Monday, February 10, 2014

የአየር ኃይል አባሉ ም/መቶ አለቃ ዳንኤል የሽዋስ ሥርዓቱን ከድቶ አርበኞች ግንባርን ተቀላቀለ

February 10/2014

የደብረዘይት አየር ኃይል አባል የነበረው ምክትል መቶ አለቃ ዳንኤል የሽዋስ ሥርዓቱን በመቃወም የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊትን መቀላቀሉን አርበኛ ኑርጀባ ለዘ-ሐበሻ በላከው ዜና አስታወቀ።


                                                   (የአርበኞች ግንባር ሠራዊት – ፎቶ ከፋይል)

እንደ አርበኛ ኑርጀባ ዘገባ አምባገነኑ የወያኔ ቡድን የታጠቀ ኃይሉን መከታ በማድረግ ንጹሃን ዜጎችን ያለ አግባብ እየጨፈጨፈ የስልጣን ዕድሜውን ለማስቀጠል የሚያደረገውን እንቅስቃሴና በሰራዊቱ ውስጥ የነገሰውን የአንድ ቡድን የበላይነት በመቃወም የደብረዘይት አየር ኃይል አባል የነበረውና L-39 ስኳድሮን ተዋጊ ጀት አብራሪ የነበረው ም/መ/አለቃ ዳንኤል የሽዋስ አገዛዙ የሚያደርስበትን ጭቆናና እንግልት ይበቃል በማለት ወደ ኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ተቀላቅሏል።

“የደብረዘይት አየር ኃይል አባልና L-39 ስኳድሮን ተዋጊ ጀት አብራሪ የነበረው ም/መ/አ ዳንኤል የሽዋስ ተቃዋሚዎችን ትደግፋለህ ከእነሱም ጋር የጠበቀ ግኑኝነት አለህ በሚል ምክንያት ተጠርጥሮ ያለምንም ወንጀል ለአምስት ወር ያህል ታስሮ እንደነበርና ከእስር እንደተለቀቀም በወያኔ የደህንነት አባሎች አማካኝነት በአይነ ቁራኛ ክትትል ይደረግበት እንደነበርም” ማስታወቁን የገለጸው የአርበኛ ኑርጀባ ዘገባ “በም/መ/አ ዳንኤል የሽዋስ የወያኔው የደህንነት አባሎች ጥላቻና ጥርጥር ምክንያት እንደገና ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑን ደርሰንበታል በማለት ወደ እስር ቤት እንዳስገቡትና ለ23 ቀናት በደብረዘይት እስር ቤት ከቆየ በኋላ ከእስር ቤት አምልጦ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊትን መቀላቀሉን ገልጿል” ብሏል።

በሌላ ዜና በሁመራ አካባቢ የሚኖሩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ደጋፊዎች ናችሁ በማለት ታስረው የነበሩ 10 ሰዎች ላይ ከ6 ዓመት እስከ 25 ዓመት በመፍረድ ወደ መቀሌና ሽሬ እስር ቤት እንደወሰዱዋቸው ታውቋል።

በመቀሌ እስር ቤት በኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ደጋፊነትና በተለያየ የአሸባሪነት ሰበብ እየፈጠረ የሚያስረው የወያኔው አገዛዝ በመቀሌ እስር ቤት ብቻ 36,900 እስረኛ የሚገኝ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ 4500 የሚሆኑት ሴቶች እንደሆኑ ታውቋል።

በዚሁ እስር ቤት ሰዎችን በሌሊት እየቀሰቀሱ በመውሰድ ደብድበው የሚመልሱ ሲሆን፣ አንዳንዶች ደግሞ በዚያው እንደወጡ እንደሚቀሩ ከአካባቢው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።

የወያኔ ካድሬዎችም በዚሁ በመቀሌ እስር ቤት ውስጥ በሚገኙ ሴቶች ላይ የወሲብ ጥቃት እንደሚፈጽሙባቸው መታወቁን የዘገበው አርበኛ ኑርጀባ፣ በዚህም ምክንያት ሁለት ሴቶች መፀነሳቸውና አስፈላጊውን እንክብካቤ ባለማግኘታቸው ሕይወታቸው እንዳለፈ ከስፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል ብሏል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዳንሻ አካባቢ በኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ስም በሕዝቡ ላይ እያደረሰ ያለው እንግልት ተጠናክሮ ቀጥሏል።
የወያኔው ገዥ ቡድን በዚሁ አካባቢ እየደረሰበት ባለው ወታደራዊ ጥቃት ሳቢያ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር እንደ ምሽግ የሚጠቀመው እናንተን ነው በማለት የአካባቢውን ህብረተሰብ ያሰቃይ እንደነበር ይታወሳል።

በአሁኑ ወቅት ብዛት ያላቸው የዳንሻና የአካባቢው ነዋሪዎችን እያሰረ ሲሆን፣ የሚሰጠው ምክንያት ደግሞ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ያስታጠቃችሁን መሣሪያ አምጡ፣ ከእነሱ ጋርም ቀጥተኛ ግኑኝነት እንዳላችሁም ደርሰንበታል በሚል ወደ እስር ቤት እያጎራቸው ይገኛል ሲል አርበኛ ኑርጀባ ለዘ-ሐበሻ የላከውን ዜና አጠናቋል።

 ዘ-ሐበሻ 

No comments: