Monday, February 10, 2014

አዲስ አበባ እና ጅማ ሌሊቱን በግድግዳ መፈክሮች ደምቀው አደሩ

February 10/2014

ድምጻችን ይሰማ/ሰኞ የካቲት 3/2006

በትናንትናው ሌሊት በተለያዩ የአዲስ አበባ አካባቢዎች እና በጂማ ከተማ በርካታ የግድግዳ ላይ መፈክሮች ተጽፈው ማደራቸው ተዘገበ! በጂማ በራሪ ወረቀትም ተበትኗል!!!

በአዲስ አበባ ወደአስኮ በሚወስደው መንገድ በጀኔራል ዊንጌትና አካባቢው፣ እንዲሁም በጦር ሀይሎች መስመር እስከ ቤተል ድረስ ባሉ ቦታዎች በግድግዳዎች ላይ ተጽፈው ያደሩት እኒሁ መፈክሮች የሰላማዊ ትግሉን መንፈስ የሚያንጸባርቁና የህዝበ ሙስሊሙ መብት እንዲከበር፣ ታሳሪዎችም እንዲፈቱ የሚጠይቁ ነበሩ፡፡ ከተጻፉት መፈክሮች መካከል ‹‹ድምጻችን ይሰማ! ኮሚቴው ይፈታ! ህገ መንግስቱ ይከበር! የታሰሩት ይፈቱ!›› የሚሉት ጎልተው የወጡ መሆኑም ታውቋል፡፡

በተመሳሳይ ሁኔታ በጂማ ከተማም በግድግዳዎች ላይ በርካታ መፈክሮች ተጽፈው ማደራቸው የተዘገበ ሲሆን በከተማዋ ሌሊቱን እጅግ በርካታ በራሪ ወረቀት ተበትኖ ማደሩና የከተማዋ አስተዳደርም በሁኔታው መደናገጡን ማወቅ ተችሏል፡፡

ካሁን ቀደምም በተለያዩ ጊዜዎች ብሶቱን በግድግዳ ላይ ጽሁፎች (ግራፊቲ) ሲገልጽ የቆየው የኢትዮጵያ ህዝበ ሙስሊም ከሁለት አመታት በላይ በሰላማዊ መንገድ ሲታገል የቆየ ሲሆን የተለያዩ የሰላማዊ ትግል ዘዴዎችን በመጠቀምም ለመብቱ መከበር የሚያደርገውን ጥረት ቀጥሏል፡፡


No comments: