Tuesday, December 2, 2014

ከ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር የተሰጠ ዕለታዊ መግለጫ

December 2,2014
ዝግጅታችን ተጠናክሮ ቀጥሏል! እርስዎም ይዘጋጁ!


‹‹ነጻነት ለፍትሓዊ ምርጫ›› በሚል የአንድ ወር መርሃ ግብር ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ ስርዓቱ መርሃግብሮቻችን በማጨናገፍ ለነጻነት የምናደርገውን የትግል ጉዞ ለማደናቀፍ ሌት ተቀን እየሰራ ይገኛል፡፡ ሆኖም የነጻነት ትግሉ ከፍተኛ መስዋዕትነት የሚያስከፍል መሆኑን የተረዳው ትብብሩ ለገዥው ፓርቲ አፈና ሳይንበረከክ ስራውን ቀጥሏል፡፡ በተለይ ከመርሃ ግብሮቻችን መካከል ስርዓቱን ያስፈራውን የ24 ሰዓት የአደር ሰልፍ ለማድረግ ዝግጅታችን አጠናክረን ቀጥለናል፡፡ ለዚህ የአዳር ሰልፍ የትብብሩ አባል ፓርቲዎች ሰው በሰው በመቀስቀስ፣ ወረቀት በመበተን እንዲሁም በየ ፓርቲዎቻችን ስም የታተሙ ቲሸርቶችን በመልበስ ህዝቡን እያነቃቃን እንገኛለን፡፡ ሰልፉ እስከሚደረግበት ህዳር 27/28 2007 ዓ.ም ድረስም ዝግጅታችን አጠናክረን እንቀጥላለን፡፡

ይህን መርሃ ግብር ስንነድፍ ለነጻነት የሚከፈለው መስዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጅተንና የቀድሞ አባቶቻችን ካሳዩት ቆራጥነት ተምረን ነው፡፡ በዚህ ለቀጣይ የትግል ጉዞአችን ጭላንጭል ለምናይበት መርሃ ግብር የኢትዮጵያ ህዝብ ከጎናችን እንዲቆም ጥሪ እናደርጋለን፡፡ በውጭም ሆነ አገር ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለነጻነት ለምናደርገው ጉዞ የጀመርነውን የሰው በሰው ቅስቀሳ በመደገፍ፣ በገንዘብ፣ በሞራልና በሌሎች ለመርሃ ግብሩና ለአጠቃላይ ትግሉ ይጠቅማል ባሉት መንገድ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ እናቀርባለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ መርሃ ግብሩ ከጀመረ ጊዜ አንስቶ በሞራልና በተለያየ መንገድ መልዕክቶቻችን ለህዝብ እንዲደርሱ ድጋፍ ያደረጋችሁልን በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ልባዊ ምስጋናችን ማቅረብ እንፈልጋለን፡፡ አሁንም ድጋፋችሁን አጠናክራችሁ በመቀጠል ታሪካዊ ግዴታችሁን እንድትወጡ እንጠይቃለን፡፡

በ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር በኩል ለሰላማዊ ሰልፉ የሚያስፈልገው ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል፡፡ በመሆኑም ህዝቡ በዝግጅቱ ከሚያደርገው ድጋፍ ባሻገር በመስቀል አደባባይ በሚኖረን ቆይታ የሚያስልጉት ቁሳቁሶች በተለይም ደረቅ ምግብና ውሃ ከአሁኑ እንዲያዘጋጅ ማስታወስ እንፈልጋለን፡፡ ህዳር 27/28 2007 ዓ.ም በመስቀል አደባባይ የሚደረገው የ24 (አዳር) ሰልፍ ኢትዮጵያውያን ላይ የተጫነውን የፍርሃት ድባብ በመስበር ለነጻነት የምናደርገው ወሳኝ ጉዞ ጅማሬ በመሆኑ በሁሉም የማህረሰብ ክፍል የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ንቁ ተሳትፎ በማድረግ ራሳቸውንና አገራቸውን ነጻ ለማውጣት የትግሉ አካል እንዲሆኑ ጥሪያችን እያቀርባለን፡፡

ያለ መስዋዕትነት ድል የለም!

ህዳር 23/2007 ዓ.ም

አዲስ አበባ

No comments: