Monday, December 8, 2014

እነ ግርማ በቀለና ጌታነህ ባልቻ መስቀል አደባባይ ላይ ንብረት አውድመዋል ተብለው ተከሰሱ

December 8,2014
ለአዳር ሰላማዊ ሰልፉ መስቀል አደባባይ ተይዘው ጨርቆስ ፖፖላሬ ታስረው የሚገኙት የ9ኙ ፓርቲዎች ትብብር ፀኃፊ አቶ ግርማ በቀለ፣ የሰማያዊ ፓርቲ የጥናትና እስትራቴጅ ክፍል ኃላፊ ጌታነህ ባልቻን ጨምሮ 27 ያህል የትብብሩ አመራሮች፣ አባላትና የሰልፉ ተሳታፊዎች ዛሬ ህዳር 29/2007 ዓ.ም ጨርቆስ አካባቢ የሚገኝ ፍርድ ቤት ቀርበው ‹‹መስቀል አደባባይ ላይ ንብረት አውድመዋል፡፡›› በሚል ተከሰዋል፡፡

ፖሊስ ‹‹ታሳሪዎቹ መስቀል አደባባይ ላይ ንብረት አውድመዋል፣ የጠፉ ንብረቶችና ያልተያዙ ግብረአበሮቻቻው ስላሉ ለምርመራ 14 ቀን ይሰጠኝ›› ሲል ጠይቋል፡፡ ታሳሪዎቹ በበኩላቸው ‹‹እኛ መስቀል አደባባይ ላይ ምንም አይነት እንቅስቃሴ ሳንጀምር ነው የታሰርነው፣ ምንም ያወደምነውም ሆነ የወሰድነው ንብረት የለም፡፡›› ሲሉ የፖሊስን ክስ አጣጥለዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር በህጋዊ መንገድ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ በሚዘጋጁበት ወቅት መያዛቸውን በመግለጽ የዋስትና መብታቸው ተጠብቆ እንዲለቀቁ ጠይቀዋል፡፡ ሆኖም ዳኛው የ7 ቀን ቀጠሮ አስተላልፈውባቸዋል፡፡

በተመሳሳይ በዛሬው ዕለት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርበው የ14 ቀን ቀነ ቀጠሮ የተሰጠባቸውና በሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ የሚገኙት ታሳሪዎች በደረሰባቸው ድብደባ ምክንያት ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል፡፡ ወደ ሆስፒታል ከተወሰዱት መካከል ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት፣ እየሩስ ተስፋው፣ ጋዜጠናኛ በላይ፣ አቤል ኤፍሬም፣ ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ስሟ ያልተጠቀሰች አንዲት ሴትና ሌሎች በርካታ ወንዶች እንደሚገኙበት ታውቋል፡፡ ሶስተኛ ከሚገኙት ታሳሪዎች መካከል ከሴቶቹ ንግስት ወንዲፍራውና ምኞቴ መኮንን ከፍተኛ ድብደባ እንደደረሰባቸው እና አብዛኛዎቹ ወንዶች ለየብቻቸው ጨለማና ቀዝቃዛ ቤት ውስጥ እንደታሰሩ ተገልጾአል፡፡

No comments: