Friday, November 14, 2014

ፌደራል ፖሊሶች ለሚፈጽሟቸው ግድያዎች ተጠያቂው ማን ነው?

November 14,2014
ከዳዊት ሰለሞን
dawitይህ ጥያቄ በቀጥታ በመንግስት ትዕዛዝ የተፈጸሙ ግድያዎችን አይመለከትም፡፡እንደውም በፓርላማ ከቀረበው ረቂቅ አዋጅ አንዱ ‹‹በግዳጅ ላይ ያለ የመንግስት ታጣቂ ለሚፈጽመው ጥፋት ተጠያቂ እንዳይሆን ››የሚሞግት ነው፡፡
ፓርላማው 446 ለ 1 የሚመራ በመሆኑም ገዢው ፓርቲ የፈለገውን አዋጅ የማውጣት መብቱ የተጠበቀ ነው፡፡በዚህ ገጽ ግን ለማንሳት የወደድኩት ታጣቂዎች ከስራ ገበታቸው ውጪ እየፈጸሟቸው የሚገኙ ግድያዎች ሀላፊ ማን ይሆናል የሚለውን ነው፡፡
ንፋስ ስልክ አካባቢ የመንግስት የሰላም አስከባሪ አባል የነበረ አንድ መቶ አለቃ ጎረቤቶቹን በ35 የክላሽ ጥይት መግደሉና ህጻናቱን ያለ ወላጅ ማስቀረቱ አይዘነጋም፡፡
መቶ አለቃው ከታሰረ በኋላ በልዩ እንክብካቤ ተይዞ ወላጆቻቸውን ባጡ ህጻናት ላይ ይዘት እንደነበርና በኋላም አመለጠ ተባለ፡፡መቶ አለቃው መጨረሻ ላይ ስለመያዙ ተነገረ፡፡
ባህርዳር የተፈጸመውን አሰቃቂ ግድያ አንዘነጋውም፡፡አፍቅሪያታለሁ ያለ ፌደራል ፖሊስ የ18 ሰዎችን ህይወት ቀጥፎ ወንዝ ውስጥ ገብቶ ሞተ የሚል ወሬ ተናፈሰ፡፡
ቂርቆስ መንደር በምትገኝ የሴተኛ አዳሪዎች ሰፈር እንዲሁ የእኔ የሚላትን ሴተኛ አዳሪ ከሌላ ወንድ ጋር ተኝታ በማግኘቱ ፌደራሉ በሁለት ጥይት ደረቷን መትቶ ለህልፈት ዳረጋት ፣ከሴትየዋ ጋር የነበረው ጎልማሳም እግሩን በጥይት ለመቆረጥ በቅቷል፡፡
ይህ ፎቶ ግራፍም በተመሳሳይ መንገድ በፌደራል ፖሊስ ህይወቱን በግፍ ስለ ተነጠቀ ወጣት የሚጮህ ነው፡፡
ጅማን በእንባ፣በድንጋጤና በተቃውሞ የሞላ ክስተት የተስተናገደው በፌደራል ፖሊስ ነው፡፡በምሽት ሰው ቤት ሰብሮ የገባው ፖሊሱ አንዲት አይነ ስውር እናትና ልጃቸውን ቀጥፏል፡፡
ግለሰቡ ስለ መያዙም ተነግሯል፡፡ግን ይህ ነገር በገዳዮቹ መያዝ ብቻ የሚያበቃ መሆን የለበትም፡፡ተጠያቂነቱ ወደ ላይም መውጣት አለበት፡፡መሳሪያ መያዝ የማይገባቸው፣ሰብዓዊነት ምን ማለት እንደሆነ የማይረዱ፣ግደሉ ሲባሉ ከመግደል የማያመነቱ፣መሳሪያ ሲጨብጡ ጭንቅላታቸውን ቃታው ጋር የሚያደርጉ ሰዎችን መለዮ እያለበሱ ስልጣናቸውን ለማራዘም እስከጠቀሟቸው ድረስ ስለሚፈጽሙት ዘግናኝ ድርጊት ደንታ የሌላቸው አካላትም መጠየቅ ግድ ይላቸዋል፡፡
የሟቾቹ ደምም በተኳሾቹ ላይ ብቻ ሳይሆን ነፍጥ ባሸከሟቸው ሀይሎች ላይም ይጮሃል፡፡

No comments: