Wednesday, August 7, 2013

ሰላማዊ የመብት ጥያቄ በሠለጠነ ውይይት እንጂ በአፈናና ግድያ መቼም ቢሆን አይፈታም!

የኢትዮጵያ ህዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ
ኅምሌ 27 ቀን 2005 ዓ/ም

22 ዓመት ሙሉ ነፍጡን ከፊት አስቀድሞ የተፈጥሮ፣ ዴሞከራሲያዊና ሕጋዊ የሆኑ መብቶቹን ለማሰከበር በግምባር ሲታገል የቆየውን ምስኪን ህዝብ በገፍ እያሠረ፤ ኢሰብዓዊ በሆነ መንገድ እያሠቃየውና ግፍ በተሞላበት ግድያም እየቀጣው የቆየው የህወሓት/ኢሕአዴግ ግፈኛ አገዛዝ፣ ይኸው ዛሬም በሰላማዊው ሕዝብ ላይ ባፈናና ግድያው ቀጥሎበት ይገኛል።

 ሐምሌ 25 ቀን 2005 ዓ/ም በምዕራብ አሩሲና በሻሸመኔ አካባቢ ኢማሞቻችን/መሪዎቻችን ይፈቱ እያሉ በሰላማዊ መንገድ ድምጻቸውን ባሰሙ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ላይ የግፍ ግድያ መፈጸሙን ሽንጎው የተገነዘበው በከፍተኛ ሃዘን ነው። ልጆቻችሁ፣ አባቶቻችሁ፤ እናቶቻችሁ፣ እህቶቻችሁና ወንድሞቻችሁ ለህወሓት/ኢሕአዴግ ጥይት ሰለባ ለሆኑባችሁ ወገኖች ሁሉ ጽናቱንና ቁርጠኝነቱን ይስጣችሁ እያልን፤ ዛሬም እንደትናንቱ የታፈነ ድምጻችሁን በማስተጋባትና ጥያቄያችሁም ፍትሃዊ ምላሸ እንዲያገኝ ከጎናችሁ በመቆም ለመታገል ቃል እንገባላችሁዋለን።

የህወሓት/ኢሕአዴግን ማንቁርት ይዞና ሥልጣኑን ጠቅልሎ በመያዝ ከፋፋይ የፖለቲካ መርዙን ሲረጭ የኖረው አምባገነን መሪያቸው የዛሬ ዓመት ገደማ ሲሞት ምናልባት የፖለቲካ ምህዳሩ በመጠኑም ቢሆን ተከፍቶና ተለሳልሶ ቢያንስ አፈናና ጭፍጭፋ ይቆምና የፖለቲካ እሥረኞችም ይፈቱ ይሆናል የሚል እጅግ አናሳም ቢሆን ግምት ተንጸባርቆ ነበር። ባመቱ የመሠከርነው ዕውነታ ግን ያው የተለመደው አፈናና ግድያ በማናለብኝነት መቀጠሉን ነው። ከዚህ ካሁኑ ግድያ አንድ ቀን አስቀድሞ ባዲሱ የፖሊስ ኮሚሸነር ትዕዛዝ ባገር ውስጥ የዜና ማሠራጫ ተነገረ እንደተባለው ማስጠንቀቂያ ከሆነ፤ ደም አፍስሰው ያልጠገቡትና ወሳኝ ሚና እየተጫወቱ ያሉ መሪዎች የግፍ ዱላቸውን በሌሎችም አካባቢዎች ሊቀጥሉበት የወሰኑ ይመስላል።

ከዘመን ብዛትና ከኢትዮጰያ ህዝብ ቁርጠኝነት እነዚህ የዘመናችን ገዢዎቹ የተማሩትና ሊማሩም ያሰቡት ነገር ምን ይሆን እያልንና ሥልጣኔ በጎደለው ድርጊታቸው እየተደመምን፤ ሕዝባችን ግን በገዥዎች ትንኮሳ ሳይረበሽ ባጠመዱለትም ወጥመድ ሳይጠለፍ የጀመረውንም እልህ አሰጨራሽ እና የሰለጠነ ትግል አጠናክሮ እንዲገፋ አደራ እያልን፤ እኛም ከጎኑ ቆመን ከመታገል ወደሁዋላ እንደማንል ቃል እንገባለን።

ሁሉም ኢትዮጵያውያንም ይህን የህወሓትን/ኢሕአዴግን ኋላቀር አረመኔአዊ ጭፍጨፋ አጥበቀው እንዲያወግዙና የመብት ጥያቄን ከሚያነሱ ሁሉ ጎን በመሰለፍ ገዳዮች ለፍርድ እንዲቀርቡ፤ የዕምነት ነጻነት እንዲከበር፣ እንዲሁም የታሰሩት እንዲፈቱ ትግሉን እንዲያጠናሩ ጥሪአችንን እናቀርባልን።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ

No comments: