Wednesday, December 25, 2013

‹‹በታማሚዎች መነገድ ስንት ያተርፋል?›› (ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ – ከቃሊቲ እስር ቤት)

December 24/2013

“ፀሐይ በሞቀው…” የፍርድ ሂደት ራሴን ለመከላከል አቅርቤው ከነበረው የተከሳሽ የመከላከያ ቃል በኋላ ዳግም ድምጼን ለማሰማት የተመለስኩበት አጋጣሚ ለወራት ሲያሰቃየኝ ለቆየው የኩላሊት ሕመሜ የቃሊቲ ማ/ቤት “የጤና ባለሙያዎች” ምንም ሕክምና ሊሰጡኝ እንደማይችሉ መሆኑ ቅር ያሰኘኛል፡፡ ጥልቅ ፍቅር እና ክብር ላለኝ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ከመልካም ዜና ጋር ብመጣ እንዴት ደስ ባለኝ ነበር፡፡ አልሆነማ!
ጉዳዩን የበለጠ ግልፅ ለማድረግ በተደረገልኝ የኩላሊት የአልትራሳውንድ ምርመራ በተለይ በግራ ኩላሊቴ ላይ በአሳሳቢ ሁኔታ እጅግ የተከማቸ አሸዋ መኖሩ ተረጋግጧል፡፡ በግራም በቀኝም ያሉ ወገኖች ይህን በማንኛውም ጊዜ መመልከት ይችላሉ፡፡ (ለጠላትም ለወዳጅም አላልኩም፡፡ ምክንያቱም በግራና በቀኝ በተሰለፉት ውድ ኢትዮጵያውያን መካከል እየከረረ የመጣ የሀሳብና የመስመር ልዩነት እንጂ ጠብታ የጠላትነት መሰረት እንደሌለ ታሪክና እውነት ይመሰክሩልናል፡፡) ለማንኛውም የቃሊቲዎቹ ሐኪሞች ስቃዬ ሊሰማቸው አልቻለም፤ ወይም አልፈለጉም፡፡ ከቶ ለምን ይሆን?
ይህን አስደማሚ የሰቆቃ ድራማ ከጀርባ ሆኖ እየመራ ያለው ባለ እጀ ረጅሙ ማን ይሆን? ለመሆኑስ አማራጭ በሌላቸው ታማሚዎች ጤንነት መነገድ ስንት ያተርፋል? ምን ይሉት ርካታስ ያጐናፅፋል? ከእኛ ስር የበቀለው የነገይቱ ኢትዮጵያችን ተረካቢ ትውልድስ ይህን አስፀያፊ ድርጊት እንዴት ይመለከተዋል ትላላችሁ? ሁላችንንም ቸርና ፍፁም የሆነው እግዚአብሔር ይርዳን፡፡
በተለይ እኔ ባለሁበት የእስርና የጤንነት ሁኔታ ላይ የሚገለፅ ሀሳብ ስሜታዊነት ሊንፀባረቅበት ቢችል ትረዱኛላችሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ሌሎችን ለመውቀስም፣ የጥላቻ ስሜትንም ለመግለፅ ተደርጎ እንዳይወሰድብኝም በትህትና እጠይቃለሁ፡፡ ክብርና ፍቅር የሚገባችሁ ውድ ኢትዮጵያዊያን በግሌ የእስር ቆይታዬ በነፍሴ ውስጥ እንደ ውቅያኖስ የጠለቀ ፍቅርና የእናንተን አጋርነት በማይነጥፍ አሳቢነት አገኘሁበት እንጂ ጥላቻን አልተማርኩበትም፡፡
እኛ ኢትዮጵያዊያን ነን፡፡ የታሪክ፣ የእምነት፣ የወግና የባሕል በአጠቃላይም የማንነት ፅኑ መሰረት አለን፡፡ ትናንት የመጣን ነገ የምንሔድ አይደለንም፡፡ እንኖራለን፤ ቢያንስ ትውልድ ይኖራል፡፡ ታዲያ እንዴት ህክምና በመንፈግ፣ ከቤተሰብ አርቆ በማሰር (የሁለትዮሽ እንግልት ለመፍጠር በማሰብ) ይህን ማንነት እንጣው? አይሆንም!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ፡፡
አክባሪ ወንድማችሁ ውብሸት ታዬ /ከቃሊቲ እስር ቤት/፤

No comments: