Wednesday, August 14, 2013

ኢህአዴግ ከከፍተኛ አበል ጋር ፀረ አንድነት ፓርቲ ስልጠና አዘጋጀ

August 14, 2013
ፍኖተ ነፃነት

አንድነት ፓርቲ የጀመረውን ህዝባዊ ንቅናቄ ለማስተጓጎል ከፍተኛ አበል በመክፈል ለአባላቱ ስልጠና ማዘጋጀቱን ለኢህአዴግ ቅርበት ያላቸው የፍኖተ ነፃነት ምንጮች ጠቆሙ፡፡

አንድነት ፓርቲ የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት በሚል መሪ ቃል የጀመረው ህዝባዊ ንቅናቄ ህዝባዊ ተቀባይነት ማግኘቱንና በስኬት መቀጠሉን ተከትሎ ኢህአዴግ “አንድነት ፓርቲንና ንቅናቄውን እንዴት ማስቆም ይቻላል” በሚል በከፍተኛ አመራሮቹ ውይይት ካደረገ በኋላ በመላ ሀገሪቱ ፀረ አንድነት ፓርቲ ስልጠና “ጠንካራ” ላላቸው አባላቱ ለመስጠት መዘጋጀቱን የሚገልፁት ምንጮቹ “ለስልጠናው ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ተመድቧል፤ ኢቲቪና የክልል ሬዲዮ ጣቢያዎችና የመንግስት ጋዜጦች አንድነት ፓርቲ የሸሪአ ህግን በኢትዮጵያ ተግባራዊ ለማድረግ ከሚንቀሳቀሱ ሽብርተኞች ጋር እየሰራ ነው የሚል የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ እንዲከፍቱ ጥብቅ መመሪያ ደርሷቸዋል፡፡” በማለት ጨምረው ገልፀዋል፡፡

ምንጮቹ አክለውም “ኢህአዴግ ከየቀበሌው  እየመረጠ ስልጠና የሚሰጣቸው አባላቱ የአንድነት ፓርቲ አመራሮችንና አባላትን በማሸማቀቅ፣በማስፈራራት፣ በቤተሰቦቻቸውና በሃይማኖት አባቶቻቸው በኩልም ከፖለቲካ እንዲወጡ ተፅዕኖ እንዲደርስባቸው የተቻላቸውን እንዲያደርጉ የሚያበቃ ነው” ብለዋል፡፡

የፍኖተ ነፃነት ምንጮች እንዳረጋገጡት የዚሁ ስልጠና አካል የሆነ  ስልጠና ከነገ ጀምሮ በደቡብ ወሎ ዞን ኩታበር ወረዳ ከየቀበሌው ለተውጣጡ ከ200 በላይ ለሚሆኑ የኢህአዴግ አባላት ለሁለት ቀን ይሰጣል፡፡

No comments: