Friday, November 14, 2014

የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ፖሊስ ጣቢያዎችን እንዲሰሩ ተጠየቁ

November 14,2014
የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች በየ አካባቢያቸው ለሚሰሩት አዳዲስ ፖሊስ ጣቢያዎች ገንዘብ እንዲያዋጡ መጠየቃቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ በየ አካባቢው የሚገኙት የፖሊስ ጣቢያዎች ነዋሪዎች ገንዘብ እንዲያዋጡ በየ ቤታቸው ደብዳቤና የገንዘብ መክፈያ ቅጽ እየሰጡ ሲሆን ነዋሪዎቹ ገንዘብ እንዲከፍሉ የተጠየቁበትን ቅጽ ሳይሞሉ መመለስ አይችሉም ተብሏል፡፡

ደብዳቤው ላይ ባለው የፖሊስ ጣቢያው ስልክ ቁጥር ደውለን ያነጋገርናቸውና ስማቸውን ለመግለጽ ፈቃደኛ ያልሆኑ አንድ የፖሊስ አባል ‹‹ህዝቡን ለምን ፖሊስ ጣቢያ እንዲሰራ ታስገድዳላችሁ?›› በሚል ላነሳነላቸው ጥያቄ ‹‹ህዝቡኮ ራሱ ነው ሴት ልጆቻችን በሰላም መግባት አልቻሉም እያለ ያለው፡፡ ፖሊስ የህዝብ እስከሆነ ድረስ ህዝብ ፖሊስ ጣቢያ ቢያሰራ ምን ችግር አለው? ህዝቡ አልከፍልም ካለ ሊቀር ይችላል፡፡ እናንተ ግን ይህን እንደጥያቄ የምታነሱት ስብሰባው ላይ ስላልነበራችሁ ነው፡፡›› ብለውናል፡፡

ከወራት በፊት ‹‹ማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ›› በሚል አደረጃጀት ህዝቡ በየቤቱና ከጎረቤት ጋር 1ለ5 በመደራጀት ከፖሊስ ጋር ግንኙነት እንዲኖረው የሚያዝ ህግ መውጣቱና ነዋሪዎቹንም ማደራጀት መጀመሩን ነገረ ኢትዮጵያ መዘገቧ ይታወቃል፡፡


No comments: