Tuesday, August 27, 2013

ህወሓቶች ‘ሁኔታችን አይታቹ ደግፉን’ ይሉናል

ባለፈው ሳምንት ነው፤ በአንድ የሰሜን አሜሪካ ከተማ። የህወሓት ከፍተኛ ባለስልጣናት በሰሜን አሜሪካ በሚካሄደው የተጋሩ ፌስቲቫል ተገኝተው ድጋፍ ለማሰባሰብ በረሩ። ከትግራይ ተወላጆች ጋር ለመወያየት መድረክ ተከፈተ። ተሳታፊዎቹ ስለ ልማትና መልካም አስተዳደር ችግር፣ ስለ ሐውዜን ጉዳይ፣ በትግራይ ተወላጆች ስለሚደርስ የሰብአዊ መብት ጥሰት ወዘተ አንስተው ይጠይቃሉ። ባለስልጣናቱም ሲመልሱ፣ “እኛ ‘ኮ ብዙ ጠላቶች አሉብን። እኛን ለማጥፋት የሚሯሯጡ ኃይሎች አሉ። እኛ'ኮ 'ትግሬ ወደ መቀሌ ዕቃ ወደ ቀበሌ' የሚሉን ሞታችንን የሚጠባበቁ ኃይሎች ይዘን ነን ያለነው። ይህ ሁኔታችን እያወቃቹ እንዴት እንዲህ ዓይነት ጥያቄ ትጠይቃላቹ? እንዴት ህወሓትን ይህን ያህል ትጠላላቹ? ሁኔታችን ኮ መረዳት አለባቹ።"

ይገርማል። ህወሓቶች ጥያቄ መመለስ ሲያቅታቸው 'ጠላት እየመጣ ነው፣ ህወሓቶች ከሌለን የትግራይ ህዝብ አደጋ ዉስጥ ይወድቃል' ይሉናል። መጀመርያ የትግራይን ህዝብ ጠላት ማነው? ለምንስ ጠላት ሆነ? ጥላቻው ማን ፈጠረው? 'የትግራይ ህዝብ ጠላት አለው' ብለን እንኳ ከተነሳን ማድረግ ያለብን የትግራይን ህዝብ ማፈን አይመስለኝም። ምክንያቱም ህዝብ ማፈን ህዝቡ ደካማ እንዲሆን ማድረግ ነው። ደካማ ከሆነ ደግሞ ለጥቃት ይዳረጋል።

በትግራይ ህዝብ ያንዣበበ አደጋ ካለ መፍትሔው ሌሎች ህዝቦች መበደል ነው? አይመስለኝም። በትግራይ ህዝብ ስም ሌሎች ህዝቦች መበደል ጠላትን ማፍራት ነው። በትክክል ስጋቱ ካለ የትግራይ ህዝብ መብቱ ተከብሮለት አማራጭ የፖለቲካ ድርጅት እንዲኖረው ሊፈቀድለት ይገባል እንጂ ሊታፈንና ሊዳከም አይገባም።

የትግራይን ህዝብ ከጥቃት ማደን የሚችሉ የህወሓት ባለስልጣናት ብቻ ናቸው ያለ ማነው?

No comments: