Wednesday, November 12, 2014

የዞን 9 ጦማርያን እና ወዳጅ ጋዜጠኞች አስራአንደኛ የፍርድ ቤት ውሎ

November 12,2014
በዛሬው እለት በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ 10 ተከሳሾቸን ጉዳይ ሊያይ የተሰየመው ችሎት በጦማርያኑ እና በጋዜጠኞቹ ላይ የቀረበውን ክስ አቃቤ ህግ አንዲያሻሽል ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
ባለፈው ሳምንት የክስ ፋይሉን አስመልክቶ የህግ እና የፍሬ ነገር ችግር አለበት በሚል የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ ያቀረቡትን የተከሳሾች ጠበቆች አንዲሁም መሻሻል የሚገባው ነገር የለውም ያለውን የአቃቤ ህግን መልስ ተከትሎ ብይን ለመስጠት ተቀጥሮ በዳኞች ለውጥ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶ የነበረው ችሎት ዛሬ ክሱ ላይ መሰረታዊ ማሻሻያ እንዲደረግ ብይን ሰጥቷል፡፡
ብይኑም በአጠቃላይ ሲታይ
1. በመጀመሪያው ክስ የጸረ ሽብር ህጉን አንቀጽ አራት በመጥቀስ በደፈናው የሽብር ስራ ተብሎ ቀርቦ ነበረውን ክስ አስመልክቶ ፍርድ ቤቱ ክሱ ፈጸሙትን ወይም ሊፈጽሙ ያሰቡትን የሽብር ተግባር በአንቀጽ ሶስት መሰረት አቃቤ ህግ በዝርዝር አንዲያስቀምጥ መቼ እና እንዴት አንደፈጸሙት ተግባሩም ምን እነደሆነ አንዲገለጽ
2. የሽብር ቡድን ፣ ግንቦት ሰባት አንዲሁም ኦነግ በማለት በተለያየ ቦታ የተጠቀሱ ስሞች ከመኖራቸው ባሻገር ግልጽ የሆነ ነገር ባለመኖሩ የተባለው የሽብር ቡድን ማን እነደሆነ በግልጽ አንዲቀመጥ ( አቃቤ ህግ በክሱ አንድም ቦታ ላይ ዞን 9 የሚል ቃል አለመጠቀሙን ያስታውሷል)
3. ስትራቴጂ እና ተልእኮ በመቀበል የሚለው ክስ ምን አይነት ስትራቴጂ እና ምን አይነት ተልእኮ ከማን ለእነማን ተከሳሾች አንደሆነ በግልጽ እንዲቀመጥ
4. የገንዘብ ድጋፍን አስመልክቶ ለሽብር ተግባር ተቀበሉት የተባለው ገንዘብ ከማን እነደተላከና ለምን ሽብር ተግባር አንደዋለ በዝርዝር አንዲገለጽ
5. የተከሳሾችን የስራ ክፍፍል አስልመልክቶ አቃቤ ህግ አቃቤ ህግ ለይቶ እነማን ምን የሽብር ስራ ክፍፍል አንደነበራቸው ለይቶ እንዲያቀርብ
6. ህገ መንግስቱን በሃይል መናድ የሚለው ክስ በአንደኛ ክስ ላይ ከተጠቀሱ ተግባራት ጋር ተመሳሳይ በመሆኑ ሙሉ ለሙሉ ውድቅ አንዲሆን እና ጉዳዩ በጸረ ሽብር ህጉ ብቻ አንዲታይ ብይን ሰጥቷል፡፡
በተመሳሳይ ፍርድ ቤቱ ሁለቱ ሴት ተከሳሾች ማህሌት ፋንታሁን እና ኤዶም ካሳዬን የማረሚያ ቤት አያያዝን አስመልክቶ ማረሚያ ቤት ሃላፌ ቀርበው መልስ አንዲሰጡ ባዘዘው መሰረት የማረሚያ ቤት ተወካይ መጥተው የእስረኞቹ አያያዝ እንደማንኛውም እስረኛ ነው ብለው የካዱ ሲሆን በተጨማሪም ማንኛውንም አይነት ችግር ካለ ከተከሳሾች ጋር በመነጋገር ለመፍታት ፍቃደኛ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም የፍርድ ሂደቱን ላለማጓተት የተከሳሽ ጠበቆች ከማረሚያ ቤቱ ጋር አንዲነጋገሩ እና መፍትሄ ላይ እነዲደርሱ አንዲሁም ለውጥ ከሌላው ግን የተከሳሽ ቤተሰቦችን ምስክርነት ለመስማት የሚገደድ መሆኑን ገልጿል። አቃቤ ህግ ክሱን አሻሽሎ ተከሳሾች አንደተለመደው በሙሉ የስሜትና የአካል ደህንነት ላይ ሆነው ወዳጆቸን ሰላም ሲሉ እና እርስ በርሳቸው ሲወያዩ ተስተውለዋል፡።
ማስታወሻ - ዞን 9 የጦማርያን ቡድን ፍርድ ቤቱ የክስ ማሻሻል ትእዛዝ በበጎ ጎን የምንመለከተው ሲሆን የፍትህ ስርአቱ የሚታማበትን የተለመደውን ገለልተኛነት የማጣት ችግር አስወግዶ ጦማሪ ጓደኞቻችንን እና ወዳጅ ጋዜጠኞችን ከክሱ በነጻ በማሰናበት ታሪካዊ ሃላፌነቱን አንደሚወጣም ተስፋ አናደርጋለን፡፡ የዞን ዘጠኝ ጦማርያን ምንም አይነት የሽብር ተግባር ላይ ተሰማርተን የማናውቅ መሆኑን ክሱም ሃሳባችንን በነጻነት ከመግለጽ ተግባራችንን ጋር ተያያዘ መሆኑን አጥብቀን እንደምናምን እያስታወስን መንግሰት ክሱን ሙሉለሙሉ ውድቅ በማድረግ የጉዳዩን ፓለቲካዊ አለመሆን አንዲያረጋግጥልን ጥሪ እናስተላለፍለን ፡፡
አሁንም ስለሚያገባን እንጦምራለን!

No comments: