Monday, June 1, 2015

ከአርበኞች ግንቦት7 ጋር አብራችሁዋል በሚል የተያዙት ክስ ተመሰረተባቸው

June 1,2015
ኢሳት ዜና :-በሰሜን ጎንደር ዞን ማክሰኝት ከተማ ነዋሪ መሆናቸው የተነገረው አቶ ዘመነ ምህረቱ እና ሌሎች የመከላከያ ሰራዊት አባላት የሽብርተኝነት ክስ እንደተመሰረታባቸው ሪፖርተር ዘግቧል። አቶ ዘመነ የመኢአድ ምክትል ፕሬዚዳንት መሆናቸው በክሱ የተመለከተ መሆኑን የዘገበው ጋዜጣው፣ መስከረም 18፣ 2007 ዓም በጎንደር በሚገኘው የመኢአድ ጽ/ቤት ውስጥ አባላትን በመሰብሰብ ” የወያኔ መንግስት መውደቂያው ደርሷል። አንድ የቶር አውሮፕላን፣ 12 የጦር ጄኔራሎች ከድተው ወደ ኤርትራ ገብተዋል። ኢህአዴግ በጦር ካልሆነ በሰላማዊ መንገድ ስልጣን አይለቅም። የህዝብ እምቢተኝነት በመፍጠር የወያኔን መንግስት መጣል አለብን፣ በ2007 ዓ.ም. የሚካሄደው አገራዊ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ አይካሄድም፡፡ ወደ ምርጫው አንገባም፡፡ ሌላ አማራጭ መጠቀም አለብን…›› ” የሚል ክስ እንደተሰመረተባቸው ጋዜጣው ዘግቧል።

በዚሁ መዝገብ በአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑት አቶ ጌትነት ደርሶ ተመሳሳይ ክስ የተመሰረተባቸው ሲሆን፣ ወደ ኤርትራ ተሻግረው ከግንቦት7 ከፍተኛ አመራር ከሆኑት ዶ/ር ክፈተው አሰፋ ጋር በመገናኘት ፖለቲካዊና ወታደራዊ ስልጠና ወስደዋል ተብሎአል። በዚሁ መዝገብ ተከሰው የቀረቡት ሌላው የአዲስ አበባ ነዋሪ አቶ መለሰ መንገሻ ሲሆኑ ፣ እርሳቸውም የአርበኞች ግንባር አባል ነበሩ ተብሎአል። ተከሳሹ ሰው በመመልመል ስራ ላይ መሳተፉንና በመንግስት ባለስልጣናትላይ ጠቃት ለመፈጸም ሲያጠና ነበር የሚል ክስ እንደተመሰረተበት ጋዜጣው ዘግቧል። የአየር ኃይል ባልደረባ የሆነው ምክትል መቶ አለቃ አንተነህ ታደሰ ዘውዴ ተመሳሳይ ክስ ተመስርቶበታል።


መኮንንኑ ታኅሳስ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከደብረ ዘይት አየር ኃይል በመነሳት ወደ ኤርትራ ጉዞ እያደረጉ መንገድ ከሚያሳያቸው ሌላ ሰው ጋር ታኅሳስ 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ወሮታ ከተማ ላይ መያዛቸው በክሱ ተመልክቷል፡፡ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ዞን ቶንጎ ወረዳ ሻንቦላ ከተማ ሻንቦላ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር ውስጥ ነዋሪ ናቸው የተባሉት ሼክ መሐመድ አብዱል ቃድር የሚባሉ ተጠርጣሪ የእስልምና ሃይማኖትን እንደ ሽፋን በመጠቀም፣ በኃይል እስላማዊ መንግሥት ለማቋቋም ሲንቀሳቀሱ ነበር በሚል ክስ ተመስርቶባቸዋል።


ከአርበኞች ግንቦት7 ጋር በተያያዘ የሚታሰሩ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና ወጣቶች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ነው። በቅርቡ 4 የአየር ሃይል ባልደረቦችና የእግረኛ ሰራዊት አባላት ተመሳሳይ ክስ ተመስርቶባቸዋል። የመኢኢድ፣ የሰማያዊ እና የቀድሞው አንድነት ፓርቲ አንዳንድ አባላት በተመሳሳይ ወንጀል ተከሰው በማእከላዊና በቃሊቲ እስር ቤቶች ይገኛሉ።


ከአርበኞች ግንቦት 7 ዜና ሳንወጣ በኒዉዚላንድ ኦክላንድ ትላንት ለ አርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የገንዘብ ማሰባሰብ በተደረገዉ ዝግጅት በተሳካ ዉጤት መጠናቀቁን አንዱአለም ሃይለማርያም ከኦክላንድ ዘግቧል። የአርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና ዲሞክራሲ የዉጭ ጉዳይ ዘርፍ ተጠሪ የሆኑት አቶ አበበ ቦጋለ በዝግጅቱ ላይ በመገኘት ድርጅቱ በአሁኑ ሰዓት የደረሰበትን እና በማከናወን ላይ ያለዉን ስራ አብራርተዋል።


አቶ አበበ የአርበኞች ግንቦት 7 በኤርትራ በኩል ስለሚያደርገዉ እንቅስቃሴና በተቃዋሚ ሃይሎች በኩል ከተቻለ ተዋሕዶ አለበለዚያም በጥምረት ለመስራት የሚያደርገዉን እንቅስቃሴ በሰፊዉ ገልፀዋል። በአሁኑ ጊዜ ሃላፊነት የጎደለዉ የሕዉሐት መራሹ መንግስት ምርጫዉን አስመልክቶ በሕዝብ ላይ እና በተቃዋሚ ፓርቲዎች ላይ እየሰራ ያለዉን ቅጥ ያጣ ግፍ የዘረዘሩት አቶ አበበ፣ አሁን ጊዜዉ ብሶታችንን ብቻ የምናወራበት ባለመሆኑ በምንፈልገዉ መንገድ ሁሉ በመደራጀት አገር አድን ጥሪዉን ተቀብለን ለአገራችን ኢትዮጵያና ሕዝቧ ልንደርስላት ይገባል ብለዋል።
በዝግጅቱ ከ20 ሺ ያላነሰ ዶላር መሰባሰቡንም በዘገባው ተመልክቷል።

No comments: