Monday, December 16, 2013

የህወሀት አመራር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሀኖምን ገመገመ

December 16/2013
የወደፊቱ ጠ/ሚንስትር ሊሆኑ ይችላሉ ተብሎ የሚነገርላቸው ዶ/ር ቴዎድሮስ ግሳጼው የቀረበባቸው " በሳውድ አረቢያ ላይ ተመጣጣኝ የአጸፋ እርምጃ እንወስዳለን" ብለው መናገራቸውን ተከትሎ ነው።

ኢህአዴግ በጉዳዩ ላይ ለመነጋገር አስቸኳይ ስብሰባ የጠራ ሲሆን ዶ/ር ቴዎድሮስም " ያለግንባሩ ውሳኔ እንዲህ አይነት ጠንካራ አስተያየት ለምን እንደሰጡ እንዲያብራሩ ተጠይቀዋል። " ዶ/ር ቴዎድሮስ በቂ ማብራሪያ ለመስጠት ባለመቻላቸው ግለ-ሂሳቸውን እንዲያወርዱ ተጠይቀዋል። ከፓርቲው ይልቅ የግል ዝናቸውን እየገነቡ ነው በሚልም ተገምግመዋል።

የሳውድ አረቢያ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒሰትር ቴዎድሮስ አድሀኖም በሰጡት መግለጫ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጠው ለ አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ ደብዳቤ ማስገባቱን ተከትሎ ነው ግምገማው የተካሄደው።

በሳውድ አረቢያ መንግስት ደብዳቤ የተደናገጡት አቶ ሀይለማርያም ወዲያውኑ በቴሌቪዥን ቀርበው ከሳውድ አረቢያ ጋር የቆየ የዲፕሎማሲ ግንኙነት መኖሩን፣ ይህን ግንኙነት አሁን በተፈጠረው ችግር እንደማይለወጥና ለወደፊቱም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

አቶ ሀይለማርያም የተናገሩትን ተከትሎ በሳውዲ የኢትዮጵያ አምባሳደር የሆኑት ሙሀመድ ካቢራ የኢትዮጵያ መንግስት 361 የኢንቨስትመንት ፈቃድ መስጠታቸውን፣ ሳውዲ በኢትዮጵያ ታላቁ ኢንቨስተር መሆኑን ገልጸዋል።

ዶ/ር ቴዎድሮስ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በጥሩ ስሜት ላይ እንዳልሆኑ ምንጮች ገልጸዋል። ሚኒሰትሩ በፌስቡክ ላይ ባሰፈሩት መልእክት ጠ/ሚንስትሩን በማጀብ በማንዴላ ቀብር ላይ ሊገኙ ያልቻሉት በጤና ችግር ምክንያት መሆኑን ተናግረዋል። ኢህአዴግ በሳውድ አረቢያ ላይ ያሳየው የተለሳለሰ አቋም እየተተቸ ነው። ዶ/ር መረራ ጉዲና ሰሞኑን ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ መንግስት በሳውዲ አረቢያ ላይ የያዘውን ፖሊሲ መተቸታቸው ይታወቃል።

No comments: