September 30 / 2013
መስከረም ፳(ሃያ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አቶ አንዳርጋቸው ይህንን የተናገሩት በኖርዌይ ከተካሄደው ደማቅ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት በሁዋላ ነው።
የግንቦት7 ዋና ጸሀፊ የሆኑት አቶ አንዳርጋቸው የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅቱ በአንድ በኩል በግንቦት7 ህዝባዊ ሀይል አባላት ላይ ከፍተኛ መነቃቃት የሚፈጥር በሌላ በኩል ደግሞ የተጣለብን ህዝባዊ አደራ ከፍተኛ መሆኑን የሚያስታውሰን ነው ብለዋል።

በውጭ አገራት ተመሳሳይ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ለማድረግ እቅድ አላችሁ ወይ ተብለው የተጠየቁት አቶ አንዳርጋቸው፣ ህዝባዊ ሀይሉ ከተግባር ጋር በተዛመደ መልኩ የገቢ መሰባሰብ ዝግጅት መርሀ ግብሩን ይፋ እስከሚያደርግ ድረስ በህዝባዊ ሀይሉ ወይም በግለሰቦች ስም ምንም አይነት የገቢ መሰባሰቢያ ዝግጅት መደረግ እንደሌለበት ገልጸዋል
በሌላ ዜና ደግሞ በርካታ ቁጥር ያላቸው በስቶክሆልም እና አካባቢዋ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ከ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ጋር ውይይት አድርገዋል። አቶ አንዳርጋቸው የግንቦት ሰባት ህዝባዊ ሃይልን ዓላማዎች፡ተልዕኮዎች እና ራዕይ በማስተዋወቅ ህዝባዊ ሃይሉ ከምስረታ ጀምሮ አሁን ያለበትን ደረጃ በምስልና በጽሁፍ የተደገፈ ገለጻ ለተሰብሳቢው አቅርበዋል።
እሳቸው እና ሌሎች የአመራር አካላት እንዲሁም አባላት የተገኙበት የውትድርና ስልጠና አንዱ የበታች አንዱ የበላይ እንዳልሆነ በማስገንዘብ ይህ ህዝባዊ ሃይል ቤተሰባቸውን፡ስራቸውን፡ ገንዘባቸውን፡ እና የተደላደለ ኑሯቸውን በመተው ከኢትዮጵያ እና ከመላው ዓለም የተውጣጡ ኢትዮጵያውያን የተዋቀረ እንደሆነ ገልጸዋል።
የግንቦት ሰባት ዓላማ በኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን ማስፈን ብቻ ሳይሆን ባለፉት 22 ዓመታት ኢትዮጵያውያን የተገፈፉትን ክብራቸውን ማስመለስ ጭምር መሆኑን አቶ አንዳርጋቸው አስምረውበታል ሲል ቴዎድሮስ አረጋ ከስዊድን ዘግቧል።
No comments:
Post a Comment