Sunday, January 11, 2015

ገዢ ቢሰባ ለመሬት አህያ ቢሰባ ላራዊት (ቢኒያም ግዛው ከኖርዌይ ኦስሎ)

Biniam Gizaw
ይሄ ምርጫ መቼስ ስንቱን ያስታውሰናል?በደርግ ዘመን እናቶች ወንድ ልጃቸውን ከየጉያቸው እየተነጥቁ እና እየታፈሱ በጦርነት ሲማገዱ ወንድ ልጅ ላለመውለድ. . . ትዝም አላለሽ ወይ የክፉ አመቱ ላንቺና ለልጅሽ ያለቀ ስንበቱ ማህጸኔን ዝጋ ይቅር ምን አባቱ በእንባ እየዳከርሽ ብለሽ ያልሽበቱ። እያሉ ፈጣሪን ወንድ ልጅ እንዳይሰጣቸው የለመኑትን ቤቱ ይቁጠራቸው። የአፈሳና የሀገራችንን አንድምታ ለመረዳት ከሰሞኑ በየከተማዎችና ጎዳናዎች ያለው የድብደባ የአፈሳና የሞት ፍርሀት ድባብ ተቀባብሎ ለቃታ የተዘጋጁ ጥይት በእያንዳንዱ ሰላማዊ ዜጋ ጆሮ ስር ተደግኖ እንደሚራመድ በቀላሉ መረዳት ይቻላል።
. . . ጭቃ ከማቡካት ጀምሮ አብሬው ያደኩት ጓደኛዬ ስሙ ጌታቸው ይባላል። እንዴት እንደምንዋደድ እንደምንተሳሰብ እና እንደምንመካከር አትጠይቁኝ። በቃ ጌቾ ምርጥ ጓደኛዬ ነው።
እናም በጊዜው ወያኔ መዲናችን አዲስ አበባ ገቡ ገቡ የሚባልበት ሰአት ኖሮ ግራ መጋባቴን ከባልንጀራዬ ላወራ በአጥር በኩል ጌቾ!ጌቾ! ብል እናቱ ወ/ሮ በለጥሻቸው ከየት እንደመጣ የማይታወቅ ከበሮአቸውን ጸሀይ ላይ እያገላበጡ ግቻ ያርግህ. . . ጎይቶም አትልም! ብለው ቀልቤን ገፈፉት። ነገሩ ወዲህ ኖሮ እሳቸውም ወ/ሮ በለጥሻቸው ታጋይ ትብለጽ ተብሎ ስማቸው መተርጎሙን ያወኩት ቆይቼ ነገር ከገባኝ በኋላ ነው። ከዚያማ እነአቶ ክፍሉ (ክፍለእግዚእ) እነአዲስ (ታጋይ ሀዲሽ) ወዘተ ስናዳምጥ የጫካ ስም ብቻ ሳይሆን የከተማም ስም እንደነበራቸው ተረዳን።
ከዛ በኋላማ ምኑን ልንገራችሁ በኳስ ሜዳ ሰው የጠፋ ጊዜ በረኛ ካልሆነ ወደ ውጪ የወጣ ኳስ አቀባይ የነበረው ጊቾ በግልጥ ፎሪ የወጣውን እንደፈለገ እና ደስ እንዳሰኘው ጎል ብሎ ሲያፀድቀው ቢደብረንም መስማማት ብቻ ሆነ። አይ የቀን ክፉ! ግንቦት 20። ይኽው እስክንበታተን ድረስ ጎይቶምም እንደኛ ባሉት ላይ ተቀይሮ ሲጎለብት ታጋይ ትብለፅ ደግሞ እነማዘርን በዳቦ ተቆጣጥረው ሲጠረንፉን ከረሙ። 
ጦጣ በአንድ ወቅት ለቃለ መጠይቅ ቀርባ ኖሮ ምን ትወጃለሽ? ተብላ ብትጠየቅ የዛፍ ላይ ትግል አለች አሉ። በፀዳ ሜዳ ግልፅነትና እውነት ባለበት ምርጫ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገሮች ማየት ከንቱ እየሆነ መምጣቱ በዕጅጉ ያሳዝነናል ። አንድ ጎጠኛ ብሔረሰብ ብቻ በሚመቸው ፓርላማና በየቀበሌው እንደ ጦጣ በስልጣኑ ላይ እየተንጠላጠለ 23 ዓመት መግዛቱ ስርዓቱ ምንኛ አስከፊ መሆኑን የሚያሳይ ነው። 
ኢትዮጵያ ለዘመናት ተከብራ የኖረችና ህዝቦቾም ልዩነትን ወደሆላ በመተው በጋራ ፣በመቻቻል ፣በመካባበር ሀገራቸውን አስከብረው ከዘር እና ከእምነት ይልቅ ኢትዮጵያውነትን በማስቀደም ኢትዮጵያዊነት የገነነባት ሀገር እንደነበረች ይታወቃል እነሆ ዛሬ ወያኔ የሁትሱና ቱትሲን ስርዓት ናፍቆ ገዢ ከኔ ዘር ሌላ ለአሳር እያለ ሰፊውን ህዝብ ለጦርነት ጋብዞታል። ወያኔ ፈጽሞ በኢትዮጵያዊነት የማያምን እና የኢትዮጵያ ህዝበም በአንድነትና በፍቅር እንዲኖር የማይፈልግ ጸረ ኢትዮጵያዊ ሲሆን ይህንንም በመረዳት እኛ ኢትዮጵያኖች አንድነታችን ለወያኔ የራስ ምታት መሆኑን አውቅን  አንድነታችንን የሚያጠናክር ስራዎች ላይ ልናተኩር ይገባል :. ዘረኛው የህህዋት መንግስት በአንድ ወቅት አርሱ አደሩ የሀገሬን ገበሬ እኔ አውቅልሀለሁ እያለ ካለበት ሀገር መሬትና ቀኤ ድረስ መጥቶ ልግዛህ እያለ መከራውን ሲያበላው . . .
ሳለቅስ ሳነባ የሰጠኽኝ ሸማ ጉድ በል ያገሬ ልጅ እንካ መርዶ ስማ የወንዝህ ማዕረግ በትግሬ ተቀማ
እያለ ለአያትና አባቱ በቅኔ ብሶቱን መናገሩ አፈናና ረግጣውን ቅሚያና ዘረፋውን መቋቋም ቢያቅተው መሆኑ ልብ ይሏል። የፈረንሳዩ ደራሲና ፈላስፋ ቪክቶር ሁጎ "When dictatorship is a fact, revolution becomes a right." ብሎ ማለቱ አንደ ወያኔ ላለ በአንድ ብሔር የበላይነት ተንፈናጥጦ እንደፈለኩ ልግዛህ ለሚል መንግስት ትክክለኛ አባባል ነው።
ምርጫ ፍትህና ዴሞክራሲ ምን እንደሆነ ለማይገባው መብት ማስከበሪያው ብቸኛ መንገድ ለለውጥ ፀንቶ መታገል ብቻ ነው። በአሳማ መንጋ የምርጫ ውድድር ያው አሸናፊው አሳማ እንጂ ነብር ወይ አንበሳ አይሆንም። በመሆኑም ያው አሳማ ነገም ልርገጣችሁ ማለቱ አይቀርም። በሰብዓዊ ትግል ተስፋ አይቆረጥም የሰፊው ህዝብ መብት ታላቅ ውቅያኖስ ነውና ጥቂት የአምባገነን ጠብታ ሰፊውን ባህር አያደፈርሰውምና አሁንም የሰብዓዊ መብት ትግል አሸናፊ ነው። በጥቂት ዘረኞችና በአንድ ጎሳ የበላይነት የተያዘው የወያኔ አገዛዝ የሰፊውና የታላቁን የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል በምንም መልኩ ሊገታው አይገባም ይልቁንም ''ገዢ ቢሰባ ለመሬት አህያ ቢሰባ ላራዊት'' እንዲሉ በማን አለብኝነት የተንሰራፋውን ወያኔና አግዛዙ መቃብሩ ተምሶ ያለቀ መሆኑ ግልፅ ነው። እናም በሁሉም አቅጣጫ የትግላችንን ትንቅንቅ ልንቀጥል ይገባል እላለሁ።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !!!

No comments: