Wednesday, October 22, 2014

የፓርቲዎች ትብብር ስምምነቱን ላልፈረሙት ጥሪ አቀረበ

October 22,2014
• ኢትዮጵያውያንም የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል
ዘጠኝ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች ትናንት ጥቅምት 11 ቀን 2007 ዓ.ም በጋራ ለመስራት የትብብር ስምምነት መፈረማቸውን በማስመልከት ዛሬ ጥቅምት 12/2007 ዓ.ም በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ትብብሩን የፈረሙት ፓርቲዎች ትብብሩን ያልፈረሙት ሌሎች ፓርቲዎች ስምምነቱን እንዲፈርሙ በይፋ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ፓርቲዎቹ በመግለጫቸው፣ ‹‹በሂደቱ ከጅምሩ እስከ መጨረሻው ተሳትፋችሁ በተለያየ ምክንያት በትናንትናው ቀን የስምምነቱን ሰነድ ያልፈረማችሁም ሆነ የአገርና ህዝብን ጉዳይ ከፓርቲ ጥቅምና ዓላማ አብልጣችሁ የምትመለከቱና ለዚህም በጋራ ለመስራት ዝግጅቱና ቁርጠኝነቱ ያላችሁ ሌሎች ሰላማዊ የተቃውሞ ፖለቲካ ፓርቲዎች ከጋራ ትግሉ እንድትቀላቀሉ ጥሪያችንን እናቀርባለን›› በማለት ፈራሚዎቹ ፓርቲዎች ይፋዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ የተገኙት የትብብሩ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነትና ዋና ጸሐፊው አቶ ግርማ በቀለ እንደገለጹት ትብብሩ ያለፉትን ድክመቶች የፈተሸና ወደፊት እንዴት እንጓዝ የሚለውን አቅጣጫ ያስቀመጠ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

ፓርቲዎቹ ለትብብሩ መነሻ የሆናቸውን ምክንያት ሲያብራሩም፣ ‹‹በገዢው ፓርቲ/መንግስት የሚፈጸሙ ኢ-ህገ-መንግስታዊ እና ኢ-ዴሞክራሲያዊ ተግባራት በአገራችን የመድብለ ስርዓትን እውን ለማድረግ ከማያስችሉበት ደረጃ በመድረሱ የተፈጠረውን ምስቅልቀስል ለመሸከምም ሆነ ተመጣጣኝ መፍትሄ መስጠት በማስፈለጉ መሆኑ ነው›› ብለዋል፡፡

በመሆኑም ዘጠኙ ትብብሩን የፈረሙ ፓርቲዎች የትብብር ስምምነት ያስፈለገበት ምክንያት፣ ‹‹ነጻ፣ አሳታፊና ታአማኒ ምርጫ እንዲካሄድ በትብብር ለመስራት፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋትና የዜጎችን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ በጋራ ለመታገል›› መሆኑን አመልክተዋል፡፡

የትብብሩ ፈራሚ ፓርቲዎች ሰማያዊ ፓርቲ፣ መኢዴፓ፣ መዐህድ፣ መኢአድ፣ ሶጎህዲድ፣ ኢብአፓ፣ ኦህዲህ፣ ከህኮ እና ጌህዴድ መሆናቸው ታውቅል፡፡

በተመሳሳይ ‹‹ከዓላማችን ለሚያደርሱን ተግባራት ተፈጻሚነት በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ተሳትፎ አስተዋጽኦ ያለው ድርሻ ከፍተኛ ስለሆነ ከጎናችን በመቆምና በንቃት በመሳተፍ የዜግነት ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ›› ሲሉ ለህዝቡ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡
 (9 photos)

No comments: