Monday, February 3, 2014

በርካታ የአዲስ አበባ ቤት ተመዝጋቢዎች ገንዘባቸውን ከባንክ እያወጡ ነው

Feb.3/2014

ጥር ፳፮ (ሃያ ስድት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከውስጥ አዋቂ ምንጮች ለማዎቅ እንደተቻለው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚታየውን የመኖሪያ ቤቶች ችግር በዘላቂነት ለማቃለል በሚል ከዚህ በፊት ከነበረው የ 20/80 የጋራ መኖሪያ ቤት ልማት ፕሮግራም በተጨማሪ በአማራጭ የ 10/90 አነስተኛ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች እና ለመለስተኛና መካከለኛ ገቢ ላላቸው በ40/60 የቁጠባ ቤት ፕሮግራም መቅረጹን ተከትሎ እስከ አንድ ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ ተመዝግቦ ነበር።

ይሁን እንጅ በአሁኑ ወቅት እጅግ በርካታ ቁጥር ያላቸው የተለያዩ የቤት ልማት ፕሮግራም ተሳታፊ ዜጎች ከፕሮግራሙ እየወጡ መሆኑ ታውቋል። ይህን ዜና እስካጠናከርንበት ጊዜ ድረስ ከ30 ሺ በላይ የሚሆኑ ነዋሪዎች ገንዘባቸውን ከባንክ አውጥተዋል።

ባንክ ቤቶች ከዚህ በፊት ለምዝገባ ስራ ሲጨናነቁ ከነበረው ባልተናነሰ በአሁኑ ጊዜ በከፍተኛ የስራ ጫና ውስጥ እንዳሉና ለዚህ አገልግሎት ብቻ አንድ መስኮት ለመልቀቅ እንደተገደዱ የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

የ20 /80፣ የ10/90 እና የ40/60 ቤቶችን ለመገንባት ከገንዘብ እጥረት በተጨማሪ የቦታ እጥረት ማጋጠሙን ኢሳት የውስጥ መረጃዎችን በማሰባሰብ መዘገቡ ይታወሳል። በተለይም የኦሮሚያ ክልል በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ከተሞችን በአዲስ አበባ ታላቁ ካርታ ውስጥ ለማስገባት ፈቃደኛ ሆኖ ባለመገኘቱ የፕሮጀክቱ ተፈጻሚነት አደጋ ውስጥ ወድቋል።
መንግስት ወደ 10 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገንዘብ ከባንክ በመበደር ቤቶችን ለመስራት ቢያስብም፣ ንግድ ባንክ በርካታ የብድር አገልግሎቶችን በመሰረዝ ለማግኘት የቻለው 6 ቢሊዮን ብር ነው። መንግስት በተለይ 40 በ60ን ተግባራዊ ለማድረግ ያወጣው እቅድ ቅጅው ለኢሳት ደርሶአል። በዚህ እስካሁን ይፋ ባልተደረገው እቅድ የቤቶች ዋጋ ቀድሞ ከተያዘለት በእጥፍ ጨምሮ በግል ከሚሰሩ ቤቶችም ጋር ሲነጻጸር እጅግ ውድ ሆኖ ተግኝቷል።

No comments: