Wednesday, February 4, 2015

ፍትህ እና ርትዕ ለሁሉም ( ቢኒያም ግዛው ከኖርዌይ ኦስሎ)

        

  በኢትዩጵያ ውስጥ ከሁለት አስርት አምታት ወዲህ በህዝብ ላይ በጣም  እየተንሰራፋ ስለሚገኘው የዘረኝነትን ተህዋስ ሳስብ በአንድ ወቅት በእስራኤል ያሉ አይሁዳውያን ያደረጉት አድሎ እና ወገናዊነት በአዕምሮዬ ይመጣል። ሁሉም ለፈለጉት ብቻ ነበር ጥብቅና የቆሙት።የሌላውን ሀዘን እና መከራ ከመጤፍ ሳይቆጥሩት በርባን!በርባን!በርባን! እያሉ በንጉሱ በር ላይ የራሳችው ወገን ብቻ እንዲፈታ አቤቱታቸው ታልቅ ነበር። ኢየሱስን አሳልፈው  ለፍርድ ሰጥተውት የራሳቸው ወገኔ የሚሉት እንዲፈታ በታላቅ አድማ ድምፃቸውን ያሰሙ ነበር።   በዚያን ጊዜ በርባን የሚባል ታወቂ እስረኛ ነበራቸውና  መፈክራችው ሁሉ እሱን የሚያወሳ ነበር።  በወቅቱ ፈራጅ ወደሆነው ቀርበው አድሎ የተሞላበት ጥያቄያቸውን አቀረቡ ገዥውም ጥያቄውን ከሰማ በኋላ እንዲህ አላቸው፥ ከሁለቱ ማንኛቸውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ አላቸው? እነርሱም በርባንን አሉ።   

       ይህ ነው አድሎ። ይህ ነው መለያየት።  ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? አሁን የደረስንበትም   ዘመን ይህንን መስሏል ። ሁሉም ቢጤዬ ለሚለው ለራሱ ፈርጆ ማድላቱ እና ለታሰረበት ሲጮህ የሌላውን ወገን አልባ መሆን ማታሰርና መንገላታት በስራህ ያውጣህ ጆሮ ዳባ ልበስ ካለው የአንድነት እና የመቀባበል ልብ ጠፍቷል ማለት ነው።           

  እንግዲያስ ትግሉ ለማን ነው?ለግለሰብ?ለፓርቲ?ለብሔራችን? ወይስ ለኢትዮጵያ ? ሚዛኑን ሳታዳሉ ምላሽ ስጡብት ። ተለያይቶ በየሰፈራው ለራስ ወግኖ እታገላለሁ ማለቱ የወያኔን እድሜ ቢያረዝም እንጂ ለኢትዮጵያ  ምንም  አይበጃትም።ወያኔ ለራሱ ብቻ ወግኗልና 23 አመታት አስቆጥሮ ሀገሪቷን ወደሚቀጥለው ረመጥ ይዞ 24 ለማለት የብቀላ አየሩን ወደውስጥ እየሳበ ነው። ሌላ የጨለማ ጉዞ።

                   እርስ በርሷ የምትለያይ መንግስት አትጸናም እንደተባለ ኢትዮጵያን በሁሉ አቅጣጫ ሸንሽኗት ይገኛል። ጎሳው፣ ክልሉ ፣ ብሔሩ፣ ፖለቲካው፣ የእምነት ተቋማቱ፣ ሚዲያው ወ.ዘ.ተ. . .  በሌላውም የኢትዮጵያ ጉዳይ ሁሉ ይህ አስከፊ የወያኔ የመለያየት መርዝ እንደ ተስቦ በሽታ በምድሪቷ ላይ ተረጭቷል። ማምከኛው ደግሞ አንድነት ብቻ ነው። የተባበረ ክንድ!           

        ወያኔ ኢትዮጵያን በአንድነቷ ሊገዛት ስለማይችል ከሰሜን አንስቶ ደቡብ ድረስ ከምስራቅ ጀምሮ እስከ ምእራብ ገንጥለህ እና ለያይተህ ግዛ በሚለው መርሁ ትውልዱ ቤተሰብ ሆኖ ሳለ እርስ በእርስ እንዳይቀባበል የጎጠኝነት እና የባይተዋርነት መንፈስ እየዘራበት ይገኛል። ውጤቱም ደግሞ እየተስተዋለ ነው። ይህን ለሚያህሉ አመታቶች በአንባገነንነት ምድሪቷን ሲመዘብር እና ወያኔ የራሱን ሆድ ሲያጠረቃ ከተጠቀመባቸው የውንብድና እና የማጭበርበርያ ስልቶቹ መሀል አንደኛው ኢትዮጵያውያንን እንደ ቅርጫ አጥንት መከትከት እና መቆራረጥ ነው። እናም ይህ የመለያየት መተት እና አዚም ብዙዎችን ለያይቶ ለኢትዮጵያዊነት ሳይሆን ለፓርቲ፣ ለግለሰብ፣ ለክልል፣ ለጎሳ ፣ ለእምነት ቤት፣ ወ.ዘ.ተ. . . ዘብ መቆም ብዙ ቦታ እየተስተዋለ የመጣ ጉዳይ ሆኗል ። ይህም በየስፍራው ያለው ልዩነት ወያኔን በግፍ አገዛዙ እስካሁን እንዲዘልቅ  አግዞታል።       

        በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የጭቆና አገዛዝ የነዳዳቸው ታጋዮች ጥቂቶች  አይደሉም ። በገዢው ቡድን የኢትዮጵያ ጠላት ወያኔ አማካይነት ደብዛቸው እና ስማቸው የጠፉት በብዙ ሺህ ይቆጠራሉ። ለአመታት ያህል በአሰቃቂ ሁኔታ ከታጎሩበት እስር በነጻ እንኳን ቢለቀቁ የአዕምሮ፣ የአካል፣ ህሙም ሆነው አሊያም ከተቀበሉት ሰቆቃ አንጻር በመሀላ ወያኔን አትድረስብኝ አልደርስብህም በማለት በአይነ ቁራኛ የሚጠበቁ ይሆናሉ።  

                ወያኔ ስላሰራቸው ሲናገር ወንጀልኞችን እና አሸባሪዎችን እንጂ ማንንም ጋዜጠኛም ሆነ የፖለቲካ እስረኛ የለኝም ማለቱን ከእውነታው ጋር ሲነጻጸር አንገት የሚያስደፋ ውሸት ሆኖ እናገኘዋለን።ፀሀይ ያሞቀው የውሸት ቋንጣ።ነገር ግን ስለታሰሩት ያለው እውነታ ሌላ ነው። በፀለምት፣ ወልቃይት ፀገዴ፣በቃሊቲ፣ ሸዋ ሮቢት፣ ዴዴሳ ፣ብርሸለቆ እና ዝዋይ የንፁህ ኢትዮጵያውያን ደም እምባ በምድሪቷ ላይ ድምፁን እያሰማ ይገኛል።  እስር ቤቶቹ ሁሉ በጋዜጠኞች እና ሀገር ሊቀና የሚችል እውቀት ባካበቱ ምሁራን ታጭቋል። ስለዚህ የታሰሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው። የታሰሩት ሁሉም ናቸው! ከሁሉም ናቸው! ለሁሉም ናቸው። በሀገራችን ላይ ማንኛውንም ነገር በቀናነት ለማድረግ መብት ከሌለን ሀገር አልባ ነን ወይም ታስረናል ማለት ነው። በእስር ቤት ውስጥ አርፈህ ከተቀመጥህ ትበላለህ፣ ትተኛለህ ፣ትፀዳዳለህ ሌላ ትርፍ እርምጃ ለማድረግ ሀሳብ እንዳለህ ከተነቃብህ ፊደል ያልቆጠሩ የወያኔ ስልጡን ገራፊዎች ይገለብጡሀል። በከተማ ውስጥ ሰለተቀመጥህ ነፃ ነህ ማለት አይደለም አሊያም ነፃ መሆንህን ማረጋገጥ ካስፈለገህ እውነቱን በአደባባይ ቆመህ ተናገር ያን ጊዜ የት እንዳለህ ይገለፅልሀል። ለዚህ ነው ኢትዮጵያ ታስራለች ብለን የምንናገረው።  የእኛም  መለያየት  ወያኔ እየቆመረ እንዲቀጥል አስችሎታል።

          በወያኔ ግዞት ውስጥ በስቃይ ስላሉት ስናስብ ወደ አዕምሮአችን የሚመጡት ኢትዮጵያዊያን ናቸው ወይስ ግለሰቦች? ከታሰሩት ውስጥ የነማን ይፈቱ? የየትኞቹ የብሔር ነፃነት ታጋዮች አሊይስ የቱ ተቃዋሚ ፓርቲ? ቀደምት የነበረው ወይስ መጤው? ለማን አቤት እንበል? መልሱ ግራ የሚያጋባ አይደለም። ለኢትዮጵያውያን ነው መሆን ያለበት። በአንድነት፣ በመጣመር፣በመያያዝ ለኢትዮጵያ ሉአላዊነት ለአንድ አላማ መሰለፍ።

             ከቶውንም ኢትዮጵያዊ ባርያ ሆኖ አያውቅም። ሀገራችን በጄኔቫ የዓለም መንግሥታት ማህበር ጠቅላላ ስብሰባ ላይ እንደ አውሮፓ አቆጣጠር መስከረም28 ቀን 1923 የመንግሥታቱ ማህበር ሃምሳ ሰባተኛዋ አባል ሆና መመዝገቧ በይፋ ታወጇል ።በዓለም መንግሥታት ማህበር መድረክ የክብር ቦታ ተሰጣት።ታዲያ ዛሬ ላይ ቆመን ይህንን የዚያን ዘመን ጀግንነት ስናስታውስ በፍፁም ቅንነትና የዋህነት የተሞላ ዕምነታቸውንና ተስፋቸውን ስናነብ የደማቸው ጩኽት እያስተጋባብን ማናችን የዚህ ዘመን ትውልድ ነን የዜግነት ግዴታን ቢያንስ ከእነሱ በተሻለ ለመወጣት  የሞራል ብቃት ያለን?           

    ዳር ድንበር የተጠበቀበት ከፋሺስቶች ጉልበት በላይ የተጎለበተበት ያንን  የመሰለ ለጥቁሩ ህዝብ ኩራት ሆኖ ወራሪው በተራው ያፈረበት እና ያጎነበሰበት ክንድ አሁንም በአንድነት አዲሱ ትውልድ ወያኔን ድባቅ ለመክተት ሊቀሰቀስ ይገባል።  ለፋሺስት ፀጉረ ልውጥ ወታደር ያልተበገረ ወኔ አሁንም በአንድነት በታላቅ እንቢተኝነትን እና አመፅ  የተሞላ ትግል  ያሻዋል። እንሔድብት ዘንድ ወያኔ አንጋዶ ያሰመረልን መስመር አሰናከለን፣በተነን፣ለየን እንጂ ለእድገት አላራመደንም።ስለዚህ በአንድነት በቁጣ እንነሳ ።

               ድምፃችን ይሰማ!!! ለአንዱ ብቻ አይደለም ለሁሉም ፍትህ እና ነፃነት  ይገባል። ሰሜኑ ፣ ደቡቡ፣ ምዕራቡ እና ምስራቁ በየክልሉ ያለው የተለያየ ቋንቋ እና ባህል ሲደመር ነው ኢትዮጵያ የሚባለው።ስለዚህም ለሁሉም መጮህ አለበት። የታሰሩት የፖለቲካ እስረኞች ሁሉም ይፈቱ። በአንድነት ለአንድ ትግል ለአንዲት ኢትዮጵያ እንቁም።  

               ወያኔ ኢትዮጵያን ሊለቅ ይገባል።ሀገርን ቀምቶ በህዝብ ከርሰ ልብ ውስጥ ያለውን ሰላም ስርቆ ደስታን ወደ ሀዘን የለወጠውን የኢትዮጵያ ጠላት ለመፋለም  የጀግና ልጅ ሆይ ተነስ ከወያኔ ረገጣ ኢትዮጵያን ነፃ ለማውጣት ያባቶችህ ወኔ እና አደራ ይጥራህ። 

ድል ለኢ ት ዮ ጵ ያ  ህዝብ !!!!                       
እናቸንፋለን!!!  Biniam Gizaw  Norway

No comments: