Thursday, December 19, 2013

ሕወሓት እና መስእዋትነት (የሕዝብ ልጆችን መስእዋትነት በክህደት የተካ መንግስት)

December 19/2013

 ሕወሓት እቃወማለሁ የምትሉ ሰዎች የሕወሓት ድርጊት የሆነውን ዘረኝነት ባትረጩ መልካም ነው:: የትግራይ ህዝብ ንጹህ ኢትዮጵያዊ ነው:: የትግሉ ጊዜ የነበረው እና አሁን ያለው የሕወሓት እና የትግራይ ሕዝብ ግንኙነት በጣም ሻክሯል:: የትግራይ ሕዘብ የሕወሓት ደጋፊ ቢሆን ኖሮ በአሁን ወቅት ሕወሓት እርስ በርሱ ባልተባላ ነበር የትግራይ ህዝብ እንደሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሁሉ እያከከ የታጋዩ እናት ..ልጅሽ በረሃ የገባው ተርቦ ነው እንጂ፤ ለኛ ብሎ አልወጣም.. እየተባለች እያለቀሰች ትገኛለች ፡፡ እነኛ ፈንጅ እርገጥ ካንተ መስዋእትነት በስተጀርባ ድል አለ፤ ብልጽግና አለ ይሉት የነበሩ መሪዎች አሁን በስልጣን ኮርቻቸው ላይ ተፈናጠው ፍጹም ጸረ-ዴሞክራሲና ሙሰኞች ሆነው ይገኛሉ፡፡ ተወዳዳሪ የማይገኝላቸው ጉበኞች ፣ የመሬት ሻጮች ፣ አገር ሻጮች ሆነው አርፈውታል፡፡

በትጥቅ ትግል ጊዜ አንድ አንድ ሰዎች የህወሓትን ስብስብ "የሰዎች ስብስብ" ነው ወይስ "ሰዎች መስለው መላእክት ናቸው የተሰባሰቡበት.. "የሚል ጥርጣሬ ውስጥ ሁሉ እስከመግባት ደርሰው እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ እንደ ዛሬ አያድርገውና በጊዜው የህዝብን ችግር ለመፍታት ህወሓት መስዋእትነት ለመክፈል ተወዳዳሪ አልነበረውም፡፡ የህወሓት መሪዎች ታጋዩ ለመስዋእትነት እንደተፈጠረና የሱ መስዋእትነት ሰላም፣ ብልጽግና፣ ለሁሉም ዜጋ እኩል የስራ እድል፣ ትምህርት እንደሚያገኝ፣ በህግ ፊት ሁሉም ዜጋ እኩል እንደሚሆን በማስተማርና በማሳመን ፈንጅ እንዲረግጥ አድርገውታል፡፡ የዚያ ዘመን ትውልድ የመስዋእት ትውልድ እንደሆነ ተቀብሎና አምኖ ታሪክ ሰርቶ አልፎዋል፡፡

አንድ ግዳጅ አለና ቅድሚያ መስዋእት ለመክፈል ዝግጁ የሆነ ማን ነው ተብሎ በሚጠየቅበት ጊዜ ልክ ተማሪዎች ክፍል ውስጥ ጥያቄ ሲቀርብላቸው ለመመለስ እኔ እኔ እያሉ እንደሚሽቀዳደሙ ሁሉ ታጋዩ ለአንዴና ለመጨረሻ ህይወቱን ለመክፈል ይሽቀዳደም ነበር፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ ይመጣል ብሎ አልገመተማ፡፡ በዚሁ ጊዜ አድልዎ ተፈጸመ ሊባል የሚችለው ለመስዋእትነት ቅድሚያ አልሰጠም በማለት ታጋዩ ለበላይ አለቃው (ጠርናፊው) ሂስ ማቅረብ ነበር፡፡ እንደ ዛሬ የህዝብና የመንግስት ሃብት መውረር የሚባለ ነገር አልነበረም፡፡
ታጋዩ ለመስዋእትነት ..እኔ ልቅደም.. እና ..የለም እኔ ነኝ መቅደም ያለብኝ.. ሲል ግን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ህይወቱን እያጣ መሆኑን ዘንግቶት አልነበረም፡፡ ዳግም ተመልሶ በሱ መስዋእትነት የተገኘውን ድል እንደማያየው አስረግጦ ያውቅ ነበር፡፡ በእኔ መስዋእትነት ጥቂቶች ያውም ፈንጅ እርገጥ ብለው ትእዛዝ በመስጠት የህዝብ መስዋእትነት ከንቱ ነገር ያተርፉበታል የሚል እምነት አልነበረውም፡፡ መስዋእትነቱን ከድተው በስልጣን ይጨማለቃሉ ብሎ አልገመተም ነበር፡፡ ጀግናው አሞራው በደርግ ቁጥጥር ስር ወድቆ ለምንድን ነው በረሃ የሄድከው ሲሉት እንደሚገድሉት እያወቀ ስልጣኑን በህዝብ ለሚመረጥ መንግስት ለማስረከብ ነው አለ፡፡ ለዚህም መስዋእትነት የግድ እንደሚልና ለመስዋእትነት ዝግጁ እንደሆነ በጠላቶቹ ፊት ሆኖ የመለሰው የውስጡን እምነት ደብቆ ጠላት ወይም ደርግ የሚፈልገውን ሃሳብ ተናግሮ ህይወቱን ማትረፍ አቅቶት አልነበረም፡፡ ወይም ደርግ እንደሚረሽነው ዘንግቶትም አይደለም፡፡ ነገር ግን በእሱ መስዋእትነት ህዝቡ ሰላምና ብልጽግና ያገኛል፤ ሁሉም ዜጋ በነፃ የሚኖርባት ኢትዮጵያ ትመጣለች በሚል ቅንነት ነበር፡፡ ህዝብ የመረጠው መንግስት ይመሰረታል፤ ህዝብ የሚቆጣጠረው መንግስት እንጂ መንግስት ህዝብን የሚቆጣጠርበት እና የሚያስፈራራበት አመራር በእኔ መስዋእትነት ይወገዳል የሚል እምነትም ስለነበረው ነው፡፡ በሱ መስዋእትነት፣ በታጋዮች ቤተሰብ እና በጭቁኑ ህዝብ የተመረጠው መንግስት ህዝብ የሚቆጣጠረው ይሆናል ብሎ ነበር፡፡ በተገላቢጦሽ በዚሁ ጊዜ በጠላትነት ተሰልፈው ይዋጉት የነበሩና አሁን ከመስዋእትነት ከተረፉ በስልጣን ላይ ያሉ ታጋዮች የታጋዩን እናት አባትና ልጆች እንደ ጠላት ፈርጀው ያሰቃዩታል የሚል እምነት አልነበረውም፡፡ ፈንጅ እርገጥ እያሉ መስዋእትነት እንድንከፍል ትእዛዝ ይሰጡን የነበሩ ሰዎች በወላጆቻችንና ልጆቻችን ላይ ክህደት ይፈጽማሉ ብሎ ማን ይገምታል፡፡ ግን በተግባር ክህደት ተፈጸመ፡፡
የታጋዩ እናት ..ልጅሽ በረሃ የገባው ተርቦ ነው እንጂ፤ ለኛ ብሎ አልወጣም.. እየተባለች እያለቀሰች ትገኛለች ፡፡ እነኛ ፈንጅ እርገጥ ካንተ መስዋእትነት በስተጀርባ ድል አለ፤ ብልጽግና አለ ይሉት የነበሩ መሪዎች አሁን በስልጣን ኮርቻቸው ላይ ተፈናጠው ፍጹም ጸረ-ዴሞክራሲና ሙሰኞች ሆነው ይገኛሉ፡፡ ተወዳዳሪ የማይገኝላቸው ጉበኞች ፣ የመሬት ሻጮች ፣ አገር ሻጮች ሆነው አርፈውታል፡፡ ክህደት የፈፀመ ልዩ መንግስት የተባለበትም ለዚሁ ነው፡፡

No comments: