Monday, June 10, 2013

በአፋር ፌደራል ፖሊሶች ከህዝቡ ጋር ሲታኮሱ ዋሉ

ሰኔ ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በትናንትናው እለት የ20 አመቱ ወጣት የሆነው ሙሀመድ ካይብ የፌደራል ፖሊስ አባላት በቅርበት ባሉበት በኢሳዎች መገደሉን ተከትሎ፣ አፋሮች ገዋኔ ወለጌሊ እየተባለ በሚጠራ ስፍራ ከፌደራል ፖሊስ ጋር ዛሬ ሲታኮሱ ውለዋል። ስቱዲዮ እስከገባንበት ጊዜ ድረስ ተኩሱ አለመቆሙን ለማወቅ ተችሎአል።

ነዋሪዎች በፌደራል ፖሊስ አባላት ላይ ተኩስ የከፈቱት ፣ ፖሊሶቹ ሆን ብለው ሁለቱን ብሄረሰቦች ለማጋጨት እየጣሩ ነው በሚል ምክንያት ነው። ከሳምንት በፊት በዚሁ አካባቢ የሚኖሩ አርብቶ አደሮች መሳሪያቸውን እንዲያስረክቡ በተጠየቁበት ጊዜ ተኩስ በመክፈታቸው ፖሊሶቹ አካባቢውን ለቀው መሄዳቸውንና ግጭቱ መብረዱን መዘገባችን ይታወሳል። ዛሬ የተፈጠረው ግጭት ባለፈው ሳምንት ከተካሄደው ግጭት ጋር እንደሚያያዝ ነዋሪዎች ይናገራሉ።

በግጭቱ ምን ያክል ሰዎች እንደቆሰሉ ወይም እንደሞቱ ለማወቅ አልተቻለም። በጉዳዩ ዙሪያ የአፋር ባለስልጣናትን ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።

No comments: