Thursday, December 18, 2014

ሱስ ትውልድና ሀገር!

December 18,2014
(ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)
shisha
በእኅታችን በሐና ላላንጎ ላይ ያ አደጋ በደረሰ ጊዜ ይሄንን ከባድ ዜና በለጠፉ ዋና ዋና ድረ ገጾች ላይ አንድ አስተያየት ሰጥቸ ነበር “ሆን ተብሎ በሱስ ትብትብ እንዲተበተብ ከተደረገ የዚህ አገዛዝ ትውልድ ከዚህ የተለየ ምን ይጠበቃል? እንደ ማኅበረሰብ ወንድም እኅቶቻችንን እናም ልጆቻችንን ከዚህ የሱስ ማጥ ውስጥ ካልታደግን በስተቀር ገና ከዚህ የከፋ ብዙ ነገርም ያሰማናል ያሳየናል” የሚል፡፡ አንዳንዶቹ የአገዛዙ ደጋፊዎች አጋጣሚውን ሆን ብየ ለፖለቲካ ፍጆታ ለመጠቀም የፈለኩ መስሏቸው አስተያየቴ ትክክል እንዳልሆነ ሲናገሩ አንዳንዶችም በመሳደብ ከአስተያየቴ ስር ምላሽ ሰጥተው ነበር፡፡ እኔ ግን ስም ለማጥፋትም አጋጣሚውን ለመጠቀምም አልነበረም፡፡ ያልኩት ነገር ለመሆኑ መረጃው ስለነበረኝ እንጅ፡፡ ወያኔ ፍጹም በደነቆረ አመክንዮና በጠላትነት ሰብእና ትውልዱን ሆን ብሎ በሱስ ማጥ ለማስጠም ሲሠራ ቆይቷል፡፡
እንደነሱ አስተሳሰብ ወጣቱ ሱሰኛ እንዲሆን በርትተው በመሥራት ሱሰኛ እንዲሆን ያደረጉበት ምክንያት “በእኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” አስተሳሰባቸው ለቡድን ጥቅማቸው አለቅጥ በመጨነቅና በማሰብ ነው፡፡ የዚህ ምክንያት እንደ የኢሐፓ ዘመን ወጣቶች በዚህች ሀገር ተመልሶ እንዳይመጣ እንዳይታይ የሞራል (የቅስም) ደረጃው የወደቀ የተሰበረ ስለ ሀገር ስለ ሕዝብ የማይገደው የማይቆረቆር ትውልድ ለማድረግ ነው፡፡ በሥልጣን ለመቆየት ለቡድን ርካሽና ነውረኛ ጥቅማቸው ሲሉ ትውልድን ሀገርን የተወሳሰበ ችግር ላይ ጣሏት፡፡ ከሱስ የጸዳ እንደ ስድሳዎቹና ሰማኒያዎቹ አጋማሽ (ከ1950-1975ዓ.ም.) ዘመን ትውልድ ከመጣ ካለ ያለሥጋት ተደላድለው መቀመጥ የሚችሉበትን ዕድል ጨርሶ እንደማያገኙት ጠንቅቀው ስለሚያውቁ፤ እንከን ጉድለታቸውን እየጠቀሰ መፈናፈኛ የሚያሳጣ የሚያፋጥጥ የሚያጋልጥ የሚሞግት የሚቃወም የሚጠይቅ የሚከስ ለምን? እንዴት? አይሆንም! አይደረግም! አይቻልም! የሚል ደፋር ተጠያቂነትና ኃላፊነት የሚሰማው ትውልድ እንዳይፈራና ሀገር አይደለም የእድር ማኅበርን እንኳን በአግባቡ የማሥተዳደር አቅም አልባ እንደመሆናቸው ከዚህ እጅግ ደካማ አቅማቸው የተነሣ ብዙ እያበላሹ ብዙ እያባከኑ ብዙ እየጎዱ እያወደሙ እያዝረከረኩ ተምረው ላይማሩ ሠልጥነው ላይሠለጥኑ ነገር ሀገሪቱን መማሪያ መለማመጃ እያደረጉ በተጫወቱባት ጊዜ በቁጣ በመነሣት ለምን እንዴት ብሎ የሚጠይቅ የሚያስጨንቅ የሚሞግት “በሉ ዞር በሉ ሀገር መቀለጃ ነው እንዴ?” ብሎ የሚያስወግዳቸው ትውልድ እንዳይኖርና እንደፈለጉ ያለክስ ያለወቀሳ ፍጹም ኃላፊነት በጎደለው መልኩ በዚህች ሀገርና በሕዝቧ ላይ ለመጨማለቅ በማሰብ ነበር እንዳይሸነጥ እንዳይቀሰቀስ እንዳይቆረቆር ሸናጭና ቀስቃሽ አናጭ አበርታች የሀገሩን ታሪክ እንዳያውቅ ካደረጉ በኋላ በሱስ ማጥ እንዲሰጥም ያደረጉት፡፡
hana3ይህ ሴራቸውም ይዞላቸው የሱሰኝነት ችግር በመንደር ወጣቶች ብቻ ሳይወሰን እጅግ አስደንጋጭ በሆነ ሁኔታ አንድም የሚያቅብና የሚከለክል በተግባርም የሚሠራ የሥነ-ሥርዓት መመሪያ (rules of discipline) ሳይኖር ሳይከለክላቸው በሀገሪቱ ባሉ ዩኒቨርስቲዎች በሙሉ በተማሪዎችና መምህራኖቻቸውን ጨምሮ የትምህርት ተቋማቱ የጫት ማመንዠኪያ ሥፍራዎች ለመሆን በቅተዋል፡፡ ይህ ችግር ከእነዚህ የትምህርት ተቋማትም ተሻግሮ አጋጥሞኝ በዐይኔ እንዳየሁት እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ በቢሮዎችም እየተመነዠከ ይገኛል፡፡
ከሱሰኝነቱ የተነሣ ትውልዱ ምን የሚል አስተሳሰብ አዳብሯል መሰላቹህ? “ለማጥናትም ሆነ ለመሥራት ያለ ጫት እንዴት ይቻላል?” እስከማለት ደርሶ ያለ እሱ ምንም ነገር ማሰብ እንዳይችል እስከመኖን ደርሷል፡፡ እንደምትሉት ከሆነ ታዲያ ማለትም “ያለ ጫት ምንም ነገር ማድረግ የማይታሰብ ከሆነ በዚህም ምክንያት ለመጠቀም ተገደን ገባንበት” ካላቹህ ከዚህኛው ከተበከለው ትውልድ በፊት የነበረው ትውልድ እንዴት ሆኖ ነበር ያለ ጫት ሥራ ሲሠራ የኖረው? ያንን ብቃት ችሎታና አቅምስ ከየት አመጣው? ጫትን ከነአካቴው የማያውቁ በርካታ ሀገራትም እኮ አሉ እዛ ያሉ ሰዎች ታዲያ እንዴት ያለ ጫት ሠርተው ስኬት ላይ ሊደርሱ ቻሉ? ይሄ ሁሉ እንዳለ ሆኖ እናንተ ጫት አመንዥካቹህ ያመጣቹህት ስኬት ምንድን ነው? በእንግሊዝኛ አይደለም በገዛ ቋንቋው እንኳን ሰዋስዉን ጠብቆ አንድ ዐረፍተ ነገር መመሥረት የማይችል የዩኒቨርስቲ ተመራቂ እስኪታጣ ድረስ የትምህርት ጥራቱ ዜሮ መግባቱና በጫት የደነዘዘ ትውልድ መፍራቱ ነው ወይ ስኬታቹህ? ተብለው ሲጠየቁ አንድ እንኳን የሚመልሱት መልስ የላቸውም፡፡ ሲጀመርም ያሉት ነገር ትክክል መሆኑን አምነው ሳይሆን ለሱሰኝነታቸው ሽፋን ለመስጠት የሱስ ጥገኛነታቸውን ጠብቀው ለመቆየት ሲሉ የሚቀበጣጥሩት ነው፡፡
ኢትዮ ምኅዳር ጋዜጣ አሁን ወዳለበት ስፍራ ከመምጣቱ በፊት ስድስት ኪሎ የስብሰባ ማዕከል አጠገብ መንገዱ ጠርዝ ላይ ነበር ቢሮው ጽሑፍ ለማቀበል ስሔድ ዐየው የነበረው ነገር እጅግ አስደንጋጭ ነበር፡፡ አጎራባች ክፍሉ ጫት መቃሚያ ሺሻ ማጨሻ ቤት ነው የዚያ ቤት ተጠቃሚዎች በሙሉ “የዩኒቨርስቲ መምህራንና ተማሪዎቻቸው” የተባሉ ናቸው፡፡ ነገሩ ሳይገባኝ የገረመኝ ነገር ሚኖር ተማሪዎቹ ምን ሰዓት እንደሚማሩ መምህራኖቹም ምን ሰዓት እንደሚያስተምሩና በየቀኑ ለሚያመነዥኩበትና ለሚያጨሱበት ገንዘብ ከየት እንደሚያመጡ ነው፡፡ ለእነዚህ መምህራን አጥንቶ ሳይሆን ውጤት ገዝቶ ለመመረቅ፣ ከኮርስ ወደ ኮርስ ለማለፍ ለፈለገ ተማሪ ያ ቤት እንደቢሮም ሆኖ ያገለግላቸዋል፡፡ እንደዚህ ቤት ዓይነት ተመሳሳይ ቤቶች ዩኒቨርስቲና አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ባሉበት ቦታ ሁሉ አለ፡፡
ይህ በወያኔ ደንቆሮና እራስ ወዳድ አስተሳሰብ የተስፋፋ የሱስ ችግር ሀገሪቱን የማትወጣበት ችግር ውስጥ ከቷታል፡፡ ከነዚህም ጥቂቶቹ፡-
  1. የሥነ-ምግባር አጥሮቻችን እየፈራረሱ ነው፡፡ ግብረ-ገብነት ጠፍቷል ለሞራል (ለቅስም) ድንጋጌዎች ዴንታ ቢስነት ተስፋፍቷል፡፡
  2. በየዩኒቨርስቲው የሚመረቀው ብቃት የሌለው ተመራቂ በየሥራ መስኩ ተሰማርቶ የሀገሪቱን ውስንና አነስተኛ የሀብት መጠን በከፍተኛ ደረጃ እያባከነና ሀገሪቱን በሌላት አቅም ለከፍተኛ ኪሳራ መዳረጉ፡፡
  3. ትውልዱ ሱሰኛ ከመሆኑ የተነሣና ሱስ ደግሞ እያደገ የሚሔድ በሽታ እንጅ አንድ ቦታ ላይ የሚቆም ባለመሆኑ በጫቱ ላይ ሺሻና ሀሽሽ ሌሎችንም ዕጾች ለመጨመር በመገደዱ እነኝህን እያደጉ የሚሄዱ የሱስ ፍላጎቶቹን ለማሟላት ገቢው (ደሞዙ) ደግሞ የሚበቃው ባለመሆኑ ሳይወድ በግዱ ሙስና ውስጥ እየተዘፈቀ ሀገሪቱ በሙስና የነቀዘች እያደረገ ለሀገር ጠንቅ መሆኑ፡፡
  4. ጫት የሚያመነዥኩ ሰዎች ያነቃናል ያበረታናል ይላሉ ነገር ግን መሰላቸው እንጅ እያበረታቸው ሳይሆን እየገደላቸው ነው፡፡ ጫትም ሆነ ሌላው ሱስ አማጭ ነገር ጥቂት አበርትቶ ከሆነ ብዙ ደግሞ የዚያን ሰው ተፈጥሯዊ አቅም ያጠፋል ይገላል፡፡ በዚህም ምክንያት ነው ያ ሱሰኛ ሰው ተጠቃሚ ከመሆኑ በፊት ይታዘዝለት የነበረ ሰውነቱ ሱሰኛ ከሆነ በኋላ ግን እሱን ካላገኘ ሰውነቱ የማይታዘዝለት ጭንቅላቱም የማይሠራለት፡፡ በዚህ ምክንያት ተፈጥሯዊ አቅማቸው ተሟጦ የጠፋባቸው የወደመባቸው በሱሱ ብቻ የሚነቁ በርካታ ሙታንና የአእምሮ ሕሙማን እንዲኖረን ማድረጉ፡፡
  5. ያ ከሱሰኝነት የተነሣ የሙሰኝነት ሰብእናቸውም ለሀገርና ለወገኝ ታማኝ እንዳይሆኑ አድርጎ የሀገርንና የወገንን ጥቅም አሳልፈው የሚሰጡ በክህደት የተሞሉ እንዲሆኑ ማድረጉ፡፡ ሌሎችም አሉ አንዱ ችግር ሌላውን እየሳበ መዘዙ ብዙ ነው፡፡ እንግዲህ ያ ደንቆሮ አሕያ የሰይጣን ቁራጭ እርጉም ከይሲ ለራሱ ወይም ለቡድኑ ርካሽና ነውረኛ ጥቅሙ ሲል ይሄንን ነቀርሳ ነው ጥሎብን የሔደው ነፍሱን አይማረዋ ሌላ ምን እላለሁ፡፡
ይሄንን በትክክል ሆን ብለው ለማድረጋቸው የሚያረጋግጡ ማስረጃዎችን ላንሣ፡-
  1. ቆየ ከዓመታት በፊት ነው የጎንደር ከተማ ፖሊሶች የአዲስ አበባ ፖሊሶች በተደጋጋሚ የሺሻ ማጨሻዎችን ከየ ጫት መቃሚያ ቤቶች እየሰበሰቡ ሲያቃጥሉ በቴሌቪዥን በመመልከታቸው እኛም እንታዘዛለን ብልው ቢጠብቁ ቢጠብቁ ትእዛዝ ሊደርሳቸው ስላልቻለ “እንዲያውስ ለምን ትእዛዝ እንጠብቃለን?” ብለው “ጫትን ዝም ብለን በማየታችን እዚህ ደረጃ ላይ ደረሰ አሁን ደግሞ ይሄ ሺሻ የሚባለውን እንደጫቱ ዝም ብንለው ሀገር ሊበላሽ አይደል?” ብለው በግል ተነሣሽነታቸው ከየ ጫት ቤቱ ሰብስበው ሊያቃጥሉ ሲዘጋጁ ወዲያው ከክልል ተደውሎ “ማን አዘዛቹህ? ባስቸኳይ ከየሰባሰባቹህበት አሁኑኑ መልሱ!” ተብለው እንዲመልሱ ተደርጓል፡፡ ይህ አስገራሚ ነገርም በሕዝቡ ዘንድ ታላቅ ቅያሜና ጥርጣሬ ፈጥሮ “ለካ እንድንጠፋ ነው እየተሠራብን ያለው” እያለ ሕዝቡ ቢያጉረመርምም ከመ ጤፍ ሳይቆጥሩት ይህ ከሆነ ከዓመት ሁለት ዓመት በኋላ ለይስሙላ ፖሊስ እንዲሰበስብ አድርገው እንዲቃጠል አደረጉ፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ከነበረውም በበለጠ ተስፋፍቶ ቀጥሏል፡፡
  2.  በየ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ዙሪያ ተማሪዎቹን ታሳቢ አድርገው በትምህርት ቤቶቹ ዙሪያ በተከፈቱ የጫትና የሺሻ ቤቶች ተማሪዎች እየተጠለፉ በርካታ ጉዳቶች እየደረሱ ትውልዱ እየጠፋ ቢቸገሩ በተለያዩ ቦታዎች ያሉ ወላጆች በተለያየ ጊዜ “መንግሥት ባለበት ሀገር እንዴት እንዲህ ያለው ኃላፊነት የጎደለው የጠላት ሥራ ይሠራል? በማለት ፊርማ አስባስበው ይመለከታቸዋል በሚሏቸው መንግሥታዊ ተቋማቶች ቢሔዱ “ሕጋዊ የንግድ ቤቶችና ግብር ከፋዮች ናቸው አርፋቹህ ተቀመጡ” የሚል ማስፈራሪያ የታከለበት መልስ ነበር የተሰጣቸው፡፡ ማንም ሰው ግብር ከከፈለ ምንም ዓይነት ነገር ይሁን በግላጭ በአደባባይ ሱቅ ተከፍቶ መሥራት ይቻላል ማለት ነው፡፡ እንደ መንግሥታዊ አካል ለኅብረተሰብ ለሀገር ጎጂ ነው ወይስ አይደለም? የሚለው ወሳኝ ጥያቄ ዐይታያቸውም አይታሰባቸውም፡፡ ለነገሩ ጎጅነቱ ጠፍቷቸው ሳያውቁት ቀርተው አይደለም ዓላማቸው ስለሆነ እንጅ፡፡
እነኝህ ወላጆች የሰጉት አደጋና ከሰጉላቸው ተማሪዎች አንዷ ሐና ላላንጎ ናት፡፡ የሐና ላላንጎ ጉዳይ በወላጆቿ ብርታት ለሕዝብ ጆሮ በቃ እንጅ በእነዚህ የሺሻና የጫት ቤቶች ሕዝብ ሳያውቃቸው ተሰብረው ከነ ሥነ-ልቡና ስብራታቸው ወድቀው የቀሩ ሊደርሱበት ይችሉት ከነበረው ሕልማቸው ተሰናክለው የቀሩ እጅግ እጅግ በርካቶች ናቸው ቤቱ ይቁጠራቸው፡፡ የሐና ወላጆች ጉዳዩን ግልጽ ካደረጉት አይቀር ለልጃቸው ስም በማሰብ ይሄንን ጉዳይ ከማድበስበስ ይልቅ “በሐና ይብቃ!” እንደማለታቸው ችግሩን ከስሩ ለመንቀል ሊረዳ በሚችል መልኩ ልጃቸው ያጋጠማትን ችግር ግልጽ ቢያደርጉት ኖሮ በእነዚህ የጫትና የሺሻ ቤቶች ዙሪያ ኅብረተሰቡ እንደማኅበረሰብ ተቀስቅሶ በነበረው ተነሳሽነት ሊወስዳቸው ይችላቸው ከነበሩት አቋሞችና እርምጃዎች አንጻር ምን ያህል በጠቀመ ነበር፡፡hana 2
ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ ግለሰቦችና ሐናን አታላ በመውሰድ ለዚያ አደጋ አመቻችታ ከሰጠቻት ጓደኛዋ እንደተሰማው፡፡ በትምህርት ሰዓት ከትምህርት ቤት ጠፍተው ጫትና ሺሻ ወደሚያስተናግዱበት ቤት ሔደው ነበር፡፡ ልጅቱን ለእርድ ያሰቧት ሱሰኛ የቤቱ ደንበኞችም ለሐና ሻይ ውስጥ የሚያደነዝዛትን ነገር ጨምረው ሰጥተዋት ራሷን ፈጽሞ በማታውቅበት ሁሌታ ላይ እያለች ነበር ያ ግፍ የተፈጸመባት፡፡ ከደረሰባት አደጋ የተነሣ አልነቃ ስትላቸው ነበር ወደ ሌላ ቦታ ወስደው እዛም ሲጫወቱባት እንዲሰነብቱ የሆነው፡፡ ይህ ግፍና አረመኔያዊ ድርጊት የሚከብደው ለጤነኛ ሰው ነው እንጅ ለእነኝህ በጫት በሺሻና በተለያዩ ዕጾች ለደነዘዙ ዜጎቻችን አይደለም፡፡ በመሆኑም ነው ለልጅቱ ሰውነቷ እንደ ጨርቅ ተቀዳዶ ወድቃም እንኳን ሳይተዋት እየደጋገሙ ያንን ግፍ ሊፈጽሙባት የቻሉት፡፡ ለእነሱ ይህ የዕለት ተዕለት ተግባራቸው ነው በርካታ ልጆች በዚህ መንገድ እንዳይሆኑ ሆነው ተሰብረው ወድቀዋል፡፡ ገመናየ ብለው ውጠው የተቀመጡና በሥነ-ልቡና ሕመም እየተሰቃዩ ያሉ እኅቶችና ወንድሞችም ጭምር በርካቶች ናቸው፡፡ ያለን መስሏቹሀል? የለንም እኮ! ነቅዘናል በስብሰናል መድኃኔዓለም ክርስቶስ ይቅር ይበለንና አንዳች መፍትሔ ይዘዝልን፡፡
  1.  ይህ የጫትና የሺሻ ቤቶች ችግር የዚህን ያህል ችግር እንደሆነ ቢታወቅም ለራሱ ጉዳይ ሲሆን በአንድ ምሽት ውስጥ ሕግ አውጥቶ አጽድቆ በማግስቱ ሥራ ላይ የሚያውል አገዛዝ ይሄንን ችግር በተመለከተ ግን ይሄው ሕዝብ እድሜ ዘመኑን እየጮኸም እንኳን ሕግ መቅረጹ ጥቅሜ ይጎዳብኛል ብሎ ስለሚያስብ ምንም ዓይነት የተቀረጸ ሕግ በሌለበት ሁኔታ ለማስመሰል ብቻ አንዳንዴ የዘመቻ እርምጃዎች እየወሰደ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ሕጉ እንዳይቀረጽና ኅብረተሰቡም ይህን ችግር በሕግ ድጋፍ ለመከላከል እንዳይችል ማድረጉ፡፡ በነገራችን ላይ ስለ ሕግ ካነሣን አገዛዙ ክልል አንድ ብሎ በሚጠራው ሀገሩ መቀሌ ጫት መቃምም ሆነ ማዘዋወር በሕግ የተከለከለና የሚያስቀጣም ወንጀል ነው፡፡ የዚህን አገዛዝ ዝቃጭ ዓላማና ሸር ዐያቹህት? በተቀረው የሀገሪቱ ክፍል ግን በሕግ የተፈቀደ ነው ለምን? ቢባል እንዲጠፋ ይፈለጋላ!
በአሁኑ ሰዓት ከአገዛዙ በሚሰጥ ምክርና ድጋፍ የተነሣ ጫት የሀገሪቱ ዋነኛ ምርት እየሆነ መጥቷል አስቀድሞ ቡናና የተለያዩ አትክልቶችና አዝርእት ይመረትባቸው የነበሩ በሀገሪቱ የትኛውም ክፍል ውኃ ገብ የገበሬው የመስኖ መሬቶችን ብታዩ ዛሬ ላይ በሙሉ በጫት ተክል ተይዘዋል፡፡ አገዛዙ የጫትን ምርትና ንግድ ሰፊ አቅድ ይዞ እየሠራበት ይገኛል ይህ አገዛዝ ከጫት ምርትና ንግድ ዐሥር ብር ያገኝ እንደሆን በጫት ምርት ምክንያት በአንድ ሽህ ብር ሊወገድ ሊሞላ ሊካካስ ሊቀረፍ የማይችል ችግር በሀገሪቱ ላይ እየፈጠረ እንደሆነ ይጠፋዋል ብየ አልገምትም ነገሩ የዓላማ ጉዳይ ስለሆነ እንጅ፡፡
ዛሬ ላይ ሌላው ቀርቶ ጫት በማመንዠክና ሺሻ በማጨስ ይታወቁ የነበሩ ዓረብ ሀገራት እንኳን ሕግ አውጥተው በከለከሉበት ዘመን ነው እኛ ግን እንድንጠፋበት በወያኔ ተፈርዶብን እንዲህ እየተደረገ ያለው፡፡ የአገዛዙ ነጋዴ ባለሥልጣናት ጫት ኤክስፖርት (የወጪ ንግድ) ይሠሩበት የነበሩት ሀገራት እንግሊዝና አሜሪካም ጫትን ከአደንዛዥ ዕጾች በመመደብ ጫትን በሕግ ከልክለዋል አሁን በእነዚህ ሀገራት በጠቀምም ሆነ ማዘዋወር ሕገ ወጥ ነው፡፡ ሌሎችም የአውሮፓ ሀገራት ተመሳሳይ እርምጃ ለመውሰድ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ጫት በሀገር ውስጥ ካልሆነ በቀር ወደ ውጪ ተልኮ የውጭ ምንዛሬ ማግኛ መሆኑ ቀረ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሀል ቡናውንና ሌሎች አትክልቶችን አስወግዶ ጫት እንዲተክል የተደረገው ገበሬ ሊደርስበት የሚችለው ኪሳራ ቀላል አይሆንም፡፡ ጫቱን ነቅሎ የነበረውን ቡናና ሌላ ተክል ተክሎ አሳድጎ ከዚያ ምርት አግኝቶ ተጠቃሚ እስኪሆን ጊዜ ድረስ በችጋር መቆራመዱ መጥፋቱም የማይቀር ነው፡፡ እዚህ ላይ ሌላም ችግር አለ ገበሬውም ራሱ የጫት ሱሰኛ የሆነበት ሁኔታ ስላለ ጫቱን ነቅሎ በሌላ ምርት ይተካል ብሎ ተስፋ ማድረጉም የማይታሰብ ሊሆን ይችላል፡፡ እንግዲህ ጣጣው ዘርፈ ብዙ ነው፡፡ እንግዲህ ከእነዚህ ሁሉ ነገሮች እንደምንረዳው አገዛዙ ሆን ብሎ እንዲስፋፋ ማድረጉን ነው፡፡
ቀደም ሲል ፋና በሚባለው ሬዲዮ ላይ በጸረ ሱስ ትምህርታዊ ዝግጅት ላይ አተኩሮ ይሠራ የነበረ አንድ ጋዜጠኛ ነበር ያን ዝግጅት ካቆመው በኋላ ወደ ሸገር ሄዶ ነበር አሁን እንደገና ወደ ፋና ተመልሷል፡፡ ያንን ዝግጅት ያዘጋጅ እንደነበረ ነገረኝ በኋላ ላይ ከአቅሙ በላይ የሆኑ ችግሮች ቢመጡበትም እነሱን ለመቋቋም ወስኖ ለመሥራት እየጣረ ለእግር ኳስ ሲባሉ ገንዘባቸውን የሚያዘንቡት ድርጅቶች ለዚህ ዓይነት ዝግጅት ሲባሉ ግን አምስት ሳንቲም እንኳን የማይደማቸው ሆኖ ስፖንሰር በማጣት አቆምኩት አለኝ፡፡ ለዚያ ሬዲዮ ቅጥር ሠራተኝነቱን ትቶ እዛው ሬዲዮ ላይ የራሱን የአየር ሰዓት በመውሰድ ነበር ያንን ዝግጅት ያዘጋጅ የነበረው፡፡ የገጠመህ ከአቅም በላይ ፈተና ምን ነበር? ብየ ስጠይቀው ምን አለኝ “ማንነታቸውን የማላውቃቸው ሰዎች በመቶ ሽዎች የሚቆጠር ገንዘብ አቀረቡልኝና ዝግጅቱን እንዳቆመው ሊያግባቡኝ ሞከሩ እንደማላደርገው ስነግራቸው እንደሚገሉኝ ዝተውብኝ ነበር” አለኝ፡፡ ይህ ጋዜጠኛ የነገረኝ ነገር እውነት ከሆነ በትውልዱ መክሰር ተጠቃሚዎች የሆኑ እነዚህ አካላት እነማን ናቸው?
ሕዝብ ሆይ! ለራስህ እራስህ እወቅበት መንግሥት መቋቋሙ ለዚህ ለዚህ ነበር፡፡ ነገር ግን ከዚህ ከዚህ አደጋ ይጠብቀኛል ወላጅ ለልጁ እንደሚያስብ እንደሚቆረቆር እንደሚጨነቅ እንደሚጠበብ ይጠበብልኛል ይጨነቅልኛል ያስብልኛል ይጠነቀቅልኛል ይቆረቆርልኛል በአግባቡ ያስተዳድረኛል ከጥቃት ይጠብቀኛል ያልከው መንግሥት ተብየ እራሱ አጥፊህ ሆኖ ሲገኝስ ጨርሶ እስኪያጠፋህ ድረስ እጅ እግርህን አጣምረህ በዝምታ ነው የምትቀመጠው ወይስ ከላይህ ላይ አውርደህ ትፈጠፍጠዋለህ???
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

No comments: