Friday, September 13, 2013

ርእዮት አለሙ እና የእስር ጉዳይ በደረጀ ሃብተ ወልድ

september 12, 2013

ጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮት ዓለሙን ለመታሰር ካበቃት ወንጀል አንዱና ዋነኛው ፦”… በቃ!” ተብሎ የተፃፈን ጽሁፍ ፎቶ ማንሳቷ ነው። .. ለኔ ይገርመኝ የነበረው፤ርዕዮትንም ከሙያና ከሞራል አንፃር ያስወቅሳት የነበረው.. “በቃ!” ተብሎ የተፃፈውን ጽሁፍ ዝም ብላ ብታልፈው ነበር። የልማታዊ ጋዜጠኛ አንዱና ዋነኛ ተግባር በህዝብና በመንግስት መካከል እንደ ድልድይ ሆኖ መንግስት (ጥሩም ይሁን መጥፎ)ምን እየሠራ እንደሆነ፤ ህዝቡም ስለ መንግስት ምን እያሰበና ምን እያለ እንደሆነ የሀቅ መረጃ ማቅረብ ነው። ከዚህ አንፃር ርዕዮት ፦”ህዝቡ በቃ እያለ ነው..” የሚል መረጃ በፎቶ ማንሳቷና በብዙሀን መገናኛ ለማቅረብ ማሰቧ ያሸልማት እንደሆነ እንጂ በፍፁም ሊያስከስሳት አይችልም። “በቃ!” የሚል ፅሁፍ በየቦታው እየተፃፈ ባለበት ሁኔታ “ህዝቡ ኑሮው ተሻሽሏል፣ አኮኖሚው አድጓል፤ ልማቱ እጎመራ ነው…” እንድትል ተፈልጎ ከሆነ፤ ያ የህዝብ ግንኙነት ወይም የካድሬ ሥራ እንጂ የጋዜጠኛ ተግባር አይደለም።

…ሀቁ ይኸው ነው። ደርግ የጠመንጃ ታጋዮቹን እንዳሰቃየበት በዶክመንተሪ ፊልም እያሰማመረ የሚተርክልን ኢህአዴግ፤ የብዕር አርበኞችን እያሰረ፣አስሮም እያሰቃየ ነው። ደርግ፤ የያኔዋን የኢህአፓ ታጋይና የ አሁኗን ኢህአዴግ ወይዘሮ ታደለች ሀይለሚካኤልን ነፍሰ-ጡር እያለች ማሰሩን- ለደርግ ጨካኝነትና አረመኔነት እንደማመሳከሪያ እያቀረበ “ጉድ!”ሲለን የነበረው ኢህአዴግ፤ የታሪክ ሀዲዱ ብዙም ሳይጓዝ -ጋዜጠኛዋንና ነፍሰ-ጡሯን ሰርካለም ፋሲልን አስሮ እዚያው እስክትወልድ ድረስ በወህኒ እንደተዋት ህያው ምስክሮች ነን።

ኢህአዴጎች ደርግን የሚከሱበትና የሚወቅሱበት ሞራል ብቻ ሳይሆን ታሪክም የላቸውም። ሳይውል ሳያድር ያን ታሪክ እነሱም እየደገሙት ነውና።

No comments: