Monday, May 11, 2015

መንግስት ከ‹‹ሁከትና ብጥብጥ›› ጋር በተያያዘ የያዛቸው የሰማያዊ አባላት ላይ ክስ መሰረተ

May 11,2015
∙ተከሳሾች ዋስትና ተከልክለዋል
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
መንግስት ሚያዝያ 14/2007 ዓ.ም ራሱ በጠራው ሰልፍ ላይ ‹‹ሁከትና ብጥብጥ በማስነሳትና በማስተባበር›› አስሯቸው የቆዩ ሰዎች ላይ ክስ መሰረተ፡፡ በፌደራል አቃቤ ህግ ከሳሽነት ክሱ የተመሰረተባቸው ሦስት የሰማያዊ አባላትና አንድ ሌላ ግለሰብ ሲሆኑ፣ ተከሳሾች ዛሬ ግንቦት 3/2007 ዓ.ም በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት መናገሻ ምድብ ወንጀል ችሎት ቀርበዋል፡፡
በእነ ማትያስ መኩሪያ የክስ መዝገብ የተካተቱት ተከሳሾች ማቲያስ መኩሪያ፣ መሳይ ደጉሰው፣ ብሌን መስፍን እና ተዋቸው ዳምጤ ሲሆኑ፣ የክሱ ይዘትም በ1996 ዓ.ም የወጣውን የኢፌዴሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 32(1)(ሀ) እና 487(ሀ) እንዲሁም 490(3) የተመለከተውን በመተላለፍ መሆኑ ተገልጹዋል፡፡ 
ተከሳሾች መንግስት በጠራው ሰልፍ ላይ ህዝቡን የማነሳሳትና ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም ሲናገሩ፣ ‹‹በፖሊስና በህዝብ ላይ ድንጋይ በመወርወር ረብሻና ሁከት፣ ብጥብጥ እንዲነሳና ሰልፉ እንዲታወክ በማድረጋቸው በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን›› እንደተከሰሱ ተመልክቷል፡፡
ሁሉም ተከሳሾች ፍርድ ቤቱ የዋስትና መብታቸውን እንዲያስጠብቅላቸው የጠየቁ ቢሆንም፣ አቃቤ ህግ ‹‹ተከሳሾቹ የምርጫ ወቅትን በተመለከተ ቀጣይ ሰልፎች ሊደረጉ ስለሚችሉ ሰልፎች ላይ ሊሳተፉ ይችላሉ…›› በማለት ባቀረበው ‹መከራከሪያ› ዋስትና ሊከለከሉ ችለዋል፡፡ በዚህም ተከሳሾቹ 11 ቀናት ቀጠሮ ተሰጥቶባቸው ወደ ቂሊንጦና ቃሊቲ እንዲወርዱ ታዝዟል፡፡ 
በሌላ ዜና ባለፈው አርብ ክስ ተመስርቶበት የ6000 ብር ዋስትና ተጠይቆበት በዛሬው ዕለት ብሩ ተከፍሎ ከእስር እንዲለቀቅ ተደርጎ የነበረው የሰማያዊ አባል ወጣት ቴዎድሮስ አስፋው ከእስር እንደወጣ ሲቪል በለበሱ ሰዎች ታፍኖ ወደ ሶስተኛ ፖሊስ መወሰዱ ታውቋል፡፡ ወላጅ እናቱ ወደ ሶስተኛ ፖሊስ ሄደው ልጃቸው እዚያ ስለመኖሩ ቢነገራቸውም ለሶስት ቀናት ያህል ግን ሊያዩት እንደማይችሉ እንደገለጹላቸው ተናግረዋል፡፡

No comments: