Tuesday, December 31, 2013

የገዢው ፓርቲ ያለመረጋጋት እና ቀጣይ የመድበለ ፓርቲ ዕጣ ፈንታ (አቶ ግርማ ሠይፉ )

December 31/2013
ግርማ ሠይፉ 

ፓርቲና መንግሰት ተቀላቅለዋል ብለን ስንል ትርጉሙ ብዙ እንደሆነ አንባቢ ይረዳዋል ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ
መረዳት ኢህአዴጋዊ አንባቢዎችን የሚጨምር አይመስለኝም፡፡ በእነሱ መስመር ምን ችግር አለው ብለው ጉንጭ
አልፋ ክርክር ለመግጠም የሚችላቸው የለም፡፡ ከላይ የሚገኙት ቱባ ባለስልጣናት አውቀው የሚያደርጉት
በስልጣን መቆያ ስለሆነ አውቆ አጥፊ ብለን ልንፈርጃቸው እንችላለን፡፡ ቀሪው ጀሌ ግን አውቆም ይሁን ሳያውቅ
ከላይ በሚወድቅለት ፍርፋሪ ተደልሎ የሚያደርገው ነው፡፡

 የፓርቲና መንግስት መቀላቀልን ለማስረዳት አንድ
ምሳሌ ላሳይ፡፡ ባለፈው ሳምንት ሀርብ ወንድማችንን አንዱዓለም አራጌን ልጎበኝ ወደ ቃሊቲ ወህኒ ቤት ወርጄ
ነበር፡፡ እንደ ቀድሞ መንገላትት አልደረሰብኝም፡፡ ሀጎስ የሚባል የወህኒ ቤቱ ኃላፊ ሌላ ሀጎስ መድቦልኝ በስርዓት ተሰተናግጄ ነው
የወጣሁት፡፡ መግቢያው ሰዓት እስኪደርስ ግን በመግቢያ በር ላይ ያሉትን ማስታወቂያዎች ሳነብ አንዱዓለም ከጎበኘሁት የቆየሁ መሆኑን የተረዳሁት ህዳር 11 የተለጠፈ ማስታወቂያ ሳነብ ነው፡፡

ማስታወቂያው እንዲህ ይላል “33ኛ ው የብአዴን ምስረታ በዓል ህዳር 14 በድምቀት ስለሚከበር በቀጠሮ ማረሚያ ቤት አዳራሽ ከቀኑ በ7፡00 ሰዓት እንድተገኙ” ይልና በማስከተል “የቀድሞ ብአዴን፣ ሕውሃት እና ኦህዴድ ታጋይ የነበራችሁ በክብር ተጋብዛችኋል” ብሎ ከመጨረሱ በፊት “በዕለቱ ከቀኑ 6፡00 በከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ ቤት ሰርቪስ እንደተዘጋጀ” በመግለፅ ማስታወቂያው ያበቃል፡፡ ገረመኝ ምን ያስገርማል እንደማትሉ ተሰፋ አደርጋለሁ፡፡ የተከበራችሁ የምርጫ ቦርድ ኃላፊዎች እባካችሁ ፓርቲዎች ሁሉ እኩል ከሆኑ ለእኛም ይህ ዕድል ይመቻችና በቀጣይ የአንድነት ፓርቲ የምስረታ በዓልን በከፍተኛ ጥበቃ እስር ቤት ከሚገኘው ወንድማችን ጋር አብረን እንድናከብር ይደረግልን፡፡

 ልብ በሉ እንግዲ አንድነት ፓርቲ የምስረታ በዓሉን “በማረሚያ ቤት” በሚገኝ አዳራሽ አይደለም በህግ የሚጠበቅበትን የጠቅላላ ጉባዔ በግል ሆቴል እንዳያካሂድ የመንግሰት ማፊያ ቡድን እየተከታተለ በሚያስፈራራበት ሀገር ውስጥ ያለምንም ይሉኝታ የቃሊቲ “ማረሚያ ቤት” ፖሊሶች የብአዴንን ልደት በመንግስት አዳራሽ በመንግሰት ሰርቪስ ያከብራሉ፡፡ ቁምነገሩ እነዚህ የስራዊት አባላት ከማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ አባልነት ገለልተኛ የመሆን ግዴታ ሁሉ ያለባቸው መሆኑን በመዘንጋት እና በማን አለብኝነት የሚፈፀሙት ድርጊት እንደሆነ መረዳት ይኖርብናል፡፡ መንግሰትና ፓርቲ ተቀላቅለው ውሃና ወተት መሆናቸውን ብዙ ምሳሌዎች አቅርበን ይፋ ማድረግ ያለብን ይመስለኛል፡፡ ዛሬ ግን ይህ መንግሰትና ፓርቲ ቅልቅል ዋናው አጀንዳችን አይደለም፡፡ ኢህአዴግ ከመንግሰት ጋር ተቀላቅሎም ቢሆን የተረጋጋ ቁመና አለው ወይ?የሚለው ለዛሬ ዋናው ነጥብ ሆኖ ይቀጥል፡፡ ምንም ጥርጥር የሌለው ግን መንግሰትን በወተት ብንመስለው፤ ወተት ውስጥ ውሃ በዝቶ ወተቱ ለዛ አጥቶዋል፡፡ ብዙ ሰዎች ኢህአዴግ እንደ ፓርቲ እንዲሁም መንግሰት እንደ መንግሰት ለቀጣይ ምርጫ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማሻሻል ፍላጎት ሊኖራቸው ይችላሉ ወይ? የሚለውን ጥያቄ በአዎንት ለመመለስ ብዙ ሰዎች እየተቸገሩ ይገኛሉ፡፡ እኔም የዚህ ሃሳብ ከሚጎትታቸው ሰዎች ውሰጥ ልመደብ እችላለሁ፡፡

ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሞት በኋላ የኢህአዴግ መሪ በሌላ ሰው እጅ ስለገባ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በመርዕ ደረጃ እንቀበለዋለን የሚሉትን የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ለመተግበር ከጫካ ፖለቲካ አዙሪት ወጥተው ያሰባሉ የሚል ፅኑ ዕምነት አሳድሬ የነበረ ሲሆን አሁን ግን የምናየው ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሞት በኋላ ያለፉት 18 ወራቶች ይህን ተሰፋ የሚመግቡ ሳይሆኑ ኢህአዴግመረጋጋት የተሳነው መሆኑ ነው፡፡ ይህ መረጋጋት ማጣት ደግሞ በድፍረት የፖለቲካ ሜዳውን ለመክፈት መንገድ የሚዘጋ ይመሰለኛል፡፡   ያለ መረጋጋቱ ምልክቶች ምንድናቸው ብለን እንፈትሽ፡፡

የገዢው ፓርቲ በጥሩ ቁመና ላይ ቢሆንልን በሀገራችን ዘላቂ የመድበለ ፓርቲ ስርዓት ለመገንባት ዕድል ጭምር ይሆናል የሚል እምነት ያለን ሰዎች ብዙ ነን፡፡ ያለመታደል ሆኖ አሁን የምናየው ሁኔታ ይህን ተሰፋ የሚያዳብር አይደለም፡፡ ከአቶ መለስ ዜናው ሞት በኋላ ፖለቲካው የሾፌር ለውጥ ሲያደርግ ሾፌሩ የፖለቲካ ስትራቴጂና አካሄድ ለውጥ ባይኖር እንኳን በጥንቃቄ በመንዳት ተሳፋሪዎችን ሳያንገጫግጩ ለማድረስ ይችላሉ የሚል ሃሳብ ነበረኝ፡፡ አሁን እየተደረገ ያለው ግን ምርጫ ለማሸሸነፍ ይረዳናል ያሉትን ፕሮፓጋንዳ አጠናክረው የቀጠሉ ነው የሚመስለው፡፡ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ያለመሳካት የሚያስጠይቃቸው ሳይሆን ስለ አሰቡት ብቻ የሚያስመሰግናቸው አድርገው እየወሰዱት ነው፡፡ ለዚህም ያለምንም ተቀናቃኝ ለቀጣይ አምስት ዓመት በስልጣን መቆየት አለብን ብለው የወሰኑ ይመስላል፡፡ ይህን ውሳኔ ደግሞ ተግባራዊ ለማድረግ ለወሰነ ፓርቲና መንግሰት በሩን ለተቃዋሚ ነፃ ውድድር ክፈት ማድረግ አደጋ አለው ነው የሚሉት፡፡ባጠቃላይ ሲታይ ኢህአደግ በአዲሱ ትውልድ እራሱን ለማደራጀት የቻለ ፓርቲ አይደለም፡፡ በዚህም መነሻ ከጀማሪ እሰከ ነባር ታጋዮች የመንግሰትን ሹመት ቦታዎች እንደ ካርታ ፕወዛ ሲቀያየሩት እንጂ አዲስ ነገረ ማየት አልቻንም፡፡ የሁለት ሺ ሁለት ምርጫን ተከትሎ መንግሰት የመሰረተው ኢህአዴግ አባል ፓርቲዎቹ መንግሰት ከመሰረቱበት ክልል የመረጋጋት ሁኔታ አይታይበትም፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው የክልል ርዕሰ መስተዳድሮች የምረጫ ዘመናቸውን መጨረስ አልቻሉም፡፡ የአዲሱን ጠቅላይ ሚኒሰትረ ሰራ መጀመር አስመልክቶ ብዙ ለውጥ የለም ብለው በጉድለት መሙላት የጀመሩት ኢህአዴጎች ትንሽ ሳይቆዩ ነው “እንደ ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር”በሚል የብሔር ተዋፅኦ ያገነዘበ ሹመቶች ይፋ የተደረጉት፡፡ ግርማ ሠይፉ ማሩ መተካካት ብለው አዳዲሰ ፊቶች ያሳዩናል ብለን ተሰፋ ስናደርግ በአማካሪ ሰም ሁሉንም የቀድሞ የአባመተካካት ብለው አዳዲሰ ፊቶች ያሳዩናል ብለን ተሰፋ ስናደርግ በአማካሪ ሰም ሁሉንም የቀድሞ የአባል ድርጅት መሪዎች (አባይ ፀኃዬ፣በረከት ሰምኦን፣ ኩማ ደመቅሳ፣ ካሱ ኢላላ) የፖሊሲና ምርምር አማካሪ አድርጎ ማሰባሰብ ምን የሚሉት መተካካት እንደሆነ ግልፅ ባይሆንም ጥናትና ምርምር የብሔር ጥንክር ይፈልግ እንደሆነ ሰለማይገባኝ የፓርቲው ያለመረጋጋት ምልክት አድርጌ ለመገመት የሚከለክል ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡

ትልቁ የኦሮሚያ ክልል ከምርጫው ማግሰት ጀምሮ ክልሉን እንዲመሩ የአቶ መለስ ግርፍ ናቸው የሚባሉት አቶ አለማየሁ አቶምሳ
ቢረከቡትም ከሶስት ዓመት በላይ ለሶስት ወር እንኳን አመራር መስጠት የቻሉ አይደሉም፤ እንደዚያም ሆኖ ኦሮሚያ ክልል ለክልል ፕሬዝዳንትነት ማስታወቂያ አውጥቶዋል ተብሎ እስኪሾፍ ድረስ ቦታው ክፍት ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ቢኖርም ባይኖርም ችግር የለም የሚያስብል ነው፡፡ ወጣቱ ምክትል ርዕስ መሰተዳድረ ወይም ሌሎች ወጣት የኦህዴድ አባላት ይህ ቦታ ቢገባቸውም ሊስጣቸው ያልተፈለገበት ምክንያት ግልፅ አይደለም፡፡ በአሁኑ ይዞታ እስከሚቀጥለው ምርጫ ድረስ ኦሮሚያ ርዕስ መስተዳድር ሳይኖረው ይቀጥላል፡፡ ከቀጣዩ ምርጫ በኋላ ወጣቶቹ ታግለው ይይዙታል ወይም ከጎምቱዎቹ አንዱ የፌዴራል ሚኒስትር ቦታውን ትቶ ክልሉን ይረከብ ይሆናል፡፡ መቼም ይህን ትልቅ ክልል ለወጣት ይሰጡታል ማለት ከባድ ነገር ነው፡፡

“ደቡብ” ክልል የምርጫ ዘመን የሚጨርሱ የፖለቲካ ሰዎችን ማቅረብ የቻለ አይደለም፡፡ ሁሉም እንደሚያውቀው የደቡብ ክልል በሲዳማ እና በወላይታ በዋነኝነት ግብግብ ያለበት ክልል ነው፡፡ ለኢህአዴግ አጋር ፓርቲዎች ጠቅላይ ሚኒስትር ቦታ እንደማይታሰብ ሁሉ፤ ለደቡብ ክልልም ከሲዳማ ውጪ የክልል ርዕሰ መሰተዳደር አይታሰብም የሚሉ ብዙ ናቸው፡፡ ሌሎች የክልሉ ህዝቦች እንዴት እንደሚያዩት ወደፊት ይታያል፡፡ በ1997 ምርጫ ቦታውን ይዘውት የነበረው አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ (ከወላይታ)፤ ለአቶ ሽፈራው ሸጉጤ (ሲዳማ) አስረክበው መጥተዋል፡፡ ይህች በክልል የተደረገች መፈንቅለ ወንበር አቶ ኃይለማሪያምን ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ስታበቃ፤ ወንበር ፈንቃዩን ደግሞ ትምህርት ሚኒሰትር ብቻ አድርጋለች፡፡

 በ2002 ምርጫ በኋላ ቦታው ላይ የቀጠሉት አቶ ሽፈራው አሁንም ለሲዳማው የቀድሞ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒሰትር አስረክበው ወደ ትምህርት ሚኒስትር ሹመት ይሁን ሽረት መጥተዋል ማለት ነው፡፡ መቼም ወላይታ የጠቅላይ ሚኒስትር ቦታም የክልልም ይሰጠኝ ሰለማይል ይህ የምርጫ ዘመን ደቡብ በሲዳማ መሪነት ይጠናቀቃል ብለን ልንወስድ እንችላለን፡፡ ይገርማል ሀገር በብቃት ሳይሆን በእንዲህ ዓይነት የብሔር ኬሚስትር ሲተዳደር፡፡ ይህ መረጋጋት ያሳያል የሚል ካለ ከመገረም ውጭ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ በቅርቡ ደግሞ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ከስልጣናቸው በቃኝ ብለው ለቀዋል፡፡ የአቶ አያሌው ጎበዜ በቃኝ ምክንያቱ ብዙ ነው፡፡ አንድ አንዶች በቅርቡ ከሱዳን ጋር ከተደረገ ስምምነት ጋር ያያይዙታል፡፡ ይህ እውነት ነው ቢባል ከክል መስተዳደርነት ተነስቶ አምባሳደር በመሆን አይደለም የሚገለፀው፤ ይልቁንም የልዩነትን ሃሳብ ለህዝብ በመግለፅ እንጂ፡፡

ለማነኛውም አቶ አያሌው መተካካት ነው ብለውናል፡፡ መተካካት እንዳልሆነ ሁሉም የሚያውቀው ቢሆንም ደከመኝ ብለው ወደ ሌላ አድካሚ ስራ ተመድበዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤታችን እንደ አለመታደል ሆኖ የጡረታና የመታከሚያ ቦታ መሆኑ ነው፡፡ ከፍተኛ ደረጃ ሚኒስትር የነበሩ ሰዎች አምባሳደር ሆነው ሲሄዱ አስገራሚ ነገር ነው፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበረ ሰው ለአንድ ዳይሬክቶሬት ተጠሪ ለመሆን አምባሳደር ሲሆን ጉዳዩ ሌላ እንደሆነ ይገባናል፡፡ ሌሎችም የጡረታ ቦታዎች እንዳሉ ማወቅ አለብን ወደፊት በስፋት እንመለስበት ይሆል፡፡ የክልሎች ርዕሰ መስተዳድሮች በቃለ መሃላ የያዙትን ቦታ መጨረስ ያለመቻል መረጋጋት ነው ከተባልን “መቼስ ማል ጎደኒ” ከማለት ውጭ ምን ይደረጋል፡፡የትግራይ ክልል በእውነቱ ከአቶ መለስ ሞት በኋላ ኢህአዴግን የሚያጠናክሩ አመራሮች የሚልክ በስብሰባም አጀንዳ አሰቀማጭ ሳይሆን ክልሉም በአዲስ አበባና መቀሌ ቡድን ተከፍሎ የሚንገራገጭ እንደሆነ ነው የምንስማው፡፡ ከአሁን በኋላ በድንገት ያጣውን የጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ ለማግኘት ቢያንስ ሃያ ዓመት በላይ እንደሚያስፈልገው ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት በመለስ ያሉትን ቦታዎች አጠናክሮ ለመያዝም ባለፈው ጊዜ የፓርቲው መሪ የነበሩት አቶ መለስ የድርሻቸውን ተወጥተዋል የሚያስብል ምንም ምልክት የለም፡፡

ጠላት ከሩቅ አይመጣም በሚል ታሳቢ ቤታቸውን እንዳዳከሙት ይታመናል፡፡ አሁን የህውሃት ችግር ታጋዮችን በወጣቶች
ለመተካት የሚደረገው ጥረት ነው፡፡ የትግራይ ነፃ አውጪ በሚል የሚጠራ ድርጅት ደግሞ ይህን ሊያሳካ አይችልም፡፡ ሕውሃትን የሚጠጉ በሙሉ ለፖለቲካ ትግል ሳይሆን ለኢኮኖሚ ጥቅም እንደሆነ እስከ አሁን ያለው ተሞክሮ ያሳየናል፡፡ አንድ አንዶች የሀገሪቱን ፖለቲካ የሚያሽከረክረው ህውሓት ነው ሲሉኝ በምን አቅሙ የምለው ለዚህ ነው፡፡ የአጋር ፓርቲዎችም ቢሆን ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ የአጋር ክልሎች ርዕሰ መስተዳድሮች ደግሞ ሲነሱ በመጀመሪያ ወደ ፌዴራል
የሚኒስትር ደኤታ ወይም ተመጣጣኝ ቦታ እንዲመጡ ማድረግ ነው፡፡ ሶማሌ፣ ቤኒሻንጉል፣ ጋምቤላ ርዕሰ መስተዳድሮች ይኽው ነው የተደረገው፡፡ እነዚህ ሁሉ ሲደመሩ ኢህአዴግ ተረጋግቶ ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት በሩን ከፍቶ ይጫወታል የሚለው ተሰፋ እጅግ የጠበበ ይመስላል፡፡ ይልቁንም ዋነኛ ስትራቴጅስቱን በድንገት በሞት መነጠቅ ብቻ ሳይሆን በቂ ተተኪ ባለማፍራት የሚንገራገጭ ፓርቲ ከስጋት ነፃ የሆነ ምርጫ ለማድግ ሊወስን እንደሚችል መጠርጠር ተገቢ ነው፡፡ ኢህአዴግ ይህ ትንተና ትክክል አይደለም ካለተ በሩን መክፈቱን የሚያሳይ እርምጃ በመውስድ መረጋጋቱን ሊያረጋግጥልን ይገባል፡፡ ለማነኛውም …… ከእኛ ምን ይጠበቃል የሚለው የአማራጭ ኃይሎች ስራ ይመስለኛል፡፡ አማራጭ ሆኖ ለመገኘት ጠንክሮ መስራት የግድ ነው፡፡ 

No comments: