Thursday, June 20, 2013

ወያኔን ማመን ቀብሮ ነው!

         
የወያኔ ጉጅሌ ፀረ-ህዝብነቱን፤ ዘረኝነቱንና ከኢትዮጵያ ህዝብ ያጣውን ተቀባይነት ለመሸፈን ሀገሪቱን ልማት በልማት አድርጌ ህብስተ-መና አዘንባለሁ ይህንንም ከእኔ ወዲያ የሚያደርግ የለም የሚል ልፈፋ ከጀመረ አመታት ተቆጥረዋል፡፡

በእነዚህ አመታት ውስጥ በህዝባችን ስም በልግስናና በብድር ከአለም አቀፍ ተቋማትና መንግስታት በገፍ የተገኘው ገንዘብ የጉጅሌውን ባለሟሎችና ሎሌዎች የናጠጡ ቱጃሮች እንዲሆኑ ማድረጉንም እናውቃለን። የህዝቡ ኑሮ ግን በየእለቱ እያሽቆለቆለ ኩርማን እንጀራ በልቶ ማደር ብርቅ የሆነበት ደረጃ ላይ ደርሰናል።

 የተስፋ ዳቦ እየቀለበ ሊገዛን የወሰነው ወያኔ፤ ዛሬ ደግሞ አባይን ገድቤ ኤሌክትሪክ ለጎረቤት ሀገሮች ሽጬ ከዚያ በሚገኘው ገቢ ዳቦ አዘንባለሁ፣ እመግባለሁ ይለናል፤ ለዚህ ደግሞ ድህነትና ረሃብ የሚቆላውን ህዝብ ከዝርፊያ ባልተናነሰ መዋጮ ቁም ስቅሉን ማሳየት ከጀመረም ውሎ አድሯል።

ወያኔ የልማትን ፕሮፖጋንዳ እንደ ልማት እንድናይለት ይፈልጋል። በልማት ዙሪያ ስለ ግልጽነትና ተጠያቂነት ስናነብለት አይኑ የሚቀላውና ራሳችንን መልሶ ፀረ-ልማትና አሸባሪ፣ የባዕድ ተባባሪ እያለ የሚያስፈራራን በልማት ስም የሚካሄደውን ዝርፊያና ተንኮል ይጋለጥብኛል በሚል ፍርሃት ስለተያዘ ነው። ወያኔ መቼም ቢሆን የብሄራዊ ጥቅም አጀንዳ የሌለው ሀገራችንን ሲሸጥና ሸንሽኖ ሲያከፋፍል የኖረ ድርጅት ከቶ በድንገት እመኑኝ የሚል የሞራል ብቃት እንዴት ሊኖረው ይችላል?

ወያኔ ከባዶ ኪስ ተነስቶ ጀምሬዋለሁ የሚለን የአባይ ግድብ፣ ከዚህም ጋር ተያይዞ የሚደልቀው የፕሮፖጋንዳ ከበሮ ለስልጣን ላይ ተንጠልጥሎ ለመቆየት እንዲያገለግለዉነዉ እንጂ የሀገርና የህዝብ ጥቅምን ያስቀደመ አለመሆኑን ወያኔንና ባህሪውን አሳምረን የምናውቅ ወገኖች እናውቃለን። ይህንን ግድብ አስመልክቶ ስለግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ገንዘብ አጠቃቀም ስለፕሮጀክቱ አዋጭነትና የቴክኒክ ችግሮች ጥያቄ ያነሳውን ሁሉ ጸረ-ልማት፣ አሸባሪ፣ የባእድ ተባባሪ በማለት የሚያስፈራራውም ለዚህ ነው።

ወያኔ የአባይን ግድብ አስመልክቶ ያሉትን የኢንጅኔሪንግ፣ የቦታና የመጠን አመራረጥ የአካባቢ ጥበቃና እንዲሁም በአለም ዙሪያ በተመሳሳይ ሁኔታ የተሰሩ ግድቦች ያስከተሉትን ችግር አንስተን እንወያይ ተብሎ ሲጠየቅ አሻፈረኝ የሚለዉና ባለሙያዎችና አዋቂዎች የተሻለ አማራጭ ሲያቀርቡ አይቶ እንዳላየ የሚያልፈዉ ወያኔ፣ ፕሮጀክቱ የፖለቲካ እንጂ የልማት አለመሆኑን ልቡ ስለሚያውቅ ነው። ልማት የሚጠላ ህዝብም ይሁን ተቃዋሚ ሃይል በሌለበት ሀገር ለመሆኑ ወያኔ ከራሱ ጆሮ ውጭ ስለልማት እንዳንወያይ የሚከለክለው ለምንድን ነው? መልሱ ግልጽ ነው፤ የወያኔ ልማት መብለጭለጩ እንጂ ጥቅሙ አይደለም። ቁም ነገሩ የወያኔ ልማት ለሰው አይደለም። ሰዉ ሰውም አይሸትም፤ በስልጣን የመቆየት የልማታዊ ስልት ቁማር እንጂ!

ወያኔ ልማት ሲያቅድ ምን ያህል ስልጣን ላይ ያቆየኛል ብሎ ነዉ እንጂ፣ ስንቱን ህብረተሰብ ይጠቅማል፣ ይረዳል ብሎ አይደለም። በአንጻሩ የወያኔ ባለሟሎችና የጦር አለቆች በዘረፋ የሰሩትን ህንጻ የሀገር ልማት ውጤት ነው ብለን እንድናስብ የሚወተውቱንም ለዚህ ነው።

ወያኔ በአባይ ግድብ ዙሪያ በራሱ የውስጥ ችግር ከተተበተበው የግብጽ መንግስት ጋር የገጠመው አተካሮም የሀገር ፍቅር ስሜታችንን በመኮርኮር አይናችንን ከወያኔ ዘረኝነትና የግፍ አገዛዝ ላይ እንድናነሳ ለማድረግና የውስጡን ፖለቲካዊ ችግር ለመፍታት ጊዜ መግዣ የወያኔ ጥበብ መሆኑን ልንረዳ ይገባል።

ግንቦት 7 የፍትህ፣ የነጻነትና የዴሞክራሲ ንቅናቄ፣ ህዝብና ሀገርን ተጠቃሚ የሚያደርግ ልማት ከዴሞክራሲ፣ ከፍትህ መስፈንና ነጻነት ውጭ ሊታሰብ እንደማይችል ያምናል።

 የኢትዮጵያ ህዝብ ነጻነቱን ከብረ – ስብእናውን ከሰማይ ዳቦ አወርዳለሁ ለሚለው የወያኔ ድለላ ላፍታ እንኳን እራሱን በማዘናጋት ከሚደርገው የነጻነት ትግል ጉዞ አቅጣጫ መውጣት የለበትም እንላለን።

ወያኔ በሚደልቀው የአባይን እገድባለሁ ፕሮፖጋንዳ ውስጥ ህዝብ አጥብቆ ሊጠይቃቸው የሚገባ በርካታ የወያኔ ሽፍንፍኖች እንዳሉ አለመገንዘብ ትልቅ የዋህነት ነው።

 ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments: