Thursday, August 22, 2013

ሰላሳ ሶስቱ ፓርቲዎች -ሰማያዊ ፓርቲን ከፓርቲዎች የትብብር መድረክ አሰናበቱ።

ነሃሴ ፲፮(አስራ ስድስት)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የ33ቱ ፓርቲዎች የትብብር መድረክ -ሰማያዊ ፓርቲን ያሰናበተው፤የፓርቲው ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ሰሞኑን ለ ሰንደቅ ጋዜጣ የሰጡት ቃለምልልስ የሌሎች ፓርቲዎችን ክብር የነፈገ ነው በሚል ነው።

በዚህም መሰረት ፓርቲዎቹ ባደረጉት ስብሰባ ሰማያዊ ፓርቲ ከስብስቡ እንዲወጣ መወሰናቸውን የቪኦኤ ዘገባ ያስረዳል።
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ፀሀፊ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ ውሳኔው የተላለፈው ባለፈው እሁድ በተካሄደ አስቸኳይ ስብሰባ እንደሆነ  ገልጸዋል።

አቶ ይልቃል ለሰንደቅ በሰጡት ቃለ ምልልስ በዚህች አገር ከሰማያዊ ፓርቲ ውጪ ሌላ ተቃዋሚ ፓርቲ አለ ብለው እንደማያምኑ መገለፃቸው ይታወሳል።

“ገዥው ፓርቲና ምርጫ ቦርድ የሰጡንን ዕውቅና ሳይቀር አቶ ይልቃል ነስተውናል”ያሉት የመኢአድ ፀሀፊ፤ህዝቡ በፖለቲካ ፓርቲዎች ላይ እምነት እንዳያድርበት ደባ ስለፈጸሙ፤ ድርጊታቸውን እንዲያርም ጊዜ ቢሰጣቸውም ሊያርሙ ስላለረቻሉ፤ ይባስ ብለውም ያንኑ ሃሳባቸውን ፡”የኛ ፕሬስ”በተሰኘ ጋዜጣ ላይ በማንፀባረቃቸው እና አቋሙ የ እርሳቸው ብቻ ሳይሆን የፓርቲያቸው ጭምር እንደሆነ በመረጋገጡ ከስብስቡ እንዲሰናበቱ ወስነናል ብለዋል።

የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ ይልቃል በበኩላቸው “የሰጠሁት አስተያየትና ያንፀባረቅኩት ሃሳብ አዲስ አይደለም፤ እውነትም    ነው”ብለዋል።

እስካሁን ሌሎች ፓርቲዎች የከፈሉትን መስዋዕትነት እርሳቸውና ፓርቲያቸው እንደሚያደንቁ ለቪኦኤ የተናገሩት አቶ ይልቃል፤ይሁንና ተቃዋሚዎች በአሁኑ ጊዜ የህዝብን የለውጥ ጥያቄ ለመመለስ በሚያስችል ጥንካሬና አቋም ላይ አለመሆናቸውን ገልጸዋል።
“እኔ ስህተተኛ ብሆን ደስታዬ ነበር”ያሉት አቶ ይልቃል፤”እነዚህ ፓርቲዎች ነን እንደሚሉት ቢሆኑ እኔና ጓደኞቼ ሰማያዊ ፓርቲን አፍርሰን ወደየሌሎች ፓርቲዎች እንገባለን፤ወይም ወደየቤታችን እንሄዳለን”ብለዋል።

“ግን እውነቱ ሌላ ነው። የኢትዮጵያን ችግር መጋፈጥ አለብን ካልን እውነቱን ማድበስበስ የለብንም” በማለት ቀደም ሲል በሰጡት አስተያዬት እንደሚያምኑ በድጋሚ አረጋግጠዋል።

No comments: