Friday, June 5, 2015

ሰማያዊ የG-7 መሪዎች በኢህአዴግ ላይ ጫና እንዲያደርጉ አሳሰበ

June 5,2015
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
ሰማያዊ ፓርቲ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ነገ ግንቦት 29/2007 ዓ.ም በሚካሄደው የG-7 ስብሰባ መጋበዛቸውን ተከትሎ የወቅቱ የጉባኤው መሪ ለሆኑት የጀርመን ቻንስለር ለአንጌላ ሜርክል በፃፈው ደብዳቤ መሪዎቹ በኢህአዴግ ላይ ጫና እንዲያደርጉ አሳስቧል፡፡
 
አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በስብሰባው ላይ መጋበዛቸው ቅር እንዳሰኘው የገለፀው ፓርቲው 24 አመት በስልጣን ላይ የቆየው የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ፓርቲ አፋኝ ለመሆኑ የ2007 ዓ.ም ጠቅላላ ምርጫን በምሳሌነት ጠቅሷል፡፡ ምርጫው ልምድ ያላቸው የውጭ ታዛቢዎች ያልተገኙበትና የአፍሪካ ህብረት ታዛቢ ቡድንም ‹‹ነፃና ፍትሓዊ›› ነበር ለማለት ያልደፈረበት፣ ሰማያዊን ጨምሮ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተጭበረበረ መሆኑን ማረጋገጣቸውን በደብዳቤው አስታውሷል፡፡
ምርጫው ገዥው ፓርቲ 100% አሸነፍኩ ያለበት፣ ተቃዋሚዎች ላይ ከፍተኛ ጫናና እስር ከዚህም ሲያልፍ ለሞት የተዳረጉበት ነበር ያለው ሰማያዊ ፓርቲ ገለልተኛ ሲቪክ ማህበራት እንዳይታዘቡ መከልከላቸውን ገልጾአል፡፡ ጋዜጠኞችን፣ ጦማሪያንን፣ የሀይማኖት አባቶችንና ፖለቲከኞችን ለማጥቃት በወጣው የፀረ ሽብር ህግ ምክንያት ኢትዮጵያ በፖለቲካ እስረኞች ብዛት ከአፍሪካ ቀዳሚዋ መሆኗን ፓርቲው አስታውሳል፡፡
የጉባኤው አባላት ከኢትዮጵያ ጋር ባላቸው የንግድ ግንኙነትና በሚያበረክቱት እርዳታ ምክንያት በሰብአዊ መብት፣ ዴሞክራሲና ልማት ላይ አዎንታዊ አስተዋጽኦ ማድረግ የሚችሉ ቢሆንም የኃይለማርያም ደሳለኝ ፓርቲ የሚመራው መንግስት ለሰብአዊ መብት፣ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት እየገደበና ተቃዋሚዎች ላይ ከፍተኛ በደል እያደረሰ ይገኛል ብሏል፡፡
ጉባኤው ሰብአዊ መብትና ዴሞክራዊያዊ መብትን ለልማትና የኢኮኖሚ ግንኙነት በቅድመ ሁኔታነት በመውሰድ ጫና ማድረግ ካልቻለ የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ግንባታን እንደሚጎዳም ሰማያዊ ፓርቲ አሳስቧል፡፡ በመሆኑም ጉባኤው የፖለቲካ እስረኞች ያለ ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ፣ ኢህአዴግ ተቃዋሚዎችን ማሰርና እንቅስቃሴያቸውን ከመገደብ እንዲቆጠብ እና አፋኝ አዋጆች ላይ ማሻሻያዎች እንዲደረግባቸው በኢህአዴግ መንግስት ላይ ጫና እንዲያደርግና ተገቢውን እርምጃ እንዲወስድ አሳስቧል፡፡

No comments: