Monday, December 30, 2013

የነጻነት ታጋይነት ምስክሩ እና የነጻነት ነጣቂ ምሳሌነቱ

December 29/2013

ሰላም ጤና ይስጥልኝ ያልገባችሁና ያልተረዳችሁ ወገኖቼ ሰሞኑን ከዚህ ዓለም በስጋ ለተለዩት፤ በተግባራቸው ከበሬታን፤ በእሳቤያቸው አንቱታን፤ ያተረፉት የደቡብ አፍሪካው የነጻነት አባትና፤ የዴሞክራሲና ፍትህ፤ የሰብአዊ መብትና የእድገት አርማ የሆኑትን ማዲባ ኔልሰን ማንዴላን አስመልክቶ በዓለማት ላይ ባሉ የመገናኛ ብዙሃን በብዛት ከበሬታቸውንና አድናቆታቸውን ችረዋቸዋል፡፡
ማዲባ ስልጣንን የለቀቁት ግን በምርጫ ተሸንፈው ሳይሆን በፈቃዳቸው ለሌሎች አርአያ ለመሆን ስልጣንን በፈቃድ ማሳለፍን ለማስተማር ሲሉ ነው፡፡ ማዲባ በምርጫ ባሸነፉበትም ወቅት ምርጫውን ለማሸነፍ ሲሉ ማጭበርበር አልፈጸሙም፤ ካርድ አልነጠቁም፤ በስልጣን በመመካት የድምጽ ቆጠራውን አልመዘበሩም፤ እድሜያቸው ያልደረሱትንና በሕገመንግስት ላይ ሊመርጡ አይገባም የተባሉ ወታደራዊ አባላትን አሰልፈው ድምጽ አልመዘበሩም ወዘተርፈ…..
በዚህ የሃዘን ስርአት ላይ ሃገራቸውንና ሌላም የተቀመጡበትን ወንበር ወክለው ለለቅሶ በቦታው የተገኙት በርካታ የሃገር መሪዎች፤ ታዋቂ ሰዎች፤ ነበሩ፡፡ በርካታ ጽሁፎችም የማዲባን ታላቅነት በማጉላትና ማንነታቸውን በማወደስ የመላው አፍሪካ አኩሪ መሪነታቸውን ተናግረዋል፡፡ የእኛም ሰውዬ ወንበር ላይ ተቀምጧልና በዚህ ስፍራ ‹‹ተገኝቶ›› ነበር፤ አዎን ተገኘ ይባል፡፡ ተገኝቶም ባደረገው ንግግር አንድም ቦታ ላይ ማንዴላ፤ በኢትዮጵያ እንደነበሩና ስልጠናም እንደተሰጣቸው፤ ማንዴላ ለኢትዮጵያ የተለየ ፍቅር እንዳላቸውና የኢትዮጵያ ጉዳይ እንደሚቆረቁራቸው የታወቀ ቢሆንም የተገኘው የኛ ሰውዬ ግን ስለዚህ ጉደይ አንድም ቃል አልተነፈሰም፡፡
ይህ ደሞ ብዙዎችን ኢትዮጵያዊያን ሲያናድድና ሲያበሳጭ የሌሎች ሃገራትን ሰዎች ደግሞ አስገርሞ አስደምሟል፡፡ ለምን ሊባል ግን አይገባም ምክንያቱም ሰበቡ የታወቀ ነውና! የኛ ሰውዬን የፈጠራቸው ሰውዬ በሞቱ ጊዜ ባደረገላቸው የብድር መላሽ ያድርገኝ፤ እኔን ደፋ ያድርገኝ ንግግሩ ላይ በዓለም ተወዳዳሪ የማይገኝላቸው መሪ ብሎ በመናገሩ በማዲባ ስርአተ ቀብር ላይ ከተናገረው ያለፈ መናገር አይችልም፡፡ እንዴት አድርጎ ማዲባን ሊያመሰግኑና ከኢትዮጵያ ጋር ስለነበራቸው ፍቅር ሊናገር ይደፍራሉ፡፡ የሱ ጀግና እኮ ከበረሃ ጀምሮ ሲገድል ሲያስገድል በመግደል ተወዳዳሪ ያልተገኘለት ነው፡፡
ማንዴላ መች ገደሉ? መች አስገደሉ? የሱ ጀግና እኮ ስልጣንን በካርድ ስርቆትና በእስር ያገኘው ነው ማንዴላ መች የምርጫ ካርድ ሰረቁ? መችስ ተቃዋሚ አሰሩ? የሱ ጀግና እኮ ሰላማዊ ሰዎችን ወንድ ሴት ሳይል፤ ልጅ አዋቂ ሳይመርጥ ያሰጨፈጨፈ ነው ማንዴላ መች ለዚህ የውርደት ክብር በቁ? የሱ ጀግና እኮ ራሱን ሽቅብ አውጥቶ ከታማኝነት ርቆ፤ ከአንድነት ተለያይቶ፤ ተወልዶ ያደገበትን ሃገር የከዳ ነው ማንዴላ ሃገራቸውን መች አፈራረሱ መቼስ ከዱ? የሱ ጀግና ከኢትዮጵያዊያን የውጭ ዜጎችን የሚያፈቅር፤ በአፍቅሮ ነዋይ ሰክሮ የረገጠውን ሁሉ ለሽያጭ፤ የተቃወመውን ሁሉ ለእስር፤ ለምን ያለውን ሁሉ ለሞት የሚዳርግ ነው ማንዴላ ከወገኖቻቸው ምንንም ሳያስበልጡ፤ ከሃገራቸው ሌላውን ሳይመርጡ፤ ለቆሙለትና መከራ ፍዳ ለተቀበሉበት ሃገርና ህዝብ ታማንነታቸውን ጠብቀው የተከበሩ ከሃገራቸው አልፈው በዓለም ዙርያ አንቱታን ያገኙ ናቸው እና ወገኖቼ እንዴት አድርጎ ማንዴላንና ኢትዮጵያን አስተሳስሮ ለመናገር ይብቃ፡፡
ከኋላው አለንጋ ይዘው አፍ አፉን የሚጠብቁት መች ያናግሩትና፤ እሱስ መች ከተሰጠው ውጪ ይተነፍስና! ለነገሩ በገዳዮች፤ በሌቦች፤ በአጭበርባሪዎች፤ በንጹሃን አሳሪዎች አፍ የኢትዮጵያና የማንዴላ ፍቅርና ግንኙነት ከሚነገር አለመነሳቱ ይሻላል፡፡ ተዋርደው ከሚያዋርዱ መጠበቃቸው ያልተጠበቀ ምርቃን ነው፡፡

No comments: