Tuesday, December 24, 2013

የወያኔ ጋሻ ጃግሬዎች እጣ ፈንታ

December 24/2013

የኢህአዴግ መንግስት እስካሁን በስልጣን ላይ በቆየባቸው አመታት እንደ አንድ የስርዓቱ ግብአት የሚጠቀመው ለፍርሃት አሊያም ለጥቅም ያደሩ አጃቢዎችን  ወደ ኢህአዴጋዊ መዘውሩ በማስገባት መሆኑ የታወቀ ነው። አጃቢዎችን በውድም ሆነ በግድ ወደ መዘውሩ ካስገባ በሁዋላም እንደ ቀደምት የአውሮፓ ቅኝ ገዥዎች እንዳደረጉት ተገዥውን ህዝብ በእጅ አዙር የሚገዙበት ስትራቴጂያዊ መንገድ በመጠቀም ከየብሄሩ ይመለምላሉ።ይህንን ስልም የወያኔ መንግስት በቀጥተኛ መንገድ ሀገሪቱን በሃይል መግዛት ያቅተዋል ማለቴ አይደለም።እስካሁንም በጉልበት እየገዛ ነውና ! ነገር ግን የእያንዳንዱ ብሄር ብሄረሰብ ህዝቦች በራሳቸው ሰዎች አማካይነት መግዛቱ ድካሙን ያቀልልናል በሚል እሳቤ ነው ።
      ታዲያም እነኝህ አድርባዮች አሳድጎ ለወግ ለማእረግ ያበቃቸውን ምስኪን ህዝባቸውን ለወያኔ መራሹ ቡድን ለጊዜያዊ ጥቅማቸው ሲሉ ሽጠዋልም እየሸጡም ነው።ለሆዳቸው ማደሩንስ ይደሩ ቢያንስ ግን ወክለነዋል የሚሉት ወገናቸው መብቱ ሲገፈፍ፣ መሬቱ ተቆርሶ ለባእድ ሀገር በግፍ ሲሰጥበት ሲቀጥልም ኢሰብአዊ በሆነ ሁኔታ የወያኔ ክንድ ሲያርፍበት ጆሮ ዳባ ልበስ ባይሉ ምንኛ ጥሩ ነበር።ሞት አይቀር ! እምቢ ላገሬ! እምቢ ለወገኔ !  ብለው የሚወሰደውን እርምጃ ቢቀበሉ ብዬ ግን እጅጉን ተመኘሁ።እንደ እኔ ሀሳብ ግን እነኚህ ሰዎች የወገኖቻቸው ስቃይና ዋይታ ሳይሰማቸው ወይንም ሳያንገበግባቸው ቀርቶ አይመስለኝም በፍርሃትና በጥቅም ታውረው እንጂ። "ላሰም ቀመሰ ያው በላ ነውና ተረቱ " ከአህአዴግ ጋር አብረው ህዝቡ ላይ ባደረሱት ሰቆቃ ልክ  ተመጣጣኝ ቅጣት ይገባቸዋል ብዬ አምናለው ።
     የዚህች አጭር ጽሁፌ መነሻ የሆኑኝ ከነዚህ ጋሻ ጃግሬዎች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ አያሌው ጎበዜ የሰሞኑ የስንብት ዜና ስለሆነ ስለ እሳቸው የሰማሁትን ጠቀስ አድርጌ አልፋለው  ።
      ለረዥም አመታት የአማራው ክልል ፕሬዘደንት የነበሩት አቶ አያሌው ጎበዜ በትጥቅ ትግል ውስጥ የነበሩ፤ ከነታምራት ላይኔ፣ አዲሱ ለገሰ፣ ተፈራ ዋልዋ፣ ህላዌ ዮሴፍ ጋር ሆነው በኢህዴን ውስጥ ያገለገሉ ሰው ናቸው። ከስልጣናቸው ተሰናብተው  በሳቸውም  ምትክ  የብአዴን  እና  የክልሉ ምክትል ፕሬዘደንት የሆኑት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው  በምትካቸው  ስልጣኑን  እንደተረከቡም ሰምተናል ። የወያኔ ከፍተኛ ባለስልጣናት እንደሚሉት  ከሆነ፤ “የአሁኑ የስልጣን ሽግሽግ፤ የቀድሞዎቹን ባለስልጣናት በአዳዲስ ሰዎች የመተካካት የስራ ሂደት ነው” ብለዋል።  እንደ አብዛኛው ለሁኔታው ቅርብ የሆኑት ሰዎች አስተያየት “አቶ አያሌው ጎበዜ ስልጣናቸውን የለቀቁት፤ ቀደም ሲል የአማራ ክልል የነበረው እና አሁን የትግራይ ክልል የወሰደው ሰፊ እና ለም መሬት ለሱዳን መሰጠቱን በመቃወማቸው ነው” ይላሉ። ለዚህም እንደማስረጃ የሚያቀርቡት ከ3 ወራት በፊት፤ በመስከረም ወር ላይ በባህር ዳር ተደርጎ በነበረው የድንበር ጉዳዮች ውይይት ላይ፤ አቶ አያሌው ግልጽ በሆነ መንገድ የሃሳብ ልዩነት ማቅረባቸው እንደሆነ ይወራል። እንደሚባለውም ከሆነ በወቅቱ ከህወሃት ሰዎች ጠንካራ የሆነ ጉሸማም ደርሶባቸው ም ነበር።
     የሰሞኑ የጥሎ ማለፍ ውድድር የሚመስለው የሙስና ትርምስ እና በመተካካት ስም ተቀናቃኞቻቸውን ከስልጣን ማባረር በውስጥ ፖለቲካ  እየተካሄደ ያለውን ኩነት  ቁልጭ አድርጎ ያሳያል የሚል ግምት አለኝ። በዚህም ሽኩቻ የተሸነፉት ባለስልጣናት  በወያኔ ዘንድ እንደ ግዞት በሚቆጠረው በአምባሳደርነት ተሹመው ወደ አንዱ ሀገር  እንዲሄዱ ሲደረግ ቀሪዎቹ ነገሩ የከፋባቸው ደግሞ እንዲታሰሩ አሊያም ከሀገር እንዲሰደዱ ይደረጋል ። አቶ አያሌው ጎበዜም በዚሁ መሰረት በአምባሳደርነት ተሹመው ወደ አንዱ ሃገር ሊሄዱ እንደሚችሉ ጭምጭምታ ይሰማል ።
     ለነገሩ በኢህአዴግ  ውስጥ ከሚገኙ አብዛኛው ሰዎች በድርጅቱ ርዕዮተ አለም አምነው የተመዘገቡ እንዳልሆነ በገሀድ ይታወቃል ።ምክንያቱም ድርጅቱ ወጥ የሆነ የፖለቲካ ፍልስፍና የለውም።የሚበዙትንም ሰዎች ወደ ኢህአዴግነት እያመጣቸው ያለው ነገር ጥቅም ብቻ ነው።
       ወደ ጽሁፌ ማጠቃለያ ስገባ ጉድና ጅራት ከወደሁዋላ ነው እንዲሉ ያቺ ወደውም ሆነ ተገደው የተቀመጡባት ወንበር  የአገልግሎት ዘመኗ ሲያከትም ወይም ወያኔ አላምጦ ሲተፋቸው የተፈጠሩበትን ቀን እስኪረግሙ ድረስ እምጥ ይግቡ ስምጥ ሳያውቁ ማጣፊያው ሲያጥራቸው በየጊዜው እየተመለከትን ነው።
      እንኚህ ጋሻ ጃግሬዎች ወያኔ እንደ አሮጌ ቁና አውጥቶ ሲወረውራቸው ከሰፊው ህዝብ ወይም ለአመታት ለጥቅም ሲያድሩለት ለኖሩለት ወያኔ ሳይሆኑ  እንደ ውሃ ላይ ኩበት ሲንሳፈፉ እያየን ነው ። ያለጥርጥር የተቀሩትም አድርባዮች በቅደም ተከተል  የመገፋትን ጽዋ እንደሚጎነጩ አምናለው ።ጊዜ ደጉ ሁሉን ያሳየናል !!!

No comments: