Thursday, December 19, 2013

የአማራው ክልል ፕሬዘደንት የነበሩት አቶ አያሌው ጎበዜ ስልጣቸውን ለቀቁ!!

December 19/2013

(EMF) ለረዥም አመታት የአማራው ክልል ፕሬዘደንት የነበሩት አቶ አያሌው ጎበዜ በትላንትናው እለት ከስልጣናቸው እንዲነሱ ተደርጓል። በሳቸውም ምትክ የብአዴን እና የክልሉ ምክትል ፕሬዘደንት የሆኑት አቶ ድጉ አንዳርጋቸው በምትካቸው ስልጣኑን ተረክበዋል። የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት እንዳሉት ከሆነ፤ “የአሁኑ የስልጣን ሽግሽግ፤ የቀድሞዎቹን ባለስልጣናት በአዳዲስ ሰዎች የመተካት ስራ ነው” ብለዋል። ይህ አባባል ግን በብዙዎች ዘንድ እምብዛም ተቀባይነት ያገኘ አይመስልም።

ሆኖም ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ለየት ያለ አስተያየት ይሰጣሉ። “አቶ አያሌው ጎበዜ ስልጣናቸውን የለቀቁት፤ ቀደም ሲል የማራ ክልል የነበረው እና አሁን የትግራይ ክልል የወሰደው ሰፊ እና ለም መሬት ለሱዳን መሰጠቱን በመቃወማቸው ነው” ይላሉ። ለዚህም እንደማስረጃ የሚያቀርቡት ከ3 ወራት በፊት፤ በመስከረም ወር ላይ በባህር ዳር ተደርጎ በነበረው የድንበር ጉዳዮች ውይይት ላይ፤ አቶ አያሌው ግልጽ በሆነ መንገድ የሃሳብ ልዩነት ማቅረባቸው እንደሆነ ይነገራል። በወቅቱ ከትግራይ ክልል ሰዎች ጠንካራ የሆነ ተቃውሞ ቀርቦባቸው ነበር። ስልጣናቸውን የለቀቁትም ለህዝብ ጥቅም ሲሉ እራሳቸውን አሳልፈው ለመስጠት ካላቸው ፍላጎት በመነሳት እንደሆነ፤ የራሳቸው ሰዎች ከሚሰጡት አስተያየት ለማወቅ ችለናል።
Ayalew Gobeze
Ayalew Gobeze
በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ፤ በወልቃይት የሚገኙ የአማራ ተወላጅ ተማሪዎች፤ የትምህርት አሰጣጡን በመቃወም “በትግርኛ አንማርም” በማለታቸው ምክንያት ቁጥራቸው 3ሺህ የሚደርሱ አማሮች፤ “በትግርኛ ካልተማራቹህ ወደ አማራ ክልል መሄድ ትችላላቹህ።” ተብለው ክልሉን ለቀው እንዲወጡ በመባላቸው፤ እንዲሁም ለረዥም አመታት የአማራ ክልል ውስጥ የነበረው የራስ ዳሽን ተራራ ግርጌ የሚገኙ ቦታዎችን የትግራይ ሚሊሻዎች እየወሰዱት በመሆናቸው ከዚህ ጋር ተያይዞ በተነሳው ውዝግብ፤ በተጨማሪም የትግራይ እና የአማራ ክልል ባለስልጣናት በድንበር ጉዳይ የሚያነሱትን እልህ አስጨራሽ ድርጊት መሸከም ስላቃታቸው ስልጣናቸውን በፈቃዳቸው እንዲለቁ ግፊት የተደረገባቸው መሆኑን የቅርብ ምንጮች ይገልጻሉ። እንደዚህ አይነት አለመግባባት ሲፈጠር ሁለቱም ወገኖች ይፈሯቸው የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ ጣልቃ በመግባባት ለማግባባት ጥረት ያደርጉ እንደነበር የገለጹት ምንጮቻችን፤ አሁን ግን የትግራይ ባለስልጣናት በማን አለብኝነት ክልሉ ማድረግ የሚገባውን ለማዘዝ እንደሚሞክሩ ተገልጿል። በአገር ውስጥ ክልሎች በድንበር ጉዳይ ሲወዛገቡ፤ በህገ መንግስቱ መሰረት ጉዳዩን የሚመለከተው የፌዴሬሽን ምክር ቤት ነው። የፌዴሬሽን ምክር ቤቱ ደግሞ ቀደም ሲል በአባይ ጸሃዬ አሁን ደግሞ በካሳ ተክለ ብርሃን (ሁለቱም የህወሃት አባላት ናቸው) የሚመራ መሆኑ፤ በአማራ እና በትግራይ መካከል የሚነሱ የድንበር ጉዳዮችን በአድሏዊነት ፍርድ ሲሰጡ ቆይተዋል። አሁን ግን አለመግባባቱ ግን ግልጽ እየሆነ መጥቶ የአማራ ክልል ፕሬዘደንት ስልጣናቸውን እንዲለቁ አድርጓቸዋል።

ይህ የሰሜን ኢትዮጵያ ክልል በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ በዋግ ሹሞች፣ በራስ እና በንጉሥ ይተዳደር የነበረ ቦታ ነው። ከሸዋ ጀምሮ እስከ ላስታ፣ ወሎ፣ አንጎት፣ ደምብያ፣ ጎጃም፣ ጎንደር እና በጌምድር በአማራ ክልል ውስጥ የሚገኙ ናቸው። አሁንም ሆነ ወደፊት አወዛጋቢ የሆኑት የሰሜን ወሎ እና የበጌምድር ክፍለ ግዛቶች ግን፤ በግድ ወደ ትግራይ ክልል ተወስደዋል። ከነዚህ ውስጥ ደግሞ የበጌምድርን ምዕራባዊ ክፍል፤ የትግራይ ባለስልጣናት ለሱዳን ለመስጠት የሚያደርጉት ድርድር ብዙዎችን ቅር ማሰኘቱ አልቀረም። አሁን ስልጣናቸውን የለቀቁት አቶ አያሌው ጎበዜም በዚህ ቅሬታ ውስጥ እንዳሉ፤ ስልጣናቸውን የለቀቁ መሆናቸው በሰፊው ይነገራል።

አቶ አያሌው ጎበዜ በትጥቅ ትግል ውስጥ የነበሩ፤ ከነታምራት ላይኔ፣ አዲሱ ለገሰ፣ ተፈራ ዋልዋ፣ ህላዌ ዮሴፍ ጋር ሆነው በኢህዴን ውስጥ ያገለገሉ ሰው ናቸው። አዲሱ ለገሰ የክልሉ ፕሬዘደንት በነበረበት ወቅት፤ አቶ አያሌው ጎበዜ ደግሞ የክልሉ ከፍተኛ ተጠሪ ሆነው እንደአውሮፓውያን አቆጣጠር እስከ 2008 ድረስ አገልግለዋል። ከ2008 ጀምሮ አሁን ስልጣናቸውን እስከለቀቁበት ጊዜ ድረስ ደግሞ የክልሉ ፕሬዘደንት ነበሩ። እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ከሚያደርጉት እንቅስቃሴ አንጻር፤ ስልጣናቸውን የመልቀቅ ምንም ምልክት እንዳልነበረና በመስከረም ወር በኢትዮጵያ እና በሱዳን መካከል ከተደረገው ስብሰባ በኋላ፤ በተለይም ከትግራይ ባለስልጣናት ጋር ልዩነት ውስጥ መግባታቸው በሰፊው ይነገራል።
Degu Andargachew, the new president of Amara region.
Degu Andargachew, the new president of Amara region.
አዲሱ የአማራ ክልል ፕሬዘዳንት የሆኑት አቶ ድጉ አንዳርጋቸው፤ በሰሜን ወሎ ዳውንት ወረዳ ተወለደው ያደጉ ሲሆን፤ ምክትል ፕሬዘዳንት በነበሩበት ወቅት በዘመድ አዝማድ እንደሚሰሩ በሰፊው ይታማሉ። ለምሳሌ እሳቸው በተወለዱበት ስፍራ ከቀበሌ ጀምሮ እስከወረዳ ድረስ ከፍተኛ ባለስልጣን ናቸው። የዳውንት ወረዳ አቃቤ ህግ አቶ ጥላዬ ወንድምነህ፣ የአቅም ግንባታ ሃላፊ አቶ ጌትዬ ወርቁ ሁለቱም የአቶ ደጉ አንዳርጋቸው የ እህት ልጆች ናቸው። የፍትህ ጽ/ቤት ሃላፊዋ ወ/ሮ በላይነሽ ጥላዬ የአጎት ልጅ ናት። የሰሜን ወሎ አስተዳደር አፈ ጉባዔ አቶ አጥናፉ፣ የውሃ ልማት ሃላፊ አቶ ብርሃኑ ደምሴ ሌሎች ቤተሰቦች ናቸው። አቶ ድጉ አንዳርጋቸው ምክትል ፕሬዘዳንት ተብለው ወደ ባህር ዳር ሲሄዱ የአክስታቸውን ልጅ አቶ ጸጋ አራጌን በስፍራው ሾመው ነበር የሄዱት። አቶ ጸጋ አራጌ ለትምህርት ሲላክ ቦታውን፤ ማለትም የዳውንት ወረዳ አስተዳዳሪ የሆኑትነትን ለአቶ ዣንጥራር የአቶ ገዱ የወንድም ልጅ ሰጥተው ነበር የሄዱት። የወረዳው የጸጥታ ዘርፍ ሃላፊው የአቶ ዣንጥራር ወንድም ናቸው። እንዲህ ያለው የርስ በርስ መጠቃቀም ወይም በስልጣን የመጠቀም ነገር ዝርዝሩ በዛ ያለ ነው። ለአሁኑ ስለአዲሱ ፕሬዘዳንት ማለት የሚቻለው ግን ይህን ያህል ነው።

No comments: