Monday, December 16, 2013

የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ በደቡብ ሱዳን

December 16/2013

በደቡብ ሱዳን ትላንት የተሞከረው የመንግስት ግልበጣ መክሸፉን የኣገርቱ መንግስት ኣስታወቀ። በቀድሞው ም/ፕሬዝደንት ማቻር የተመራው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ የከሸፈው ለፕሬዝደንት ሳልቫኪር ታማኝ የሆኑ ወታደሮች የበላይነትን በማግኘታቸው ነው ተብሏል።
Salva Kiir Präsident Südsudan
የቀድሞው የኣገሪቱ ም/ፕሬዝደንት ከስልጣን የተባረሩት ባለፈው ሀምሌ ወር ሲሆን ቅርበት ያላቸው ምንጮች እንደሚሉት ከዚያ ወዲህ በመንግስትም ሆነ በገዚው የSPLM ግንባር መካከል ክፍፍል ተፈጥሯል።
ከእሁድ ቀትር በኃላ ጀምሮ እስከ ዛሬ ማለዳ የዘለቀው የተኩስ ልውውጥ ኣሁን መቆሙን እና በከተማይቱ ጁባ ኣንጻራዊ መረጋጋት መስፈኑን የኣይን እማኞች ይናገራሉ።
በቀድሞው ም/ፕሬዝደንት የሚመሩ ያኮረፉ ወታደሮች እና ፖለቲከኞች በመንግስት ኃይሎች በተለይም በቤተመንግስት የጸጥታ ኃይሎች ላይ የከፈሩት ድንገተኛ ተኩስ ከየኣቅጣጫው እያስተጋባ ትላንት ምሽት እና ለሊቱን በሙሉ በከተማይቱ ጁባ የዘለቀ ሲሆን የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናትን የጠቀሱ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ውጊያው ዛሬ ጧትም በመጠኑ ቀጥሏል። ዓለማውም በዓለማችን የመጨረሻው ዓዲስ መንግስት የሆነውን የደቡብ ሱዳን መንግስት ለመገልበጥ ነው ተብሏል። በኣገሪቱ ጦር ውስጥ የሚገኙ የተወሰኑ የሰራዊቱ ዓባላትም በዋና ከተማይቱ ጁባ የሚገኘውን የመሳሪያ ግ/ቤት ወረው ለመዝረፍ ሞክረው ነበር። የደቡብ ሱዳን የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ባርናባ ማሪያል ቤንጃሚን ለአሶሺዬትድ ፕሬስ እንደነገሩት ከሆነ ግን ወረራውን በመመከት የመሳሪያ ግ/ቤቱን ለመታደግ ተችሏል። የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ እንደሚሉት ኣንዳንድ ፖለቲከኞችም ተይዟል። የመፈንቅለ መንግስት ሙከራውን የመሩት የቀድሞው ም/ፕሬዝደንት ሬክ ማቻር ስለመያዛቸው ግን ማረጋገጥ ኣልቻሉም። የደ/ሱዳን የመ/ሚኒስቴር ቃ/ኣቀባይ ኮ/ል ፊሊፕ ኣጉዬር ዛሬ ረፋዱ ላይ ለዜና ሰዎች እንዳስረዱት ለፕ/ት ሳልቫኪር ታማኝ የሆኑ ወታደሮች በኣሁኑ ሳዓት የጁባ ከተማን ሙሉ በሙሉ ይቆጣጣራሉ።
በቅጡ የታጠቁ እና መትረየስ በተገጠመባቸው ተሽከርካሪዎች የታገዙ በርካታ ወታደሮች በጁባ ዋና ዋና መንገዶች ላይ ለቁጥጥር ተሰማርተው እንደሚንቀሳቀሱ የገለጹት የዓይን እማኞችም ከወታደሮች በስተቀር ዛሬ ጎዳናዎች ላይ የሚታይ ሰላማዊ ሰው ኣለመኖሩን ለዜና ሰዎች ኣስረድቷል። የግብጽ አየር መንግድም የጁባ ኣውሮፕላን ማረፊያ በመዘጋቱ ዛሬ ወደዚያው ያደርገው የነበረውን በረራ ለመሰረዝ መገደዱን ኣስታውቐል። በዚያ የሚገኘው የተመድ ሰላም ኣስከባሪ ጦር በበኩሉ በከተማይቱ በተጋጋለው የከባድ መሳሪያ ተኩስ ልውውጥ የተነሳ በተጠንቀቅ መሆኑን እና በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ሰዎችም ወደ ካምፓቸው እየሸሹ መሆናቸውን ኣስታውቐል። በኣዲሲቷ የዓለማችን ኣገር ደ/ሱዳን መንግስት ውስጥ ልዩነት እና ፍጥጫ የነገሰው ፕ/ት ሳልቫኪር ባለፈው ሀምሌ ወር ምክትላቸውን ማቻርን ከስልጣን ማባረራቸውን ተከትሎ ነው። ከሁለት ዓመታት በኃላ በ2015 በዚያች ኣገር በሚካሄደው ፕሬዝደንታዊ ምርጫ የሳልቫኪር ብርቱ ተፎካካሪ ይሆናሉ ተብለው የሚጠበቁት የቀድሞው ም/ፕ/ት ማቻር ከስልጣን እንደተባረሩ በሰጡት መግለጫ ኣገሪቱ ኣንድ ሆና እንድትቀጥል ከተፈለገ የኣንድ ሰው ኣገዛዝ ማክተም ኣለበት። ኣንባገነናዊ ኣገዛዝን መታገስ የለብንም ብለውም ነበር። የማቻር መባረር ከመንግስት ም/ቤትም ኣልፎ በገዢው ፓርቲ ውስጥም ክፍፍል መፍጠሩን የተረዱት የUS አሜሪካ እና የኣውሮፓ ህብረት ዲፕሎማቶች ውጥረቱ ወደ እርስ በእርስ ግጭት እንዳያመራ ስጋታቸውን ገልጸው ነበር።
Südsudan Juba Ausschreitungen UN 16.12.2013
ሳልቫኪር የቀድሞው ሸማቂ እና የኣሁኑ ገዢ ፓርቲ SPLM የወታደራዊ ክንፍ መሪ በነበሩበት ወቅት ማቻርን ጨምሮ ኣሁን ከእሳቸው ጋር የተባረሩት የግንባሩ አባላት ለአስርተ ዓመታት ከሱዳን መንግስት ጋር በተካሄደው ውጊያ ወቅት በከፍተኛ የዓመራር እርከን ላይ የነበሩ ናቸው። ዘ ሱዳን ትሪብዩት የተሰኘው ጋዜጣ እንደዘገበው ከሆነ ግጭቱ የተጀመረው፣ ትላንት እሁድ መሆኑ ነው፣ ከፕ/ት ሳልቫኪር የዲንካ ጎሳ የሆኑ ወታደሮችን ለማጥቃት በተንቀሳቀሱ ከኑዌር ጎሳ የሆኑ የማቻር ታማኝ ኃይሎች መካከል ነበር። ጁባ የሚገኘው የአሜሪካ ኢምባሲም ዜጎቹ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኣሳስቧል። የተመድ የደ/ሱዳን ልዩ መልዕክተኛም ውጥረቱ ኣሁንም ድረስ ኣለመቀረፉን ጠቅሰው ሁለቱም ወገኖች በኣስቸኩዋይ ተኩስ ኣቁመው ፖለቲካዊ መፍትሄ እንዲያፈለልጉ ጥሪ ኣድርገዋል።
ጃፈር ዓሊ
ሸዋዬ ለገሰ

No comments: