Saturday, August 3, 2013

የአንድነት ፓርቲ አባላት ከአጉራ-ዘለል የወያኔ ካድሬዎች ጋር ግብግብ ይዘዋል

August 3, 2013
 
አንድነት ፓርቲ እሁድ ሐምሌ 28፣ 2005 “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ መፈክር ስር በተለያዩ የክልል ከተሞች የሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ አባላቱ ቅስቀሳ በማድረግ ላይ ናቸው። ይሁንና ከወያኔ አጉራ-ዘለል ካድሬዎችና ታጣቂዎች እየደረሰባቸው ያለው ወከባ ተባብሶ ቀጥሏል። ነብዩ ሀይሉ እና ሌሎችም በፌስ-ቡክ ገጾቻቸው ሁኔታውን እንደሚከተለው ይገልጹታል፣

UDJ calling for protest in Bahirdar
በባህርዳር የአድነት ፓርቲ አባላት በቅስቀሳ ላይ። ፎቶ Bisrat Woldemichael
 
በወላይታ የተሸጠ ጀነሬተር እንዲመለስ ተደረገ

በወላይታ ሶዶ ዙሪያ ወረዳ አዳራሽ(አዳራሹ ከ200 ሰው በላይ የመያዝ አቅም የለውም) አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ለሚያከናውነው ስብሰባ ህዝቡን ለመቀስቀስ ሞንታርቦና ጀነሬተር የሚያከራይ ነጋዴ በመጥፋቱ(በከተማው ጀነሬተር በማከራየት ህይወታቸውን የሚገፉ ነጋዴዎች በብዛት የሚገኙ ቢሆንም ካድሬዎች ቀጠን ያለ ትዕዛዝ በማስተላለፋቸው መከራየት አልተቻለም)የጄነሬተር መጥፋት ያሳሰባት ወ/ሮ ጸሀይ ወ/ጊዮርጊስ አነስተኛ ጀነሬተር በ2300ብር ትገዛለች፡፡
ሻጩ ጀነሬተሩን በህጋዊ መንገድ ከሸጠና መኪናው ላይ እንዲጫን ከተደረገ በኋላ ግለሰቡ እንባውን እያዝረከረከ የተከፈለውን ገንዘብ በመያዝ ጀነሬተሬን መልሱልኝ በስህተት ነው የሸጥኩላችሁ››ይላል ፡፡ነጋዴው ለምን እንደዚህ እንደህጻን እያለቀሰ መልሱልኝ ማለቱን የተረዱ የፓርቲው አባሎችም ጀነሬቱን መልሰውለታል፡፡
—————————
መቀሌ፣ የአንድነት አመራሮች ከነ መቀስቀሻ ሞንታረቮአቸው በቀዳማይ ወያኔ ፖሊስ ጣቢያ ታሰሩ

የአንድነት ፓርቲ አመራር የሆኑት አቶ አርአያ፣ የአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራር የሆኑት አቶ እንግዳ ወ/ፃዲቅ እና የአንድነት ፓርቲ የትግራይ ዞን ፀሀፊ አቶ ክብሮም ብርሀነ በመቀሌ ከነ መቀስቀሺያ ሞንታረቮአቸው ቀዳማይ ወያነ ክፍለከተማ ፖሊስ ጣቢያ ታስሩ፡፡ አቶ እንግዳ ወ/ፃዲቅ እና አቶ ክብሮም ብርሀነ ለሁለተኛ ጊዜ እንደታሰሩ ልብ በሉ!!! የመቀሌ ነዋሪዎች አመራሮቹን ለማስፈታት ከፖሊስ ጋር እየተከራከሩ ነው፡፡‪
—————————-
ባህርዳር፣ አንድነት ፓርቲ በባህር ዳር ነገ ሐምሌ 28 ለሚደረገው ሰላማዊ ሰልፍ የተጠናከረ ቅስቀሳ እየተደረገ ነው

የባህር ዳር እና የአካባቢዋ ነዋሪዎችም በተቃውሞው ሰልፉ ላይ በንቃት ለመሳተፍ መዘጋጀታቸውን ለፍኖተ ነፃነት ዘጋቢዎች ተናግረዋል፡፡
ኢህአዴግም የባህር ዳር ህዝብ ባሳየው ንቁ ተሳትፎ በመደናገጡ በተለያዩ ቤተ ክርስትያኖች ቅዳሴ ዘግይቶ እንዲጀምር ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡ ቀበሌዎችም የተለያዩ ስብሰባዎችን አስጠርቷል፡፡ ባህር ዳሮችም ነገ ሰላማዊ ሰልፉን ለማድመቅ የተለያዩ መፈክሮችን በየቤታቸው በማዘጋጀት ላይ ናቸው፡፡
—————————-
አርባምንጭ፣ በአንድነት ፓርቲ በሁለት መኪናዎች አርባምንጭን በቅስቀሳ አድምቋታል፡

በራሪ ወረቀቶች እየተበተኑ ነው ፖስተሮችም በብዛት እየተለጠፉ ነው፡፡ የኢህአዴግ ካድሬዎች “ሰልፉ ላይ እንዳትወጡ” የሚል ቅስቀሳ ቢያደርጉም የአርባምንጭ ነዋሪዎች በሰልፍ ላይ ለመገኘት መወሰናቸውን እየተናገሩ ነው፡፡
—————————-
ጅንካ፣ ከትናንት ጀምሮ ከፍተኛ ቅስቀሳ እየተደረገ ነው

ከአጎራባች አካባቢዎች በሰልፉ ላይ የሚሳተፉ ዜጎች ወደ ጅንካ እየገቡ ነው፡፡ ከትላንት ጀምሮ ፖስተሮች እንዳይቀደዱ የአካባቢው ህዝብ እየጠበቀ ነው፡፡ በኢህአዴግ ካድሬዎች በ 1 ለ 5 መዋቅር ሰልፍ አትውጡ በሚል የጀመረው ቅስቀሳ ከሽፏል፡፡

No comments: