Saturday, February 14, 2015

የ2007ቱን ሀገራዊ ምርጫ ሂደት እና ከምርጫዉ ዉጭ ያሉ አዋጭ አማራጮችን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የአቋም መግለጫ

February 14,2015

pg7-headerአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሰላማዊ፣ ተዓማኒና ፍትሀዊ በሆነ ምርጫ የማይፈልጋቸውን መሪዎች መሻር፤ የሚፈልጋቸውን ደግሞ መሾም የሚያስችሉትን መሠረቶች ለመጣል የሚታገል ንቅናቄ ነው። እንደሚታወቀው የሕዝብ እውነተኛ ፍላጎት የሚገለጽበት እውነተኛ ምርጫ እንዲኖር ገለልተኛና ቀልጣፋ የፍትህ ሥርዓት፣ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት ሊኖሩ ይገባል። ነፃ የሚዲያ ተቋማትና በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የሲቪክ ማኅበራት መኖርም መታለፍ የሌለባቸው አቢይ ጉዳዮች ናቸው። አማራጭ ፓሊሲዎችን ማቅረብ የሚችሉ በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የፓለቲካ ፓርቲዎች ከሌሉም አማራጮች የሉምና ምርጫ ትርጉም የለውም። ይህ ሁሉ ቢሟላ እንኳን ምርጫውን የሚያስፈጽመው አካል ገለልተኛ፣ ሀቀኛና ተዓማኒ ካልሆነ የሚደረገው ምርጫ የመራጩን ሕዝብ ፍላጎት የሚያንፀባርቅ ሊሆን አይችልም።
ከላይ የተዘረዘሩትን የምርጫ እሴቶች ሙሉ በሙሉ ባይሆንም እንኳን የተወሰኑትን በመጠኑም ቢሆን ያካተተ ምርጫ እንዲኖር መጣርና በሂደት የምርጫውን አፈፃፀም ማሻሻል ይቻል ይሆናል በሚል እምነት የዲሞክራሲ ኃይሎች በህወሓት የሴራ ምርጫዎች ሲሳተፉ ቆይተዋል። ሆኖም በህወሓትና በእውነተኛ ምርጫ መካከል ያለው ተቃርኖ እያደር እየሰፋ ሲሄድ እንጂ ሲጠብ አልታየም። በህወሓት ሙሉ ቁጥጥር ስር በሚካሄድ ምርጫ ኢትዮጵያን የሚጠቅም ለውጥ ሊመጣ ይችላል የሚለው እምነት ለአርበኞች ግንቦት 7 ፈጽሞ የተሟጠጠው ከምርጫ 97 ማግስት ጀምሮ ነው። በግንቦት 7 ቀን 1997 ዓም የኢትዮጵያ ሕዝብ በታላቅ የለውጥ ተስፋ የሰጠው ድምጽ በህወሓት የተዘረፈው ከላይ የተዘረዘሩት ተቋማት ያልነበሩ በመሆናቸው፤ ስለዚህም ከምርጫ በፊት ተቋማቱን መገንባት፤ ተቋማቱን ለመገንባት ደግሞ ህወሓትን ከስልጣን ማስወገድ ይገባል ብሎ በማመኑ ነው አርበኞች ግንቦት 7 በሁለገብ የትግል ስልት በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘው።
ያም ሆኖ ግን በምርጫ ላይ ያላቸው ተስፋ ፈጽሞ ያልተሟጠጠ ፓርቲዎችን በማክበርና ሥራቸውንም አስቸጋሪ ላለማድረግ ሲባል ከምርጫ 97 ወዲህ የነበሩ ብሄራዊም ሆነ ክልላዊ ምርጫዎችን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምርጫ ዉጭ ያሉ ሌሎች አማራጮችን ብቻ እንዲመለከት አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ አድርጎ አያውቅም ነበር። አሁን ግን የአገራችን ኢትዮጵያ የፓለቲካ ሁኔታዎች ይህንን የቆየ አቋም በሚያስቀይር መንገድ፤ የአገራችንን የወደፊት ዕድል ብቻ ሳይሆን ባጠቃላይ ያካባቢውን ሰላም በሚጎዳ መልኩ ተቀይሯል። የሰሞኑ የወያኔ እርምጃዎች ትንሽ ተስፋ ያደርግ የነበረውን የዴሞክራሲ ወገንተኛ ተስፋም እምሽክ አድርጎ በልቶታል:: እየተቃረበ ያለው ዓይነት የፌዝ ምርጫ ወያኔ እንደ እንጄራ የራበውን የተቀባይነት እጦት ለአጭር ጊዜ ያስታግስለት ይሆናል እንጂ የሀገሪቱን እያደር እየተወሳሰበ የመጣ ችግር ለጊዜውም እንኳን የሚያስታግስ አይሆንም፤ ይልቁንም ጊዜው በገፋ ቁጥር ችግሩ መቋጠሪያ የጠፋው እየሆነ ይሄዳል::
የሁኔታውን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር የወቅቱን የአገራችን የፓለቲካ ሁኔታ በጥንቃቄ መርምሮ የሚከተሉት ግንዛቤዎች ላይ ደርሷል።
1. ህወሓት ብዙዎች እትዮጵያዊያን የተሰውላቸውን አንድነት ፓርቲንና መኢአድን በመበተን የድርጅቶቹን ስምና ንብረት ለአገልጋዮቹ መስጠቱ፤ ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው የመራጭን ድምጽ መስረቅ ሳይበቃው የምርጫ ተወዳዳሪንም መዝረፍ መጀመሩን አመላካች ነው። ይህ ተግባር ህወሓት የምርጫ ውጤትን ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችንም እሱ ራሱ ለመምረጥ መወሰኑን ያሳያል፤ ከዚህ በተጨማሪ የሴራ ምርጫውን ከጅምሩ ጀምሮ አስቀድሞ እስከተወሰነለት መዳረሻው ድረስ ለምንም ዓይነት ያልተጠበቀ አጋጣሚ (በምርጫው ወቅት የሚደረጉትን ክርክር ተብዬዎች ጨምሮ) እድል ላለመስጠት ወስኖ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በግልጽ ያሳያል፤
2. ይህ እኩይ ውሳኔ በምርጫ ቦርድ ፊርማና አንደበት ቢነገርም ምንጩ የህወሓት ፓሊት ቢሮ መሆኑን የሚከተሉት ተግባራት ይጠቁማሉ፤
2.1. በምርጫ ቦርድ በኩል እንዲገለጽ የተወሰነው እርምጃ ለማስመሰል ያክልም ቢሆን የህጋዊነት ሽፋን እንዲኖረው አለመደረጉ ውሳኔው ፍጹም እብሪተኛ በሆነ አካል መወሰኑን ያመለክታል። እንዲህ ዓይነቱ እብሪተኛ አካል ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ነው። ውሳኔውን ለማስፈፀም የነበረው ጥድፊያም ይህንኑ ያጠናክራል።
2.2. ለማስመሰያ ያክል እንኳን ምንም አይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሳይኖር ፓሊስ የአንድነትና የመኢአድ ቢሮዎችን መውረሩ፤ ህወሓት አንድነትንና መኢአድን አጥፍቶ የድርጅቶቹን ስሞችና ንብረቶች ለሚፈልጋቸው ሰዎች ሰጥቶ በአስቸኳይ ለምርጫ ድራማው በፊት መስመር ሊያሰልፋቸው መወሰኑን አመላካች ነው። እንዲህ ዓይነት ከባድ ውሳኔ የሚሰጠው ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ብቻ ነው።
2.3. ወደ ፈቃድ መንጠቅ ከመደረሱ በፊትም በሰማያዊ ፓርቲ፣ በአንድነትና በመኢአድ አባላት የደረሰው አረመኔያዊ ድብደባ፤ ንቁ የፓለቲካ ተሳትፎ የሚያደርጉ ዜጎች ላይ የሚደርሰው እስር፣ መሰወርና እና ባልታወቁ ሰዎች ተገድሎ መገኘት መብዛት እነዚህን አገራዊ ፓርቲዎች የመበተን የፓለቲካ ውሳኔ መሰጠቱን አመላካቾች ናቸው።
3. ለጊዜው የፈቃድ ነጠቃና የንብረት ዘረፋ የተፈፀመው በአንድነትና በመኢአድ ላይ ቢሆንም በሰማያዊ ፓርቲ ላይ በየእለቱ እየጠነከረ የመጣው የአፈና እርምጃም በተመሳሳይ ፓርቲውን ወደማገድ አለዚያም ፈጽሞ መንቀሳቀስ ወደማይችልበት ደረጃ ሊያደርሰው ይችላል የሚል እምነት አሳድሯል። ሌሎች ፓርቲዎችም ከዚህ ህወሓት ካሰመረው የውሸት ጫወታ መስመር የመውጣት ዝንባሌ ቢያሳዩ ተመሳሳይ እርምጃ አይቀርላቸውም።
4. የህወሓት የወቅቱ የጥፋት ዒላማ ያነጣጠረው አንፃራዊ በሆነ መንገድ የተሻለ መዋቅርና ማኅበራዊ መሠረት ባላቸው እና በአገራዊ አጀንዳዎቻቸው በሚታወቁ ፓርቲዎች ላይ መሆኑ፤ የወቅቱ የጥፋት ዘመቻ የኢትዮጵያ አንድነትን የማዳከምና ከፋፍሎ የመግዛት የህወሓት ትልቁ አጀንዳ አካል መሆኑን ያሳያል።
5. እራሱን በዘር ያደራጀዉና ኢትዮጰያ ዉስጥ ያለዉ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ አደረጃጀት ከዚሁ እሱ ከተደራጀበት የዘር አደረጃጀት ዉጭ እንዲሆን በፍጹም የማይፈቅደዉ የወያኔ አገዛዝ፤ መጣፊያው ሲያጥረውና ወደ ማይቀረው ውድቀቱ ሲያመራ፤ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል እንዳለችው አህያ አገራችን ኢትዮጵያን በቀላሉ ወደማትወጣዉ የዘዉግ ግጭት ዉስጥ አስገብቶ ዘመናት ያስቆጠረዉ አንድነቷ እንዲፈረስ በትጋት እየሠራ መሆኑን ያሳያል።
6. ከመለስ ዜናዊ ሞት ወዲህ ህወሓት ከሁሉን ጠቅላይ (totalitarian) አገዛዝ ወደ ፋሽስታዊ ቡድንነት ያሽቆለቆለ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ህወሓት ዘረኛ፣ ጠቅላይና ፈላጭ ቆራጭ ጨቌኝ በመሆኑ ፋሽስት ብለነዋል። ሆኖም በታሪክ የሚታወቁ ፋሺስታዊ አገዛዞች ከፍተኛ ብሄራዊ ስሜት የነበራቸው ሲሆን የህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝ ግን ብሔራው ስሜት አልባ መሆኑ ልዩ እና የበለጠ አደገኛ ያደርገዋል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን የህወሓት መሪዎችንና ጥቂት ሌሎች አጫፋሪዎቻቸውን የያዘ ለጊዜው አስተባባሪ መሪ የሌለው ሆኖም ግን የጦር ሠራዊትን፣ የስለላ መዋቅሩንና ፓሊስን ተቆጣጥሮ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያን እየገዛ ያለው ይህ አስኳል የለሽ ፋሽስታዊ ቡድን መሆኑ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን ተደላድሎ መሪ እንዲፈጥር ከተፈቀደለት አገራችንን የከፋ መከራ ውስጥ ሊከታት እንደሚችል ግንዛቤ ተወስዷል።
ከላይ በአጭሩ ከተራ ቁጥ 1 እስከ 6 የተዘረዘሩትን በማገናዘብ በግንቦት 2007 ሊደረግ የታቀደውን አምስተኛው ዙር ሀገር አቀፍ የሴራ ምርጫን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7 አመራር ውሳኔዎችን አስተላልፎ ከዚህ የሚከተሉት ጥሪዎችን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አቅርቧል።
1. በምርጫ 2007 መሳተፍ ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ ሁኔታዎችን ከማመቻቸት ይልቅ ፋሽስታዊውን ቡድን የሚያጠናክርና የኢትዮጵያን ሕዝብ የወደፊት ዕድል የሚገድል በመሆኑ፣ ለፍትህ፣ ለነፃነት፤ ለዲሞክራሲና ለአገር አንድነት ግድ ያላቸው ወገኖች ሁሉ ከአሁኑ ከዚህ የይስሙላ ምርጫ ዉጭ ዓይኖቻቸውንና ሙሉ ጉልበታቸዉን በሌሎች የኢትዮጵያን ሕዝብ ነፃነት በሚያፋጥኑ አማራጮች ላይ እንዲያሳርፉ ጥሪ ያደርጋል። አርበኞች ግንቦት 7 የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ ዓይን ያወጣ የሴራ ምርጫ ይልቅ መብቱን፤ ነፃነቱንና እኩልነቱን በሚያፋጥኑለት በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመፅ የትግል አመራጮች ላይ እንዲሳትፍ ለመላው ያገሪቱ ሕዝብ ጥሪ ያስተላልፋል። ህወሓት ማኅበረሰባችንን ለመከፋፈልና ለማባላት የሚያደርገውን እኩይ ሴራ በጋራ እንድናከሽፈው ወገናዊ ጥሪ ያስተላልፋል፤ “አንከፋፈልም፤ ተከፋፍለንም አንጠቃም“ እንበል ይላል::
2. ህወሓትን ማስወገድ የሚቻለው በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ በመሆኑ፤ ከሁለቱ አንዱንም አለመያዝ ሌላ ሰው ታግሎ ነፃነቴን ያቀዳጀኝ እንደማለት የሚቆጠር በመሆኑ፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በአፋጣኝ ከእነዚህ ሁለት የትግል ዘርፎች ዉስጥ የተሻለ አስተዋጽኦ አበረክታለሁ በሚለው የትግል ዘርፍ ውስጥ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪ ያቀርባል።
3. አርበኞች ግንቦት 7፣ በሁለቱም የትግል ዘርፎች ድርጅታዊ መዋቅሩን እያሰፋና ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በመተባበር በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ ህወሓትን ከስልጣን ለማስወገድ አቅዶ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ኢትዮጵያዊያን በስፋት እንዲቀላቀሉት፤ በኅብረት እንድንቆም እና የህወሓትን ውድቀትና የኢትዮጵያን ትንሳኤ እንድናፋጥን ጥሪ ያደርጋል::
4. ያለንን አቅም በሙሉ ህወሓትን በማስወገድ ላይ ካዋልነው አንድ ጠንክር ያለ ሕዝባዊ አመጽ አገዛዙን ሊያፍረክርክው የሚችል በመሆኑ፤ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ከምርጫ ጋር ለተያያዙ ሥራዎች ሊውል ታስቦ የነበረው የሰው ኃይል፣ ጊዜ፣ ገንዘብና እውቀት ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀሻነት እንዲውል ጥሪ ያደርጋል።
5. በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንም በ2007 ምርጫ ላይ ጊዜና ንብረት ከማባከን ይልቅ በአንድ ልብ በኢትዮጵያ ውስጥ ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀስ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ ጥሪ ያደርጋል። ከሁሉም ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች የተውጣጣ አካል የዚህን ጥሪ ተፈፃሚነት እንዲከታተል ቢደረግ ይበልጥ ውጤታማ ይሆናል ብሎ ያምናል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ
ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ

No comments: