Thursday, February 19, 2015

እውን ወያኔ ሐርነት ትግራይ የሚደነቅ የሚከበር ነገር አለውን?

February 19,2015
(ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው)
tplf addis
በእስካሁኑ ግፍ ያልጠፋኸው ነገር ግን ለማይቀርልህ ወገኔ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ! እንኳን ለአጥፊህ ለወያኔ ሐርነት ትግራይ 40ኛ ዓመት የልደት በዓል አደረሰህ! የዚህች ሀገር ነቀርሳ በውስጧ የበቀለበት 40ኛ ዓመት እነሆ ከነገ ወዲያ እሮብ የካቲት 11 2007ዓ.ም. ይከበራል፡፡
ግን ወያኔ ማን ነው? እውን የሚከበር የሚያኮራ ማንነት አለው? ነው ወይስ የሚረገምና የሚያሳፍር? ከዚህ ቡድን ውስጣዊ ታሪክ እንደምንረዳው ይህ ቡድን በርዕዮተ ዓለምና በአስተሳሰብ ልዩነት በግል ጥቅምና በሥልጣን ሽኩቻ አንዱ ሌላውን እየበላ አንዱ በሌላው እየተበላ እርስ በእርስ እንደ አውሬ እየተባላ እየተጠፋፋ በመጨረሻ በአውሬነቱ የበረታው የበረታው አስከፊው አስከፊው ቀርቶና ተቧድኖ ለዚህ የደረሰ እኩይ ሰይጣናዊ ቡድን ነው፡፡
የወያኔን የትግል ታሪክ ስናይ ከቀደምቶቹ የሕወሀት አባላት ጥለው ከወጡትም ካሉትም ከተገለሉትም በተለያየ ጊዜ በሰጡት ቃለ መጠይቆቻቸውና በጻፉት መጻሕፍቶቻቸው ላይ እንደተረዳነው ወያኔ እዚህ ለመድረስ ተጀምሮ እስኪጨረስ ድረስ አብዛኛውን ጊዜ ከዓረብ ሀገራት ከሸአቢያ በተለይም ከሱዳን ለሚያደርገው የትጥቅ ትግል ምድሯን እንደፈለገ እንዲጠቀምበት ፈቅዳ ለወያኔ መሸሻ መሸሸጊያ መሠልጠኛና መደራጃ የተለያዩ ዓይነት ድጋፍ እርዳታዎችን ያገኝ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ደርግ በበቀል 800ኪ.ሜ. ድረስ ወደ ሱዳን ዘልቆ እየገባ በጦር አውሮፕላን የሚደበድብበት ሁኔታ ነበር፡፡ ሱዳን ከወያኔ የምትፈልገው ብዙ ነገር ነበርና በወያኔ ትግል ወቅት ለወያኔ ብዙ ዋጋ ከፍላለች፡፡ ወደ ኋላ አካባቢ ደግሞ ወያኔ ድጋፍ እርዳታን ከአውሮፓና ከአሜሪካ ያገኝ ነበር፡፡
እነኝህ አካላት ሁሉ ሁሉን አቀፍ ድጋፍና እርዳታ ለወያኔ ሲሰጡ እንዲሁ በነጻ ያለ ጥቅም ከሱ የሚፈልጉት ነገር ሳይኖር አልነበረም፡፡ ሁሉም ከወያኔ እንዲሰጣቸው ወይም እንዲደረግላቸው የሚፈልጉትና ወያኔም ሊያደርግላቸው ቃል የገባላቸው የየራሳቸው ጥቅሞች አላቸው፡፡ የሚያሳዝነው ሁሉም እንዲደረግላቸው የሚፈልጉት ነገር ሁሉ የሀገራችንንና የሕዝቧን ብሔራዊ ጥቅሞችና ሉዓላዊነት በእጅጉ የሚጎዱ መሆናቸው ነው፡፡ እነኝህ አካላት የፈለጉት ምንም ከባባድ ነገር ቢሆንም ቅሉ ከራሱ ጥቅም የሚበልጥበት ምንም ነገር ለሌለው ለወያኔ የወንበዴ ቡድን ግን ኢምንት ነውና እንደየፍላጎቶቻቸው ተቀብሎ አስተናግዷቸዋል፡፡ ለምሳሌ የሱዳንን ብናይ ወያኔ የገባላትን ከጎንደር እስከ ጋንቤላ በ1600 ኪ.ሜ. እርዝመት ከ40 እስከ 60 ኪ.ሜ. ስፋት የሚያህልን ከአንዳንድ የአውሮፓ ሀገራት በእጅጉ የሚልቅ መሬት ከሀገራችን ቆርሶ በሰነድ ደረጃ አስረክቧታል፡፡ ይህ በሰነድ አረጋግጦ የሰጣትን መሬት ግን መሬት ላይ ተፈጻሚ አድርጎ ወደ ሱዳን ለመቀላቀል በተደጋጋሚ ተሞክሮ ከሀገሬው በተነሣ የቆረጠ ቁጣ ሌላ መዘዝ እንደሚያመጣበት ስለሠጋ የራሱን ምቹ ጊዜ እየጠበቁለት ይገኛሉ፡፡ ሸአቢያም ከሚፈልገው በላይ አሰብን ያህል ወደብ ከነምርቃቱ አግኝቷል፡፡ ቢዘረዘር ሐተታው ብዙ ነው ብቻ ሁሉም የየድርሻቸውን አግኝተዋል እያገኙም ይገኛሉ፡፡
እንግዲህ የታሪክ አተላዎቹ፣ የወራዶቹ፣ የደናቁርቱ፣ የባንዳ ውላጁ ሁሉና የደዳብቱ ኩራት ወያኔ “አይ! ይሄማ እንዴት ይሆናል? እናንተስ እንዴት ደፋሮች ብትሆኑና እንዴትስ ብትንቁን ነው ኢትዮጵያዊያን መሆናችንን እያወቃቹህ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄ የምትጠይቁን?” የሚልበት ጉዳይ አንዲት እንኳን ሳይኖረው የሀገሪቱን ብሔራዊ ጥቅሞች አሳልፎ በመስጠትና ለመስጠትም ቃል በመግባት በሀገር ክህደት ወንጀሎች እስከ አፍንጫው ተነክሮበት ነው ለዚህ ስኬቱ የበቃው፡፡ እኔን የሚገርመኝ በእነኝህ ሁሉ አካላት ሁሉን አቀፍ ድጋፍና ምቹ ሁኔታዎች ተደግፎ 17ዓመታትን ያህል ዘመን መፍጀቱ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ሕወሀት ምን ያህል ደካማ እንደነበረ ነው፡፡ ወያኔ ከጠላት ያገኝ የነበረውን ድጋፍና እርዳታ እርም ስለሆነ እሱን ተውትና እንዲያው ተገን ብቻ የሚሰጥ አንድ ጎረቤት ሀገር ቢኖርና በኢትዮጵያ አንድ ሌላ የከፋው ኃይል እንበል ለምሳሌ በወያኔ እስከ የዘር ማጥፋት ወንጀል ድረስ እየተፈጸመበት ያለው የአማራ ሕዝብ ይሄንን ዕድል ቢያገኝ 17 ዓመታት አይደለም መንፈቅ እንኳን የሚፈጅበት መሆኑ በጣም ያጠራጥረኛል፡፡ ወያኔ ይሄንንም ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ነው የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም አሳልፎ እየሰጠ ሉዓላዊነቷን እያስደፈረ ጎረቤት ሀገራትን በሙሉ በጥቅም ይዞ መሸሻ መሸፈቻ እንዳይኖር ዙሪያውን ያጠረብን፡፡
ሌላ እንደ ወያኔ ያለ የጥፋትና የክህደት ኃይል ኢትዮጵያ ውስጥ ቢኖርና ወያኔ በመጣበት የረከሰ የጎደፈ ነውረኛና ወራዳ መንገድ ለመምጣት ቢሞክር ላይሳካለት የሚችልበት ምንም ምክንያት የለም፡፡ ምክንያቱም ይህ ወያኔ የመጣበት መንገድ የመጨረሻ ደካማ የተባለ ኃይል ሁሉ ሊመጣበት የሚችልበትና ለስኬትም ሊበቃበት የሚችልበት የመጨረሻው መንገድ በመሆኑ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ የወያኔን የትግል ተጋድሎና ስኬት ሊያደንቅና ክብር ሊሰጥ እችል የነበረው ወያኔ ለግል ቡድናዊ ጥቅሙ ሲል የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም፣ ክብር፣ ሉዓላዊነት ለድርድር ሳያቀርብና እየቸረቸረ አሳልፎ ሳይሰጥ ውድ መሥዋዕትነትን ከፍሎ በጀግኖች በቆራጦች በአርበኞች በፋኖዎች መንገድ የመጣ ቢሆን ነበር፡፡ ነገር ግን ወያኔ በተፈጥሮው ጠባብ፣ እራስ ወዳድ፣ ወራዳ፣ ነውረኛ፣ ደንቆሮ፣ ርካሽ፣ ከሀዲ፣ የእፉኝት ልጅ፣ በፀረ ኢትዮጵያ ዓላማ የተመረዘ እኩይ የእርግማን ልጅ የአጋንንት ውላጅ ስለሆነ ማንም ያስገደደው ሳይኖር ከፊሎቹን ከያሉበት ድረስ እየሔደ ያላሰቡትን እያሳሰበ “እንዲህ ብታደርጉልኝ እንዲህ አደርግላቹሀለው” እያለ እየዞረ እየለመነ እየተማጸነ ይሄንን ዓይነት በአሳፋሪነቱ ተወዳዳሪ የማይገኝለትን ኢትዮጵያዊ ደም ካለው ፈጽሞ የማይጠበቅ በእጅጉ የራቀና ባዕድ የሆነ ወራዳና ነውረኛ መንገድ ፈጥሮ ሊመጣበትና ለስኬት ሊበቃበት ቻለ፡፡ በዚህ የወያኔ ነውረኛና ወራዳ ማንነት ሊኮራ የሚቃጣው ማንም ዜጋ ካለ ለበሽተኛነቱ ፈጽሞ አትጠራጠሩ፡፡ ለሀገር ለወገንም ቅንጣትም እንኳን የማይጠቅም ይልቁንም የሚያጠፋ ነውና አደራቹህን ሲያጋጥማቹህ እንደ እባብ እራስ እራሱን ቀጥቅጣቹህ አጥፉት፡፡
ወያኔ ከራስ ወዳድነቱ፣ ከጠባብነቱ፣ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” የአሕያ አስተሳሰቡ የተነሣ በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሀገራችንን እንደ ግል ንብረቱ በመቁጠር ስንትና ስንት ሊያገለግሏት የሚሹ የተማሩ የበቁ የነቁ የጠነቀቁ ምሁራን እያሏት “እኛን እስካልመሰለ ጊዜ ድረስ ሽ ጊዜ አዋቂ ምሁር ቢሆን አንፈልገውም፡፡ መርሖዋችንን እስከተቀበለ ጊዜ ድረስ ደግሞ መሀይምም ቢሆን በሚንስትር ደረጃ እንሾመዋለን” በሚለው በብዙኃን መገናኛ በአቶ መለስ በተገለጸው የአገዛዙ አቋም መሠረት ሥልጣንና ኃላፊነት የተባለን ቦታ ሁሉ በደናቁርት ልጆቹና አጋር ደጋፊዎቹ ጠቅጥቆ ሞልቶ ሀገሪቱ በሌላት አቅም ብዙ ነገር እየተበላሸባት እየባከነባት እየጠፋባት እየተበላባት ተምረው ላይማሩ ነገር መማሪያ መለማመጃ መቀለጃ መጫወቻ አድርገዋት ይገኛሉ፡፡ ይህ ሁሌም ሳስበው ድንቅ የሚለኝ የአገዛዙ አቋም ወያኔ ሳያፍር ሊያራምደው ሊሠራበት የቻለበት ምክንያቶች አንደኛ ሊደብቀው ባልቻለው ባለው ፈላጭ ቆራጭ ፀረ ዲሞክራሲ (በይነ ሕዝብ) እና ፀረ ሕዝብ ማንነቱ የተነሣ፣ ሁለተኛ ሊከውነው ሊፈጽመው የሚፈልገውን በየ ፈርጁ ያለውን ያሰበውን ፀረ ሕዝብና ፀረ ኢትዮጵያ የጥፋት ዓላማ ሊያስፈጽሙት ስለማይችሉ፣ ሦስተኛ ምሁራን ከጎናቸው ቢሆኑ በአላዋቂነታቸው መሸማቀቅ ሊሰማቸው የሚችለውን መሳቀቅና ሀፍረት በመፍራት ናቸው፡፡
tplf12በእነዚህ ምክንያቶች የተነሣ እያየነው እንዳለነው ሁሉ ሀገራችን የ4ኛ ክፍልና የ5ኛ ክፍል የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ ጄኔራሎች ሚንስትሮችና የሥራ ኃላፊዎች ያሉባት በ21ኛው መቶ ክ/ን ተገዳ በመሀይማን የምትመራ የዓለማችን ብቸኛ ሀገር ለመሆን በቅታለች፡፡ በዚህም የወያኔ የደነቆረና አንባገነናዊ አሠራር ምክንያት በገንዘብ ሊሰላ የማይችለው ቀርቶ በገንዘብ ሊሰላ የሚችለው በዚህች ሀገር የደረሰባት ኪሳራና ጉዳት ይሰላ ቢባል በትሪሊዬን (በብልፊት) ደረጃ የሚጠቀስ የገንዘብ መጠን ሊገልጸው መቻሉን እጠራጠራለሁ፡፡ ከዚህ የሚከፋው ጉዳትና ኪሳራ ግን በገንዘብ ሊገለጹ የማይችሉ የደረሱብን ጉዳትና ኪሳራዎች ናቸው፡፡ እንግዲህ ወያኔ ማለት ይሄ ነው እና ታዲያ ወያኔን በየትኛው ኢትዮጵያዊ ተፈጥሮውና ብቃቱ፣ ማንነቱ፣ ድንቅ ሥራው፣ ጽናቱ፣ ቁርጠኝነቱ መልካም ምግባሩ ነው ላደንቀው የምችለው? መች ጭንቅላቴ ላሸቀና? መች ታመምኩና? መች ማሰብ ተሳነኝና? መች ደነቆርኩና? መች ሆዴን አመለኩና? እነዚህ የወያኔ ርካሽና ወራዳ ማንነቶች እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ሊገለጽ በሚከብድ በማይቻል ስሜት እንድጠየፈው እንድንቀው ያደርጉኛል እንጅ ከቶ እንዴት ሆኖ በምን ተአምር ነው እንዳደንቀው እንዳከብረው የሚያደርጉኝ? ወያኔን ባሰብኩ ቁጥር ሀገሬን እንዴት ተሸማቃ ተጨንቃ ተሸብራ ተመሰቃቅላ እንደማያት ማን በነገረልኝ?
ወያኔ ሀገር አያውቅም ወያኔ ሕዝብ አያውቅም ለወያኔ ሀገሩ ትግራይ ናት ለወያኔ ሕዝቡ የትግራይ ሕዝብ ነው፡፡ ምንም እንኳን ወያኔ እየለፋ እየደከመ እየጣረ ያለው ለትግራይና ለትግራይ ሕዝብ ነው ይበል እንጅ ነገሩን ልብ ብለን ካየነው ግን የትግራይን ሕዝብ መቃብር ነው ተግቶ እየቆፈረ ያለው፡፡ የትግራይ ሕዝብ አልገባውም እንጅ ወያኔ እሱ በሥልጣን እስካለ ጊዜ ብቻ እንዲኖር አድርጎ ነው ሰይጣናዊ ሸር እያሴረበት ያለው፡፡ ወያኔ ሆን ብሎ በትግራይ ሕዝብ ስም በሌላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ግፍ በደልና ክህደት እየፈጸመ ፍጹም ኃላፊነት በጎደለው ተግባርና ጠላትነት ሕዝቤ በሚለው የትግራይ ሕዝብ ላይ ተግቶ በነፍሱ እየቀለደበት እየቆመረበትና ሴራ እየተበተበበት ይገኛል፡፡ ወያኔ “በእኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” አስተሳሰቡ ምክንያት እሱ የማይኖርባት ኢትዮጵያ ከመጣች ሊያፈራርሳት ቆርጦ ከጠዋቱ አስቦበት የጥፋት ሴራውን ሕገ መንግሥቴ በሚለው የፀረ ኢትዮጵያ ሰነዱ አስቀምጧል፡፡ ከዚህ ቀደምም እንዳልኩት ወያኔ ፀረ ኢትዮጵያና ሕዝቧ መሆኑን ከሚያጋልጡበት ድርጊቶቹ አንዱ ይሄንን አንቀጽ ሕገ ምንግሥቴ በሚለው ሰነዱ ማካተቱና በዚህም አጥፊ አስተሳሰቡ መሠረት ባሕረ ምድርን ማስገንጠሉ ነው፡፡ ይሄንን ጸረ ኢትዮጵያ ሰነዱን ለማጽደቅ የተደፋፈረው ለዚህች ሀገርና ሕዝብ ካለው የባዕድነትና የጠላትነትና የቅጥረኛነት ስሜቱ የነተሣ ነው፡፡ ይህ ወያኔ ኢትዮጵያን ለመበታተን ያሴረበት አንቀጽ በየትኛውም ሀገር ሕገ መንግሥት ወያኔ ባሰፈረው መልኩ ተቀርጾ አያውቅም፡፡ በገዛ ሀገሩ ላይ የሚያሴር ሕገ መንግሥት ተብየ የወያኔው የጥፋት ሰነድ ለዓለማችን ብቸኛውና የመጀመሪያው ነው፡፡
ወያኔ ልማት የሚባል ነገር አያውቅም ጥፋት እንጅ፡፡ ብዙ የዋሀን አሉ ወያኔ ልማት እየሠራ የሚመስላቸው፡፡ ለመሠረተ ልማት ዝርጋታ እያለ በሀገሪቱ ስም ዓለማቀፋዊ ደረጃውን የጠበቀ ሥራ ሊያሠራ የሚችል ብድርና እርዳታን ይወስድና አብዛኛውን መዝብሮ ይወስዳል ከአበዳሪዎቹ “የታለ የተሠራው?” መባሉ አይቀርምና ካልሠራም ሌላ ብድርና እርዳታ ማግኘት ስለማይችል ተመዝብሮ በቀረው በጥቂቱ የማይረባ ተመርቆ ለአገልግሎት ከመብቃቱ በፊት ውኃ ውስጥ እንደገባ ካርቶን የሚፍረከረክ መንገድ፣ ተገቢውን አገልግሎት መስጠት የማይችል የቴሌኮምና የመብራት ኃይል አገልግሎት ወዘተ. እየገነባ በብዙ ቢሊዮን (ብልፍ) የሚቆጠር ብድርና ዕርዳታ በማምጣት ሀገሪቱን ላልተገባና እጅግ ከአቅም በላይ ለሆነ በትውልደ ትውልድ ተከፍሎ ለማያልቅ ባለዕዳነት ዳርጓታል፡፡ ይሄም ወደፊት ብዙ ብዙ ብዙ መከራና ችግር ይዞ ይጠብቃታል፡፡
አሁን ወያኔ 40ኛ ዓመቱን እያከበረ ይገኛል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ ምን ታዘብኩ መሰላቹህ?  ከሦስት ወራት በፊት ወያኔ ቅሊንጦ አስሮኝ እያለ እዚያ ካሉ ከተለያየ የአስተሳሰብ ጫፍ ካሉ ወገኖች ጋር በሀገራችን ችግሮች ላይ ያተኮረ ያደረግነውን ውይይትና ክርክር ከቅሊንጦ ከወጣሁ በኋላ ኅዳር ወር ላይ “የሀገራችን ፖለቲካና ስሉጣን (አክቲቪስቶች) በቅሊንጦ” በሚል ርእስ በጻፍኩት ሦስት ተከታታይ ጽሑፍ ላይ ገልጨው ነበር፡፡ እዚያ ያደረግነውን ውይይትና ክርክር ባሰፈርኩበት ጽሑፍ ላይ ታዲያ እነዚህ ተወያይ ተከራካሪ ወገኖች ወያኔና ሌሎቹ የጥፋት ኃይሎች እጅግ በሚያሳዝን ሁኔታ ለእርኩሳዊ የጥፋት ዓላማቸው ሲሉ በአማራ ሕዝብ ላይ የሚያወሩትን ስም ማጥፋትና የፈጠራ ወሬ ይዘው ያነሡትን ስም ማጥፋት እያንዳንዷን ነቅሸ በማውጣት ሐሰት ስለመሆኑም በመረጃ አስደግፌ ካስተባበልኩ ካረጋገጥኩ በኋላ የአማራ ሕዝብ ለዚህች ሀገር ነጻነት ህልውና ሥልጣኔና ደኅንነት ዕድሜ ልኩን ምን ያህል መራራ መሥዋዕትነት ሲከፍል እንደኖረ፣ በዚህም ሳቢያ ዛሬ ድረስ ስር ለሰደደ ድህነትና መሰል ችግሮች መዳረጉን ዘርዝሬ በውይይቱ ላይ ያልኩትን የሚከተለውን ቃል አስፍሬ ነበር፡-
“እናም የወያኔ መርዘኛ የጥፋትና የፈጠራ ፕሮፖጋንዳ (ልፈፋ) እና ስብከት ሰለባ ስለሆንን እንጅ ጭንቅላት ቢኖረን፣ ወደ ኋላም ወደ ፊትም ደወ ግራም ወደ ቀኝም መመልከት ብንችል፣ አርቀን አስፍተን ጠልቀን ማሰብ ብንችል፣ ኢትዮጵያዊነቱ ቢሰማን፣ የሀገራችንንና የሕዝቧንም ህልውና የምንፈልግ የምንመኝ የምንወድ ብንሆን በምንም ተአምር ያውም በሐሰተኛ ወሬ ለአማራ ጥላቻ ሊያድርብን አይችልም ነበር፡፡ ለዚህች ሀገርና ሕዝብ ህልውናና ነጻነት አማራ ለከፈለው ገደብ የለሽ መራራ ዋጋና መሥዋዕትነት እናመስግነው ብንል ለምስጋናችን ተስተካካይ ቃል ፈጽሞ ልናገኝለት አለመቻላችንን በሚገባ በተረዳን ነበር፡፡ ከፍለን ልንጨርሰው የማንችለው ዕዳ እንዳለብን በተረዳን ነበር፡፡ አማራን ልንጸየፍ ልንጠላ አይደለም ወደነውም ለፍቅራችን የልባችን ባልደረሰ ነበር፡፡ ውግዘትና ጥላቻውን ትተን ክብር በሰጠነው በኮራንበትም ነበር፡፡ ለዚህ ነው ለአማራ ያለው የጥላቻ መንፈስ መሠረቱ ድንቁርና፣ ጠባብነት፣ የሀገር ጣላትነትም ነው ያልኩት” ብየ፡፡
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
ታዲያ እላቹህ ወያኔ ይህችን እንዳለች ቀዳላቹህና አማራ የምትለዋን አውጥቶ የትግራይ ሕዝብ የምትለዋን ተካላቹህና በአቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ የሕወሀት 40ኛ ዓመት የእንኳን አደረሳቹህ መልእክት ላይ አስገብቶ እንዲያነቧት አደረገ፡፡ አይገርማቹህም? አየ ወያኔ! በዚህ እንቋጭ አውቃለሁ ወያኔ በርካታ ለጆሮ የሚከብድ ጉድ እንዳለበት የሙስናውን የተለያየ ዓይነቱን ግፉና በደሉን ሁሉ እንዘክዝክ ካልን በዓመትም የሚያልቅ አይመስለኝም፡፡
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

No comments: