠት በማንኛውም የፓርቲው ደረጃ ላይ በመሆን ለመስራት መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
1619254_634234963328108_581967544042254518_n

No comments: