Monday, November 3, 2014

የአንድነት ፓርቲ አዲስ አመራር መግለ ጫሰጠ

November 3,2014
‹‹በእነሀብታሙ ላይ የተደረገው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት እጅግ አሳፋሪ ነው››
‹‹ኢንጂነር ግዛቸው በአንድነት ቤት እንደጀግና መታየት አለባቸው››
‹‹ከመኢአድ እና ሰማያዊ ፓርቲዎች ጋር ተዋህደን መስራት አለብን››
አቶ በላይ ፍቃዱ /የአንድነት ሊቀመንበር/
—————-

‹የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አሸባሪ ነው››
‹‹ዘንድሮም አዋጁ ይሰረዝ ብለን መጠየቃችንን እንቀጥላለን››
አቶ ግርማ ሰይፉ /የፓርላማ ተወካይ የአንድነት ም/ፕሬዚዳንት/

——————————–
ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ጥቅምት 20 ቀን 2007 ዓ.ም፣ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት) ‹‹በፖለቲካ እስረኞች ላይ እየተፈጸመ ያለው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት አሳሳቢ ደረጃ ላይ ይገኛል!›› በሚል ርዕስ በጽ/ቤቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቶ ነበር፡፡ መግለጫውንም የሰጡት የወቅቱ የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ በላይ ፍቃዱ፣ ም/ ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ሰይፉ እና የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዘካሪያስ የማነ ብርሃን ናቸው፡፡


የኢህአዴግ አገዛዝ ከጊዜ ወደጊዜ ሰብዓዊ መብት በመጣስና ዜጎችን በማሰቃየት ወደር የሌለው መሆኑን የጠቀሰው መግለጫው ‹‹ሥርዓቱ ለአገዛዜ ያሰጉኛል የሚላቸውን ንጹሃን የፖለቲካ አመራሮችን፣ ጦማሪያንና ጋዜጠኞችን ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ ክስ በመመስረት ማሰሩ ሳያንስ እነዚህን ዜጎች ሰብዓዊ ክብራቸውን በመድፈርና ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት እየፈጸመ በማሰቃየት ላይ ይገኛል፡፡›› ብሏል፡፡


ፓርቲው የሥርዓቱ ዱላ ሆኖ እያለገለ ያለው የጸረ-ሽብርተኝነት አወጁ እንዲሰረዝ በህዝባዊ ንቅናቄ መጠየቁን በማውሳት ገዥው ፓርቲ ግን አምባገነንነቱን አጠናክሮ በመቀጠል በዜጎች ስቃይ መደሰትን ለጥያቄው ምላሽ ማድረጉን አስረድቷል፡፡


አቶ አንዷለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ አንዷለም አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሺ፣ ሀብታሙ አያሌውና ሎሎችም በፖለቲካ እምነታቸው የተነሳ ወደማሰቃያ ስፍራ የተወሰዱ የአንድነት የቁርጥ ቀን ልጆች መሆናቸውን የጠቆመው መግለጫው፣፣ በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው በማዕከላዊ እስር ቤት በሚገኙት ዳንኤል ሺበሺ እና ሀብታሙ አያሌው ላይ የደረሰውን ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት ኮንኗል፡፡


ከመግለጫው በኋላ ከጋዜጠኞች የተለያዩ ጥያቄዎች ተነስተው ምላሽ ተሰጥቶባቸው ነበር፡፡ ‹‹በእነ ሀብታሙ ላይ የተደረገው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት እጅግ አሳፋሪ ነው›› በማለት ለጥያቄዎች መልስ በመስጠት የጀመሩት አቶ በላይ ‹‹የቀድሞ የፓርቲው ሊቀ-መንበር ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው በሕገ ደንቡ መሰረት በፈቃዳቸው መልቀቂያ ካስገቡ በኋላ ብሐራዊ ምክር ቤቱ ኃላፊነት በተሞላበት መልኩ የስልጣን ሽግግሩን በሕግ አግባብ ፈጽሟል፡፡ ኢንጂነሩ ውሳኔያቸው ትክክል ነበር፡፡ እሳቸውም ደስተኛ ናቸው፡፡ ኢንጂነር ግዛቸው በአንድነት ቤት እንደጀግና መታየት አለባቸው፡፡ ብዙ ፈተናዎችን አልፈዋል፡፡ በአንድነት ቤት የተለየ ቦታ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡›› ብለዋል፡፡


ውህደትን በተመለከተ ለቀረበላቸው ጥያቄም የፓርቲው አዲሱ ሊቀመንበር ‹‹ከፓርቲዎች ጋር አብሮ የመስራት አቋም አለን፡፡ የአንድነት እና የመኢአድ የውህደት ጉዳይ ቢያልቅም በአሰራር ደረጃ ትንሽ የሚቀር ነገር አለ፡፡ በአንድነት ዕይታ የፖለቲካ ምህዳሩን ማስተካከል አለብን፡፡ ከመኢአድ እና ሰማያዊ ፓርቲዎች ጋር ተዋህደን መስራት አለብን፡፡ በድርጅቶቹ ባህል አኳያ እንጂ ሶስታችንም ከርዕዮተ ዓለም ጀምሮ ብዙ ልዩነት የለንም፡፡ አንድ ነን፡፡ ይህ ውህደት መቼ እንደሚሆን በእርግጠኝነት መናገር ባልችልም አንድ ቀን ግን እውን ይሆናል ብለን እናምናለን›› የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
የፓርላማ ተወካዩ አቶ ግርማ ሰይፉ በበኩላቸው፣ የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁን አስመልክቶ ለቀረበላቸው ጥያቄ ፓርቲያቸው በ‹‹ሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት›› በሚለው ንቅናቄ ‹‹አዋጁ ይዘረዝ!›› በማለት መጠየቃቸውን አስታውሰው፣ ‹‹ዘንድሮም አዋጁ ይሰረዝ ብለን መጠየቃችንን እንቀጥላለን፡፡ የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ አሸባሪ ነው›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡


በመጨረሻም ፓርቲው በመግለጫው፣ የበደልን ዘመን ለማሳጠር እንዲቻል ህዝቡ በቁጭት ለለውጥ እንዲነሳ ጥሪ አቅርቦ በደልን ለማስቆም መታገል ወሳኝና ብቸኛው መፍትሄ መሆኑን አስረድቷል፡፡

No comments: