Tuesday, February 10, 2015

የአልፋ ቀራኒዮ አንደኛ ደረጃ ት/ቤት ተማሪዎች ክፍል ጥለው መውጣታቸው ተገለጸ

February 11.2015
• ‹‹የተማሪዎች ጥያቄ የእኛም ጥያቄ ነው›› መምህራን
ዳይሬክተራችን ያለ አግባብ ተነስቶብናል ያሉ ዓለም ባንክ አካባቢ የሚገኘው የአልፋ ቀራኒዮ አንደኛ ደረጃ ት/ቤት ተማሪዎች ክፍል ጥለው ከግቢ መውጣታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ዳይሬክተራቸው ለትምህርት ቤቱ አስተዳደር ባለመመቸቱ ከቦታው እንደተነሳ የገለጹት ተማሪዎቹ ዛሬ የካቲት 2/2007 ዓ.ም ጠዋት ላይ ‹‹በዳይሬክተሩ ጉዳይ እንድታነጋግሩን እንፈልጋለን፡፡ እኛ የምናውቀው ምንም ስህተት እንደሌለበት ነው፡፡›› ብለው ሲጠይቁ የትምህርት ቤቱ ስራ አስኪያጅ ‹‹ስለዚህ ጉዳይ እናንተ አያገባችሁም፡፡ ከፈለጋችሁ ተማሩ፡፡ ካልፈለጋችሁ ለቃችሁ መውጣት ትችላላችሁ፡፡›› እንዳሏቸው ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የአልፋ ቀራኒዮ አንደኛ ደረጃ መምህር ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
በተለይ የ7ኛ 8ኛ ክፍል ተማሪዎች ጥያቄያቸው ካልተመለሰላቸው መማር እንደማይፈልጉ በመግለጻቸው በሩ ተከፍቶ ከግቢ እንዲወጡ ተደርገዋል ተብሏል፡፡ ተማሪዎች ከትምህርት ቤቱ ግቢ ወጥተው ውጭ መቆማቸው ተከትሎም ግጭት ይፈጠራል የሚል ስጋት እንደተፈጠረ መምህራኑ ገልጸዋል፡፡
‹‹ርዕሰ መምህሩ ከተማሪዎችና ከመምህራን ጋር ተግባብቶ በመስራቱ ለትምህርት ቤቱ አስተዳዳሪዎች ስላልተመቸ እንጅ ያጠፋው ጥፋት የለም፡፡ የተማሪዎች ጥያቄ የእኛም ጥያቄ ነው፡፡ ሆኖም የርዕሰ መምህሩ ጉዳይ ብቸኛ ችግራችን አይደለም፡፡ ትምህርት ቤቱ በበርካታ ችግሮች የተተበተበ፣ ለመምህራንና ተማሪዎች የማይመች ትምህርት ቤት ሆኗል፡፡›› ሲሉም መምህራኑ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡

No comments: