Saturday, June 22, 2013

ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ስራቸውን እየሰሩ ነው ማለት ነው!

Bucknell University Professor of Economics Berhanu NegaJune 21, 2013
 
ሰሞኑን ከኢህአዴግ ጋር የስጋ ዝምድና አላቸው እየተባሉ የሚጠረጠሩ ወዳጆቻችን ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ከአንዳች ሀይል ኢህአዴግን ለመገዳደሪያ የሚሆን ገንዘብ እንዳገኙ የሚያሰማ ድምፅ አጋርተውናል፡፡ ችግሩ ግን ይህ ገንዘብ ከየት እንደተገኘ እርስ በርሳቸው ስምምነት ላይ አልደረሱም፡፡ አንዳቸው ከኤርትራ ነው ሲሉ ሌላኛው ደግሞ ከግብፅ ነው ይላሉ፡፡ በደንብ ጆሮ ጣል ብናደርግ ከኢህአዴግ መንግስት ነው የሚልም አይጠፋም፡፡

ወዳጆቻችን ያጋሩን ድምፅ ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ከሆነ ቦታ የተገኘውን ብር፤ ለእንትን ይሄን ያህል፣ ለእንትና ይሄን ያህል እያሉ ሲናገሩ ያስደምጣል፡፡ በዚህ ላይ ያስደነቀኝን ልናገር እና እመለሳለሁ ቆይ አዲስ መስመር ላይ እንገናኝ፡፡

ዶክተሩ የሆነውን ብር እዛው ለመከላከያ እና ደህንነቱ የተበጀተ ነው፤ ሲሉ ሰማናቸው፡፡ ይሄኔ በተለይ እንደኔ በኢህአዴግዬ ፍቅር የተለከፈ ሰው ክው!!! ማለቱ አይቀርም፡፡ ደህነነት እና መከላከያችን ከመንግስት ከሚመደብለት በጀት ውጪ በግንቦት 7 ደግሞ ሌላ በጀት አለው ማለት ነው፡፡ ይቺን ነው መፍራት፤ ዶክተሩ ስራቸውን ቀጥ ለጥ አድርገው እየሰሩ ነው ማለት ነው፡፡

ታድያ ለዚህ ነዋ የኢህአዴግዬ ገመናዋ ሁሉ ቀድሞ አደባባይ የሚሰጣው!!! እኔ ልሰጣ … ልበል ወይስ አልበል! (በቅንፍም ይቅርብኝ እነ እንትና ሳይሉ እኔ ቀድሜ ልሰጣ… ብል እነሱን ማሳጣት ሆንብኛል!) ከቅንፍ ስንወጣም ለኢሳትም የሆነ ብር ይሰጣል ሲሉ ዶክተሩ መናገራቸውን አዳመጥኩ፡፡ በእውነት ዶክተርዬ የተባረኩ ኖት፡፡ … እንዴ… በአሁኑ ጊዜ ማን እንደዚህ ያደርጋል… የምር እኮ ኢሳትን ሁሉም መርዳት አለበት፡፡ ግንቦት 7 ከረዳው በጣም ጥሩ ጅምር ነው፡፡ እንኳን ሌላ ቀርቶ ግንቦት 20 ም ራሷ ኢሳትን መርዳት አለባት፡፡ እንዴ ኢቲቪ የማይሰራውን በሙሉ የሚሰራው ኢሳት አይደለ እንዴ…! ታድያ እንዲህ እንዲተጋገዙ ሁሉም የአቅሙን ቢያዋጣ ምን ችግር አለበት!

ወደ ዋናው መስመር ስመለስ ወዳጆቻችን “ፈልፍለው” ይፋ ባደረጉት መረጃ ዶክተሩ ለካስ አልተኙም ብለናል፡፡ እና ይበርቱ ልንላቸው ይገባል፡፡

ገንዘቡ ከግብጽ ነው፤

ግብፅ የምር ለኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች ገንዘብ የምትረዳ ከሆነ ተጃጅላለች ማለት ነው፡፡ ሌላ ቀርቶ ኢህአዴግ እንኳ ያንን ሁላ አድርጋለት አልተመለሰላትም፡፡ በእውኑ ሌሎቹማ ከኢህአዴግ የበለጠ ለሀገራቸው ተቆርቋሪ አይደሉምን…!
ገንዘቡ ከኤርትራ ነው፤

ወይ…. ኤርትራ….!!! አሁን ማን ይሙት ኤርትራዬ ከራሷ አልፋ ለሌላ ሰው ይሄንን ያክል ብር መስጠት ትችላለች…! ይሄንን ሃሳብ የሰነዘሩ ሰዎች በእርግጠኝነት ኤርትራዊያን ናቸው፡፡ አላማውም የኤርትራም መልካም ገፅታ ለመገንባት ሳይሆን አይቀርም ብለን እኛ ጠርጣሮቹ እንጠረጥራለን!

የትም ፍጪው ኢህአዴግን አስወጪው፤

ዶክተር ብርሃኑ ነጋ ግንቦት 7 የሚባል ተቃዋሚ ፓርቲ መስርተው ሁለገብ በሆነ ዘዴ ኢህአዴግን ወግድ እለዋለሁ ብለውናል፡፡ ግንቦት 7 ይህ ከሆነለት የዘመናት ብሶት የወለዳቸው ሁሉ ተሰባሰበው ዋንጫ እንደበላ ሰው “የእርግብ አሞራ” እያሉ የሚጨፍሩለት ደስታ የሚሆን ይመስለኛል፡፡ ታድያ ለዚህ አላማ ገንዘብ ከየትስ ቢያመጡ እኛ ምን አገባን…!?

ከአቤ ቶክቻው የፌስቡክ ገጽ የተወሰደ

No comments: