Monday, December 8, 2014

እነ ፍቅረማሪያም የሽንት ቤትና ሌሎች ቆሻሻዎች የሚፈስበት ጋራዥ ውስጥ ታስረዋል

December 8,2014
እነ ወይንሸት ንጉሴ 7 ቀን ተቀጠረባቸው
በሰላማዊ ሰልፍ ዝግጅት ወቅት ታፍና ቤላ 18 ተብሎ በሚጠራው ፖሊስ ጣቢያ ታስራ የምትገኘው ወይንሸት ንጉሴና ሌሎች 6 ወጣቶች ሾላ አካባቢ በሚገኘው ፍርድ ቤት ቀርበው 7 ቀን ተቀጠረባቸው፡፡ ወይንሸት ‹‹ባልፈተቀደ ሰላማዊ ሰልፍ በመሳተፍና ሁከት መፍጠር›› የሚል ክስ የቀረበባት ሲሆን እሷ በበኩሏ ሰልፍ ማሳወቅ እንጅ ማስፈቀድ እንደማያስፈልግ በመጥቀስ የዋስትና መብቷ ተረጋግጦላት እንድትፈታ ጠይቃለች፡፡
‹‹የያዝናቸው በቅርብ ቀን ነው፣ ያልተያዙ ግብረ አበሮቻቸው አሉ፣ መረጃም እናሰባስባለን›› ያለው ፖሊስ 14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ተጠይቆ 7 ቀን ተሰጥቶለታል፡፡
በሌላ በኩል ኮተቤ አካባቢ የታሰሩት እነ ፍቅረማሪያም አስማማው፣ ተስፋሁን አለምነህ፣ ሺፈራው ዋለና ሌሎች 8 ታሳሪዎች የሽንት ቤት ፍሳሽ በሚልፍበት ጋራጅ ቤት ውስጥ መታሰራቸውን ገልጸዋል፡፡ እነ ፍቅረማሪያም የታሰሩት ፖሊስ ከግለሰብ የተከራው ህንጻ ውስጥ ሲሆን የታሰሩበት ጋራዥም ከህንጻዎቹ ላይ የሚገኙት ሽንት ቤቶችና ሌሎች ቆሻሻዎች የሚያልፉበት ነው ተብሏል፡፡ እነ ፍቅረማሪያም ከ2 ቀን በፊት ፍርድ ቤት ቀርበው ‹‹በሽብርተኝነት›› ክስ 10 ቀን እንደተቀጠረባቸው ይታወቃል፡፡

No comments: