Friday, October 4, 2013

ለሕዝባዊ ተቃውሞ የወያኔ ፈቃድ የማይጠየቅበት ቀን እንዲመጣ እንታገላለን!!!


         
መስከረም 19 ቀን 2006 ዓ.ም. አንድነት ለዲሞክራሲና ፍትህ ፓርቲ ከሌሎች በርካታ ፓርቲዎች ጋር በመተባበር የጠራው ሕዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዷል። ይህ ሕዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ከዝግጅቱ እስከ ፍፃሚው ብቻ ሳይሆን ከፍፃሚው በኋላም በድርጊቶች የታጀበ ነበር።


ወያኔ ለሰልፉ እውቅና ሰጥቶ እያለ “መቀስቀስ አይቻልም፤ ፓስተር መለጠፍ አይቻልም፤ በዚህ ማለፍ፣ በዚያ መዞር አይቻልም” እያለ የፓርቲው መሪዎችን፣ አባላትንና ደጋፊዎችን ሲያስር፣ ሲፈታ፣ ሲያዋክብ ሰንብቷል። ይህም ሆኖ ግን የፓርቲ መሪዎች፣ አባላትና ደጋፊዎች ወከባውን ተቋቁመው ሰላማዊ ሰልፉን መጀመር ቻሉ።

ወያኔ ሰልፈኛው ወደ መስቀል አደባባይ እንዳይደርስ የለመደውን ጉልበት ተጠቀመ። ከተለያዩ አቅጣጫዎች ይተሙ የነበሩ ሰላማዊ ሰልፈኞች እንዳይገናኙ በፓሊሶች ታገቱ። ኢትዮጵያ ውስጥ አፈና የደረሰበት ደረጃ ጎልቶ ታየ። ሰልፈኛው ሊደርስ ያሰበው ቦታ – መስቀል አደባባይ – መድረስ ሳይችል ቀረ። የሰልፉ አስተባባሪዎች የነበሩበት ብዛቱ በመቶ ሺህ የተገመተ ስብስብ ሊደርስ በቻለበት ቦታ የመዝጊያ ሥነሥርዓት ፈጽሞ ተበተነ።

የወያኔ ጆሮ ጠቢዎች ከሰልፊ በፊት፣ በሰልፉ ጊዜ እና ከሰልፉ በኋላ ግንባር ቀደም የሰልፉ ተዋንያንን የማደን፣ የማዋከብ፣ የማሠር፣ የመደብደብ “ሥራ” በዝቶባቸው ሰንብቷል። ባሠሩና ባዋከቡ መጠን ግን የሕዝብ ምሬት እየበረታ መጥቷል።

ወያኔ ሰልፉን ለመቆጣጠር እጅግ ብዙ የሆነ የፓሊስ፣ የጦርና የሰላይ ሠራዊት ለማሠማራት ተገዷል። ይህ ራሱ አንድ ድል ነው።
ከዚህ ሰልፍ የተገኘው ጥቅም ግን ይህ ብቻ አይለም። ወያኔ በሕዝብ ልብ ውስጥ ዘራሁት ያለው ፍርሀት በኖ የሚጠፋ መሆኑ፤ እድል በተፈጠረ ጊዜ ሁሉ ወጣቶች በፈጠራ ሥራዎቻቸው ተመልካችን ማስደመም የሚችሉ መሆኑን፤ የተለያዩ ሀይማኖቶች ተከታዮችን ለማጋጨት ወያኔ የሸረበው ድር የተበጣጠሰበት መሆኑ ሰልፉ አሳይቷል።

በሌላ በኩል ደግሞ ወያኔ በወታደር እና በሰላዮች ብርታት ላይ የቆመ ሥርዓት መሆኑን አሳይቷል። ወያኔ በጠመንጃና በስለላ ላይ ያለው ሞኖፓሊ ካልተሰበረ ሕዝባዊ ተቃውሞዎችንም እሱ ከሚፈልጋቸው ክበብ እንዳይመጡ ማፈን የሚችል መሆኑ አሳይቷል።
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ይህንን የወያኔ ወታደራዊና የስለላ ሞኖፖሊ መስበር የሥራው አንድ አካል አድርጎ ይመለከታል።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በሕጋዊና ሰላማዊ መንገድ አምባገነኑን ወያኔ በመገዳደር ላይ ያሉትን ወገኖች ትግል ያደንቃል። እንዳንዳንዳችን የየበኩላችን ጥረት ካደረግን የኢትዮጵያን የመከራ ጊዜ በእጅጉ እንደምናሳጥር ያምናል።
ግንቦት 7 ሕዝብ ተቃውሞ ለማቅረብ የወያኔን ባለሥልጣኖች ፈቃድ መጠየቅ የሚያበቃበት ጊዜ እንዲመጣ ተግቶ ይሠራል። ለዚህ ዓላማም ተባብረን እንድንቆምም ጥሪ ያደርጋል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

No comments: