Thursday, May 14, 2015

በአቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ላይ ዘለፋ አዘል ግምገማ ተካሄደ

May 13,2015

ኢሳት ዜና :- ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በሰብሳቢነት የሚመሩት  ኢህአዴግ፣  ከፍተኛ የግንባሩንና የመንግስት አመራሮችን በመገምገም ለሚቀጥሉት አምስት አመታት የመንግስት ስልጣን የሚይዙትንና ድርጅቱን የሚመሩትን ሲመርጥ ከርሟል። ሁሉም የኢህአዴግ ከፍተኛ ሹሞች የተገመገሙ ሲሆን፣ የመንግስት ስልጣን ያልያዙ ነገር ግን በግንባሩ ውስጥ ያገለገሉ ነባር ታጋዮችም በግምገማው ተሳትፈዋል። አቶ ሃይለማርያም ግምገማውን በሰብሳቢነት ሲመሩ ቆይተው፣ የመጨረሻው ተገምጋሚ ራሳቸው ሆነዋል። በጠ/ሚኒስትር አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ላይ የተደረገው ግምገማ አንድ ሙሉ ቀን የወሰደ ሲሆን፣ ከምሽቱ ሶስት ሰአት ላይ መጠናቀቁን ምንጮች ገልጸዋል። አቶ ሃይለማርያም ብዙዎችን የግምገማ ነጥቦች ለመቀበል ፈቃደኛ አለመሆናቸው ለግምገማው መራዘም ምክንያት ሆኗል።
ሁሉም ባለስልጣናት  የሚገመገሙባቸው ነጥቦች ተመሳሳይነት አላቸው።  አስተያየቶች የሚሰጡትም በእነዚህ ነጥቦች ዙሪያ ነው። አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ  በቅድሚያ ራሳቸውን የሄሱ ሲሆን፣ እንዲህ ብለዋል ” ጥራት ያለው እቅድ አዘጋጅቶ በማከናወን ረገድ ፣ ራስን በንባብ ለማብቃት ጥረት በማድረግ ላይ እንዲሁም የለውጥ ትግበራ ላይ ችግሮች አሉብኝ” ። ነገር ግን “ስራን ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ በመፈጸም፣ ስራን በተሟላና ጥብቅ ስነምግባር በመፈጸም፣ ለስራ የተሰጠኝን መሳሪያዎች በእኔ ባይነት ስሜት በመጠቀምና በመጠበቅ እንዲሁም በፖሊሲ አፈጻጸም ላይ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ በኩል  ችግሮች የሉብኝም” ብለዋል። ኪራይ ሰብሳቢነትን በመታገል በኩል በከፊል ችግሮች አሉብኝ ሲሉ አክለዋል።
ከቃለ ጉባኤው ለመረዳት እንደሚቻለው የመጀመሪያውን ሂስ ያቀረቡት ነባሩ የህወሃት ታጋይና የጠ/ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አርከበ እቁባይ ናቸው። አቶ አርከበ ” የተጠራቀሙ ችግሮችን በመፍታት በኩል ችግሮች አሉብህ፣  ካቢኔህ ውስጥ ያለውን  የጥራት ችግርም በደንብ አላየኸውም፤ ለሃገሪቱ አመራር ቶሎ ምላሽ አትሰጥም፤ ‘እኔ የሚመስለኝ እንዲህ ነው’ ከማለት ውጭ፣ ቆፍጣና የሆነ አመራር አትሰጥም፤ ስራዎች ሁሉ ከሌላው አካል እንዲመጣልህም ትጠብቃለህ፣ ብዙውን ጊዜ በቅጻቅጾች ላይ አትኩረህ አይሃለሁ፤ ከብሄራዊ ደህንነት እና የቴክኖሎጂ ቁርኝት ጋር ያለውን ችግር ቁጭ ብለህ አለመፍታትህ ውዝግቡ እስካሁን እንዲቆይ አድርጎታል” ሲሉ ሂስ ሰንዝረዋል።
ሌላው የህወሃት አባል አቶ አስመላሽ ወ/ስላሴ ደግሞ  ” ስልጣንን ጠቅልሎ የመያዝ ነገር አለ፤ ስዎችን እርስ በርስ የማጋጨት ነገርም አለ፣ ለአማካሪዎችህ ‘እሱ ምን ሰርቶ ነው’ ትላለህ፣ በፖሊሲና እና ስትራቴጂ ላይ አዲስ የፈጠርኸው ቋንቋም የለም፣ ፓርላማው በአንተ
ጊዜ አዲስ ቃላትን እንኳ አለመደም፣ ይህም ከንባብ  የመጣ ችግር ነው፤ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን በመደገፍ ፤ ሃሳብን በመቀበል ረገድ ችግር አለብህ፣ ገንቢ ሃሳብም በመስጠት ላይ ችግር ይታያል”” ብለዋል። አቶ ሃይለማርያምን እጅግ ያበሳጫቸው የአፋር ክልል ፕሬዚዳንት አቶ እስማኤል አሊሴሮ ያቀረቡት ትችት መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ።በቃለ ጉባኤው ላይ ሰፍሮ እንደሚታየው  አቶ አሊሴሮ ” ተግባብቶ መስራት ላይ ችግር አለ፣ ከክልሎች ጋር ያለው ግንኙነት እንዲሻሻል
የእሱ አስተዋጽኦ የለበትም፣ ያልተጻፉ ህጎች ይወጣሉ፤ ከክልሎች  ጋር ሳትነጋገር ከምክትሎች ጋር የኮሚኒኬሽንን ስልጣን በመጋፋት የህዝብ አስተያየት ትሰበስባለህ፤ ሰዎች ነጻ ሆነው እንዲሰሩ አለማድረግ፤ ገፍቶ ሄዶ ችግሮችን አለመፍታት፣ በአማራና አፋር፣ በትግራይና አፋር ድንበሮች ያለውን ውዝግብ ተጋፍቶ ችግሮችን ለመፍታት አለመቻል፣ ጥሩነትን ወይም በጎነትን አለማበረታታት፣ አንዳንድ ሚኒስትሮች ቤተመንግስት እንዳይገቡ መከልከል፤ እቅድ ከማውጣት ጀምሮ በፖለቲካ ላይ ለውጥ ለማምጣት ስትጥር አለመታየት” የሚሉ ትችቶችን በንባብ አሰምተዋል።
አቶ ሃይለማርያም ይህን ጽሁፍ ያዘጋጀውንና እንዲቀርብ ያደረገውን ሰው አውቀዋለሁ በማለታቸው ከፍተኛ ውዝግብ ተፈጥሮ ነበር፣ እንደምንጮች መረጃ። ወ/ሮ ሙፈሪያት ከሚል ባቀረቡት ሂስ ደግሞ ” በመንግስት በጀት እና ፋይናንስ እገዛ ማድረግ እና  ስራ እንዲሰራ መደገፍ ሲኖርብህ አትገድፍም፤ የመከላከያ ገንዘብ አወጣጥን በተመለከተ በከፊል በኦዲተር እንዲጣራ ከተስማማህ በሁዋላ ፣ በግልህ ሽረህ በእኔ ላይ ዛቻ እንዲደርስብኝ አስደርገሃል። ቤተመንግስቱን ኦዲት ለማድረግ በኦዲተርነት ሰርቶ የማያውቅ ሰው ተመድቧልና አይሆንም ስል፣ ‘ሂጂ ስራሽን ስሪ ዛሬ ችሎ ሊሆን ይችላል’ ተብያለሁ፣ ይሄ ስራ እንዲሰራ አለመፈለግ ነው። ለለውጥም ዝግጁ አይደለህም። በረከት ሰብስቦን ሁሉም ስህተቱን ሲቀበል አንተ አልተቀበልህም፣ ይሄ ለለውጥ አለመዘጋጀትህን ያሳያል።” ብለዋል።
ወ/ሮ ሙፍሪያት  ” ከቢሮ ስነምግባር አንጻርም ችግሮች አሉ ይላሉ። ወደ ውጭ አገር በሚደረግ ጉዞ ላይ አድልዎ መኖሩን ራሳቸውን በምሳሌነት በማቅረብ ተናግረዋል። ” በግል ‘ አንቺ ተጽኖ ፈጣሪ አይደለሽም ፣ ደቡብ አንቺን ከሚወክል ቢቀር ይሻል ነበር’” ተብያለሁ የሚሉት ወ/ሮ ሙፈሪያት፣  ወደ አውሮፓና ግብጽ ለሚደረገው የዲፕሎማሲ ጉዞ አስቀርቶኝ ወደ አዋሳ ልኮኛል ብለዋል። ዋናው ኦዲተር በአግባቡ እየሰራ አለመሆኑን ስናገርም ሙፈሪያት ስራ አትሰራም ብለኸኛል። ከካሱ ኢላላና ከሽፈራው ጋር ተጋጭቼ አንድም ቀን ችግሩን ለመፍታት አልሞከርክም፤ የሰው ስም ታጠፋለህ፣ ትለማመናለህ”” ሲሉ የሰላ ትችት አቅርበዋል። ወርቅነህ ገበየሁ ደግሞ ”   ቆራጥ አመራር በመስጠት በኩል መሰራታዊ ክፍተቶች አሉብህ” ያሉዋቸው ሲሆን፣  የፌደራል ፖሊስ ራሱ ተሟሙቶ ካልሰራ በስተቀር ሃይለማርያም አያግዘውም ሲሉ አክለዋል። “አፋጣኝ መልስ መስጠት ላይ ችግር አለ። የፌደራል ፖሊስ
ኮሚሽነር በነበርኩበት ዘመን፣ ህዳር 23 ሶማሊ በነብርኩበት ጊዜ በተደጋጋሚ ደውየ ‘ ስብሰባ ላይ ነኝ’ በሚል አልመለስክልኝም፤ ይዘነው የመጣነውን ፕሮግራም ጠፍቶብኝ ከደህንነቶች ጋር ስጨቃጨቅ ውዬ ፣ ተሰድቤ በበነጋታው ችግሩን ስነግርህ ልትፈታው አልቻልክም። የፌደራል ፖሊስ ከደህንነት ክፍሉ ጋር ያለው ግንኙነት የደከመ ነው። ጋምቤላ ላይ ያሉ ተዋጊዎችን እናጥፋቸው አሁንም ሶማሊና አማራ ክልል  ያሉ አማጽያንን እናጥፋ ስልህ የደህንነት ክፍሉና ጸጋየ በርሄ ይዘውታል ብለኸኛል። ጅጅጋ በተፈጠረው ነገር አራት ጊዜ ደውየ ምላሽ ሳጣ ለሳሞራ ደወልኩ፣ እናም ‘ ለእኔ ከማሳወቅ ይልቅ ከጦሩ ጋ መንጠንጠል ይወዳል’ አልከኝ። ኢንሳ፣ ኢሳያስ ክፍል ስንሄድ ‘ሁሉንም ነገር እንዳታደርጉ ተብለናል’ እንባላለን። ከሁሉም የደህንነት ክፍሎች ጋር ፊትና ሁዋላ ሆነን እያለ በግዴለሽነት ችግሩን አልፈታሃውም” ሲሉ ጠንካራ ነቀፌታ አቅርበዋል። ነባሩ የህወሃት ታጋይ አቶ ስብሃት ነጋ በበኩላቸው ” ሃይለማርያም ቸልተኝነት ያበዛል፣ በጣም ችላ ይላል፤ ስራዎችን ይገፋል። የሚያውቃቸውን ክህሎት፣ ካለው ሃላፊነት አንጻር ለሌሎች ላማካፈል አይጥርም፤ ያለመጋጨት ነገር አለ። ሚኒስትሮች ‘በፍላጎት እንዳንሰራ ከሚያደርጉን ነገሮች አንዱ ስልጠናዎችን ስናገኝ  ስለሚያሳልፍብን ነው’ እያሉ ስሞታ ያቀርባሉ። በስራ ስምሪት ወቅት በምትፈልጋቸው ስራዎች ላይ ራስህ ሰው ትመድባለህ። በረከት ላይ ትለጠፋለህ።” ብለዋል።
ሌላው ነባር ታጋይ አባይ ጸሃየ ደግሞ ” ሚኒስትሮች ሃላፊነት ተስምቷቸው የሚሰሩ አይመስለውም፤ ድጋፍ የማይሆን ክትትል ያበዛል፣ ሰራተኞችን በጣም ይንቃል። ከፍተኛ ሃላፊዎች ቢታመሙም የታመሙ አይመስልህም። ስራን ያላገናዘበ ሞራልን የሚነካ የሚያስፈራራ ደብዳቤ ለአራት ሚኒስትሮች ሰጥተሃል።” ሲሉ ሂሰዋቸዋል። የብአዴኑ ሊ/መንበርና ምክትል ጠ/ሚኒስትሩ በፊናቸው ” ከህዝብ ወገንተኝነት ጋር በተያያዘ፣ አሁንም ቢሆን፣ ሁሉም እምነቶች በእኩል መስተናገድ ሲገባቸው ለፕሮቴስታንት ሃይማኖት ማዳለት እንዳለ ተገንዝቤአለሁ፤ ስራን በቁጭት ትሰራለህ ብየ አላስብም፣ የመሪነቱን እንዳልታማ እንጅ ለስራው ተቆርቁሮ የሚሰራ አይመስለኝም።  አስተያየት ሲሰጥ ተቀብሎ ለማሻሻል ከመጣር ይልቅ ሃሳቡ ጥሩ ነው ብሎ የመግፋት ነገር አለ፤ ከደህንነት ክፍሉና ከጠባቂዎችህ ጋር ያለህ ግንኙነትም የደከመነ ነው” ብለዋል።
በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ወ/ሮ ሮማን ገብረስላሴ ደግሞ ” ፈጣን ምላሽ መስጠት ላይ፣  ስብሰባ ከገባህ በምንም መንገድ መልስ አትሰጥም፣ ስራን ከፋፍሎ ያለመስጠት ነገር አለ። በሰው ላይ እምነት የማጣት ነገር አለ። ችግርን ወደ መድረክ አምጥቶ ከመፍታት ይልቅ ወደ ዝምታ ታመራለህ። ” ብለዋቸዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ የብአዴኑ አቶ አህመድ አብተው በበኩላቸው ” ታዳላለህ፣ የአቶ አዲሱ ለገሰን ስልጠና እንዳላገኝ ተከልክያለሁ፣ በአንተ አመራር ጥሩ ስራ መስራትና ጥሩ ስነምግባር ማሳየት የመብት መጣስን ያመጣል፣ በጣም ሃይለኛ ተንኮል አለብህ፤ በአንድ ስብሰባ ላይ ‘አማራ አይቀበልህም’ ብለህ ከብሄሬ ጋር ልታጋጨኝ ሞከረሃል። በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያሉ ሌሎች ስራዎችን ትተሃቸዋል ስልህ ‘ ስለሌሎች አያገባህም፤ እኔ ጠ/ሚኒስትር ነኝ’ አልከኝ። ለመማር እንኳ ዝግጁ አይደለህም። እኔ እየተማርኩ መሆኔን እያወቅ ከፈቃድ አሰጣት ጋር አድልዎ ታደርጋለህ። ከጓደኞችህ ጋር በመሆን ‘አህመድ አገሪቱን በእንዱስትሪ ጭስ አፈናት ‘ ብለህ አፌዝክብኝ፤ ሰራተኛ ምንም አይመስልህም። ሞራል ትነካለህ፣ ሞራል አትጠብቅም፣ አስተካክል።” ብለዋል።
ሌላው ትችት አቅራቢ የደህዴኑ የኮምኒኬሽን ሚኒስትሩ አቶ ሬድዋን ሁሴን ናቸው። አቶ ሬድዋን ” ገንቢ አስተያየት መስጠትን በተመለከተ ፣ ብዙ ጊዜ አንድ ፕሮግራም አስቤ እጠይቅሃለሁ። ነገ ዛሬ እያልህ ሃሳብ አትሰጠኝም። አመራር ተቆራርጦ ይሰጣል። በወኔና በእልህ ሂ ደቱን ለመለወጥ የሚደረገው ጥረት አናሳ ነው። ከእኔ ጋር በጥሩ ሁኔታ እያወራ ፣ ከሌላ ሰው ጋር ስለእኔ ሌላ ነገር ነው የሚናገረው፤ ለበረከት ‘እሱና ሽመልስ ልዩ ተልእኮ ያላቸው ሰዎች ናቸው፣ ልቆጣጠራቸው አልቻልኩም’ ብሎ ነግሮታል። ለእኔ አልነገርከኝም። የአመራር መስፈርቶችን ታሟላለህ አልልም።” የሚል ትችት አቅርበዋል።
አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ በቀረቡባቸው ሂሶች ላይ መልስ ሰጥተዋል። “መሻሻል ያለባቸውን አሻሽላለሁ” ብለዋል። “ብዙውን ስራ እራሴ እሰራለሁ በሚል ለመስራት ስለምሞክር ነው ክፍተቶች የተፈጠሩት” የሚሉት አቶ ሃይለማርያም፣  “ስራውን ጠቅልሎ ይዟል ለሚባለው ግን የሚገባኝን ይዣለሁ ብየ ነው የማስበው” ብለዋል።  ሰዎችን ማጋጨት ለተባለው  “እኔ ሰዎችን በማጋጨት ምን ላገኝ? ችግር ያለበትን ሰው ችግር አለበት ፣ ጥሩውንም ጥሩ ነው” እላለሁ። ሲሉ ተከራክርዋል። “ሶማሊና አማራ፣ ትግራይ አፋር ላይ የተነሳው ችግር ከአሰራር ጋር በተያያዘ የመጣ ችግር መሆኑን የገለጹት አቶ ሃይለማርያም፣ በሙፍሪያት ለተነሳው ቅሬታም ” ሙፈሪያትና ሽፈራውን ለማስማማት ሁለቱም ጋር ችግር አለ፤ አባይ እንዲፈታው ነግሬዋለሁ፡፡ ብለዋል””
“ስንሰራ ከፖለቲካ ጋር አስተሳስረን እንስራ ነው ያልኩት እንጅ ስራን አልከለከልኩም የሚሉት አቶ ሃይለማርያም በአቶ አህመድ  በአቶ አህመድ ለቀረበባቸው አስተያየት ደግሞ ” ፊት ለፊት ለራስህን ነው የነገርኩህ፣ ለሌላ ሰው በቀልድ መሃል ላወራ እችላለሁ።” ሲሉ በመካድና ባለመካድ መሃል ሆነው መልሰዋል። “ለውጭ ጉዞ ታዳላለህ የተባለውን በአሰራራችን መሰረት ብናየው ጥሩ ነው ” ያሉት አቶ ሃይለማርያም፣ “እገሌ ከገሌ የሚባል ሳይሆን የስራውን አዋጭነት አይተን ነው  ሰዎችን የምንመድበው ሲሉ አክለዋል። “ሰው ሲጋጭ ደስ ይልሃል የተባለውን አልቀበለውም” ብለዋል።   “ስራ ሲሰራ በግድ መሆን ባለበት ቀን ሊሰራ አይችልም፤ ችግሮች አሉ።  የደረሰንን ስልጠና አዳርሰናል፣ ማንንም የምነካ ሰው አይደለሁም፤ ማንንም አልንቅም” ሲሉ ራሳቸውን ለመከላከል ሞክረዋል።
“እምነትን በተመለከተም በእኔ እምነት ሁሉንም እኩል እያስኬዱ ነው ” አቶ ሃይለማርያም፣  የሙስሊሙንም የክርስቲያኑንም ችግሮች እኩል አያለሁ፣ ያለሁት ፖለቲካ ላይ ነው። ብለዋል። በአቶ ስብሃት ለቀረበባቸው ሂስ ደግሞ ” ስብሃት በጣም ይጮሃል፣ እንዳሞራ ሁሉ ይዞረኛል፣ እዚህ ሳወያይ ሁሉ በጣም ይጮሃል፣ አለቃ መሆን ችግር ነው ብየ ዝም አልሁ። ንግግር ከመልክ ያምራል ይባላልና የተሳሳትኩት ነገር ካለ አርማለሁ።በአባባል ክፈተት ካለ ይቅርታ እጠይቃለሁ። በማለት በአቶ ስብሃት ላይ ያላቸውን ቅሬታ ገልጸዋል። አቶ ሃይለማርያም የቀረበባቸውን ሂስ ቢቀበሉም ሌሎች አባሎቻቸው ግን በሂስ አቀባበላቸው ላይ የሰላ ትችት ከመሰንዘር አላገዳቸውም። የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ በከር ሻሌ ዱሌ ” ሃይለማርያም አሁንም ለመማር አልተዘጋጀህም፣ ሰው ከሁለት ነገሮች አያመልጥም፣ ከፈጣሪና ከህሊናው።  ቀኑን ሙሉ በውይይት ፈጅተን የተሰጠን ምላሽ አልተመቸኝም”ያሉ ሲሆን፣  የአካባቢ ጥበቃና የደን ሚኒስትር አቶ በለጠ ታፈረ ደስታ በበኩላቸው “አብዛኛውን ገፍቶታል፣ ወደውስጡ አላስጠጋውም፣ ሁሉን ከተከላከለ በሁዋላ አስተካክላለሁ ብሎአል ” ብለዋል።
ዶ/ር ደብረጺዮን ገ/ሚካኤል ደግሞ  ” ከፊሎችን አልነካሃቸውም ፣ መኮርኮምም አይቸብሃለሁ፤ ይሄ ከአንድ የአገር አመራር አይጠብቅም” ያሉ ሲሆን፣ ወ/ሮ አስቴር ማሞ  ደግሞ ” አቀባበሉ ላይ ዞሮ ዞሮ ላንተ ነው የሚጠቅምህ፣ እዚህ አገር ላይ የሆነ አሻራ ብታሳርፍ ያንተ ስም ነው የሚነሳው ፣ ፍቅርንና የመተባበር መንፈስን ብትዘራ ጥሩ ነው።” ብለው ምክር ለግሰዋቸዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሃኖም ደግሞ ” ሁሉንም ጥያቄዎች ሳያቸው በወቅቱ መፈታት ይችሉ ነበር። ነገ የተሻለ አማራጭ እንዲኖረን እነዚህን ወስደህ ማረም አለብህ። የሙስሊም የመፍትሄ አፈላላጊ አመራር ማሰሩን በተመለከተ ትእዛዙ የመጣው ከላይ ነው። ባይሰራው ኖሮ ነበር የምጠይቀው” በማለት ውሳኔ የሚወስን ሌላ ሃይል እንዳለ ፍንጭ ሰጥተዋል። አቶ ደሴ ዳልኬ ደግሞ ” በከፍተኛ አመራሩ ውስጥ ያለው መሰረታዊ ችግር ምንድነው የሚለውን ለይቶ የመፍታት ነገር ቢጠናከር” የሚል ሃሳብ ሲሰነዝሩ፣  አቶ አረከበ እቁባይ  የአቶ ደሴን ሃሳብ በመደገፍ  ” ጠንካራ ጎኑ እንዳለ ሆኖ መስተካከል ካለበት ነገር አንዱ ነገሮችን ጠቅልሎ መያዝ ላይ ነው። በአሰራራችን መሰረት ሚኒስትሩ የራሱን ስራ ፣ የክልል አመራሮችም ያራሳቸውን ስራ መስራት አለባቸው። ያንን ማስተካከል ያለብህ ይመስለኛል።” ብለዋል።
አቶ በረከት ስምኦን በበኩላቸው “ቸልተኛ መሆንህና በችግሮች ልክ ቶሎ ምላሽ አለመስጠትህ በተለይ ከራሱ ጠባቂዎችና ከቤተመንግስት ደህንነቶች ጋር እንደፈለገ እንዲጨፈርብን አድርጎናል። እዚህ ላይ  ብታስተካክል ጥሩ ነው። ሌሎችን ጉዳዮች በተመለከተ ራሱ ባለቤቱ ነው መሙላትና መጨነቅ ያለበት” ሲሉ የድጋፍ አይሉት የተቃውሞ አስተያየት ሰጥተዋል። አቶ ሃይለማርያምም በመጨረሻ የቀረበባቸውን ሂስ እንደሚያስተካክሉ ተናግረው ግምገማው አብቅቷል።   አቶ ሃይለማርያም የ ቢ ደረጃ ማግኘታቸውን ከቃለጉባኤው ግምገማ  ውጤት ያሳያል።

No comments: