Sunday, July 27, 2014

የ53 አመቱ አባት የጥቁር ሽብር ሰለባ አስገራሚ ክስተት

July 27/2014
ቢቢኤን ራድዮ እንዳቀረበው፦
መንግስት ሀምሌ 11 በወሰደው የጭካኔ ተግባር ወጣቱ ወንዱ ሴቱ ህጻናቱ አዛውንቱ የጥቁር ሽብሩ ሰለባ ሁነዋል፡፡ የዚህ ጥቃት ሰለባ ከሆኑት መካከል የ53 አዛውንት ሰው ይገኙበታል፡፡ ይህ በምስሉ ላይ የምትመለከቱት የርሳቸውን በከፍተኛ ድብደባ የቆሰለ ሰውነት ነው፡፡
የ53 አመቱ ሰው ከቢቢኤን ሬድዪ ጋር የደረሰባቸውን ነገር አስመልክቶ ቆይታ አድረግዋል፡፡ ሙሉዉን ቆይታ ከራሳቸው አንደበት የምትሰሙት ይሆንና በመጠኑ ቀንጭበን በጽሁፍ እናካፍላችሁ፡፡
Muslim abat
የጁምአን ሶላት በአንዋር መስጅድ ለመስገድ ዘግየት ብለው ስለደረሱ ውጭ አስባልት ላይ ነበር መስገጃ ካኪ ያነጠፉት፡፡ ምንም ተቃውሞ ባልተጀመረበት ሶላትም ባልተሰገደበት ሁኔታ ፖሊሶች መስግጃውን አንሱ በማለት ትንኮሳ ጀመሩ ይላሉ ግለሰቡ፡፡ እርሳቸውም ከእድሚያቸው አንጻር ሁኔታዎቹን ለማረጋገት ይሞከራሉ፡፡ በዚህ ሰአት ግን የፖሊሶቹ ምላሽ ያልጠበቁት ነበር ፡፡ በያዙት ዱላ ለሶላት የተሰበሰበውን ምእምናን መደበደብ ጀመሩ፡፡ እኚህ አባትን በርካታ ፖሊሶች ከበው ይደብድቡዋቸው ጀመር፡፡
የዱላ ውርጅብኝ የበዛባቸው አባትም ወደ መዲና ህንጻ ሩጠው ይገባሉ፡፡ ፖሊሶች ተከትለው ከገቡ በሁላ እየጎተቱ መሬት ላይ በመዘርጋት ዘግናኝ ድብደባ እንደፈጸሙባቸው ይናገራሉ፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ ከእድሜያቸው አንጻር በዚሁ እንኩዋን አልተዋቸውም፡፡ በጾመኛ አንጀታችው እየደበደቡ ወደ ልኩዋንዳ ፈጥኖ ፖሊስ ማሰልጠኛ ወሰዱዋቸው፡፡
ልኩዋንዳ ሲደርሱ እሳት እየነደደ ነበር ይላሉ፡፡ ከዛም የሴቶችን ጅልባብ ሀይማኖታዊ አልባሳት የሳቸውም ኮፍያ ጭምር በሳት ተቃጠለ፡፡ ወደ ሰፊ ሜዳ ከወሰዱዋቸው በሙሉ በግራና በቀኝ ዙርያውን ፖሊሶች ተደርድረው በመሃል እየቀጠቀጡ ከፍተኛ ድብደባ ተፈጸመባቸው፡፡ በ120 በ90 ሜትር የሚሆነውን ሜዳ እያዞሩ ቀጠቀጡን ሲሉ ይናገራሉ አዛውንቱከድብደባውም ሌላ ኮፍያቸው ጫማቸው ተቃጥልዋል፡፡ አጸያፊ ስድብም ተሰድበዋል፡፡ ዱላቸው ተሰባብሮ ሲያልቅ እሳት ረመጡን እንዲረግጡ አድረገዋቸው፡፡ እስከ ሌሊቱ 9 ሰአት ይህ ሁሉ ሲፈጸምባቸው ጾመኛ ነበሩ፡፡
ዘጠኝ ሰአት ላይ አውጥተው ጣልዋቸው፡፡ ሌሊት ለተሃጁድ ሶላት የሚሄዱ ሰዎች ሲያገኙዋቸው አለቀሱ፡፡ የ53 አመቱ አባት ጀርባቸው በምስሉ እንደሚታየው ቆስሉዋል:: ራሳቸው ተፈርክስዋል፡፡
በመጨረሻም ምን ይላሉ ሲል የቢቢኤን ጋዜጠኛ አብዱረሂም ላቀረበላቸው ጥያቄ አዛውንቱ አስገራሚ ምላሽ ሰጡ፡፡ እንዲህም አሉ ”የደረሰብኝ ነገር የሰው ልጅ በወገኑ ላይ የሚፈጸመው ተግባር አይደለም፡፡ ይህም ሁኖ ግን ሰላማዊነታችንን በፍጹም መተ ው የለብንም፡፡ ድምጻችን ይሰማ ጁምአ ቢጠራ ሰባራ እጄን ወንድሞቼ ጋር እሰለፋሉ የምንፈልጋት ሰላማዊ ትግል ውጤት እስክትመጣ ሌላ ምን አደረጋለሁ፡፡ ለሙስሊሙ የማስተላልፈው ሰላማዊ ትግላችን መቀጠል አለበት፡፡ ይህን ስል ሁሉም ይደብደብ ማለቴ ሳይሆን እውነተኛ ነጻነታችን የምትከበርባት ሀገር እስክትመጣ መታገል አለብን፡፡ አንድነታችን ይዘን ጥያቄያችን እስኪመለስ እነሱ ይግደሉን እነሱ ይጨፍጭፉን እኛ በሰላማዊ ትግል አሻራችንን እናሳረፍ፡፡ በኔ የደረሰው ኢምንት ነው በጥይትም የተመቱ አሉ እንበርታ ይላሉ የ53 አመቱ አባት፡:
ለመስማት ተከታዩን ሊንክ ይጫኑ
http://goo.gl/pYP0hD
በጣም አነስተኛ መጠን ያለው ሊንክ
http://goo.gl/NBc1Kx

የኢትዮጵያ አየር ኃይል በ1966ቱ አብዮት – ከሮበሌ አባቢያ

July 27/2014
ታሪክማ ሊረሳ አይገባም
ታህሣሥ 7 ቀን 1966 ዓ.ም የነጌሌ ጦር አባሎች ለአዛዦቻቸው ላለመታዘዝ ወሰኑ። የምድር ጦር አዛዥ የነበሩት ሌተና ጄኔራል ድረሴ ዱባለ አማፅያኑን እንዲያረጋጉ በታዘዙት መሠረት የመንግሥት ልዑካን ይዘው ታህሣሥ 23ቀን 1966 ዓ.ም ነጌሌ ጦር ሠፈር ገብተው ሠራዊቱን ሲያነጋግሩ የተጠበቀውን መልስ ስላልሰጡ እርሳቸውም ከነተከታዮቻቸው ታገቱ፡፡ በ27/4/66 በአየር ኤታማጆር ሹም በጄኔራል አበራ ወልደማርያም የሚመራ የዓፄው ልዑካን ቡድን ወደ ነጌሌ ተልኮ በመደራደር፣ ታጋቾችን ሊያሰፈታ ቻለ። ነገር ግን ያድማው መነሻ ኢኮኖሚ-ተኮር ቢመስልም፣ አንደምታው በሌሎችም የጦር ኃይሎች ካምፖችም ውስጥ በመዛመቱ ምክንያት፣ መለዮ ለባሹ ለአብዮት ፍንዳታ አጋር ኃይል እንደሚሆን መሠረታዊ ለውጥ ለሚፈልጉ ተራማጅ ኃይሎች የምሥራች ሆኖ በግልፅ ይታይ ነበር።
የነጌለው አድማ የፖለቲካ አጀንዳ ይዞ ደብረ ዘይት የአየር ኃይል ጠቅላይ መምሪያ ወደሚገኝበት ብቅ አለና የጎጃሙን ተወላጅ ማስተር ቴክኒሺያን ግርማ ዘለቀን እና በሕቡእ አብረው የተደራጁትን እነ ሲኒየር ቴክኒሽያን አበበ አረጋን፣ እንዲሁም ከጎረቤት የአየር ወለድ ጦር የተባበሩለትን ባለሌላ ማእረጎችን አገኛቸው። እነርሱም ታሪክ ለመሥራት ለአብዮታዊ ተግባር ተነሱ! በዚህ ጽሁፍ ውስጥ  ዘርዘር አድርጌ እንደምገልጸው፣ ጀግናው ግርማ ዘለቀ ከፍተኛ መኮንኖችን አግቶ የአየር ኃይሉን ከተቆጣጠረ በሗላ ከንጉሠ ነገሥቱ ጋር በስልክ በቀጥታ ፖለቲካዊ ድርድር ጀመረና አስደናቂ ወጤት አስገኘ። ባላሌላ ማዕረጎች (non-commissioned officers)፣ አየር ኃይልን የሚያክል አግራዊ ተቁአም ተቆጣጥረው የፖለቲካ ለውጥ ሲያስገኙ በየትም ተነግሮ አያወቅም።
የ“እኛና አብዮቱ” ደራሲ ጠቅላይ ምኒስትር ፍቅረስላሴ ወግደርስ የአየር ኃይል መኮንን ስለነበሩ  ይህን ምዕራፍ በመጽሐፈቸው ለምን እንዳላካተቱት በመገረም ለጊዜው በጥያቄ ልለፈው።
ወደሚቀጥለው አርዕስት ከመሸጋገሬ በፊት፣ በሙስና ያልተበከሉ የወያኔ የመከላከያ፣ የደህንነተና የበላይ ከበርቴ አለቆቻቸውን በቀጥር ስር በማወወል የጀገናውን ግርማየ ዘለቀን ምሳሌ በመከተል ሰላማዊ ለውጥ ለማምጣት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እዲያደርጉ መማፀን ከዓላማዬ ውስጥ አንዱ ነው።
ስለዚች ጽሑፍ ዓላማ ጥቂት ልዘርዘር
አብዮቱ በየካቲት ወር 1966 ዓ.ም (18/6/66) ሲፈነዳ፣ ለብዙሀኑ ብሩህ ተስፋ  የፈነጠቀ መስሎ ታይቶ ነበር። ለጥቂት ጊዜም ቢሆን ደም ያላፋሰሰ ሰላማዊ ትግል ሂደቱ፣ “ኢትዮጵያ ትቅደም፣ ያለምንም ደም” በሚል መፈክር ዙሪያ ሕዝቡን አሰልፎ እንደ ነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው።
በ1966ቱ የኢትዮጵያ አብዮት በቀጥታ የተሳተፍነውና በውስጡም ስንጓዝ ያጋጠሙንን ተግደሮቶችና የተከሰቱትን ሁነቶች ለታሪክ ጸሐፊዎች በማስረጃ ማቆየት የዜግነት ሞራላዊ ግዴታ ነው። እግዚአብሔር ረዢም እድሜ ሰጥቶኝ እስከ አሁን ስለአደረሰኝ በአብዮቱ ሂደት ወቅትና በፊት በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ ላይ በሀላፊነት ላይ ተመድቤ ሳገለግል፣ ካካበትኩት የሥራ ልምድና በዚያም ሳቢያ በእጄ የገቡትን ሰነዶችና የመዘገብኳቸውን የግል ማስታወሻዎች በመመርኮዝ፣ በኔ አስተያየት ወቅታዊ ናት ብዬ ያመንኩባትን፣ ይህችን አጭር ጽሑፍ ለአንባቢ አቅርቤያለሁ።
ስለሆነም፣
  • በ1966ቱ አብዮት መዳራሻና ዋዜማ የዓፄው መንግሥት ወታደሮችና የፖሊስ ሠራዊት ወገናዊነታቸውን ለሕዝብ በማሰየት ዘውዳዊውን አገዛዝ በመገርሰስ ያስመዘገቡትን አኩሪ ታሪክ፣ የወያኔም የመከላከያ ሠራዊት፣ የፈፌዴራል ፖሊስና የብሔራዊ ደህንነት ተቋም አባላት በበኩላቸው በአርአያነት እንዲከተሉ በአጽንኦት መምከር አንዱ ዋና ዓላማዬ ነው።
  • የዛሬው የኢትዮጵያ ትውልድ፣ ከ1996 ጀምሮ ላለፉት 40 ዓመታት በእናት ሀገራችንና በህዝቦቿ ላይ ያደረሰው ውድቀት እንዳይደገም ከታሪክ በትክክል ተገንዘቦ ላንዴና ለመጨረሻ የሚደረገውን የነጻነት ዘመቻ እንዲቀላቀል አሳስባለሁ።
  • ጀግናው ማስተር ግርማ ዘለቀ እና ቆራጥ የትግል ጓደኞቹ እንደነ ሲኒየር ቴክኒሽያን አበበ አረጋ፣ ማስተር ቴክኒሽያን አየለ ኃይሌ የመሳሰሉትን ይዞና የአየር ወለድ መለዮ ለባሾችን አሰተባብሮ፣ ከሁለቱም ወገን ከፍተኛ መኮንኖችን አግቶ፣ አብዮታዊ የፖለቲካ ጥያቄ ለአፄው መንግሥት ስላቀረበ፣ የ ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ኃብተወልድ ካቤኔ በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ፣ የስንብት ደብዳቤ ለዓፄው አቅርቦ ደም ሳይፋሰስ በሰላም መሰናበቱንና በልጅ እንዳልካቸው ካቢኔ መተካቱን ላንባብያን ሳስታውስ፣ ምትክ የማይገኝላቸው ጠቅላይ ምኒስትር አክሊሉ ላሳዩት አርቆ አስተዋይነትና የፖለቲካ ብስለት አድናቆቴን እየገለጽኩ ነው።
በ1966ቱ አብዮት የኔን ተሞክሮ በተመለከተ በተለይ ለታሪክ ጸሐፈት የሚሆን አንድ መጽሐፍ ለማዘጋጀት ማቀዴን በዚህ አጋጣሚ እገልጻለሁ። ምክንያቱም፣ ጠቅላይ መምሪያው የሚገኝበት ግዙፍ የደብረ ዘይት አየር ኃይል ጣቢያ፦
  • ምሁራን ከአዲስ አበባና ካካባቢዋ እንዲሁም ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካ፣ ከአፈሪካና ከእስያ እየመጡ ፣ የተወያዩበት፣ ያስተማሩበት፤
  • ፖሊሲና ፕላን የሚዘጋጅበት፤የአብዮቱን ፍንዳታ ተከትሎ ከባድ የውሳኔ ሀሳቦች የፈለቁበት፤
  • የአብዮቱን ፍንዳታ ተከትሎ ልዩ ልዩ የፖለቲካ ድርጅቶች አባሎቻቸውን በሕቡእ ለመመልመል የተረባረቡበት፤
  • የአየር የአየር ኃይል ሠራዊት ተሰብስቦ የዘውድ ሥርዓትም ሆነ የወታደራዊ መንግሥት በፍፁም ስለማንፈልግ፣ ሕዘባዊ መንግሥት እንዲቋቋም የውሳኔ ሃሰብ የሰጠበት፤
  • የዳበረ ዘመናዊ ቤተ መጻሕፍት የተከማቹበት፤
  • ዘመናዊ ላቦራቶሪዎችና የጥገና ወረክሾፖች የሚገኙበት፣
  • ለ34 ለዩ ልዩ ሙያዎች የሥልጠና ፋሲሊቲ የተዘጋጀበት፤
  • የንጉሠ ነገሥቱ የከፋፍለህ ግዛው ሥርዓት ተንኮል የተጋለጠባት፤
ስፍራ ነው። በእጩ መኮንንነት ተምሬ የተመረቅሁበት፣ ያስተማርኩበት እስካ ከፍተኛ ደረጃ አዛዥነት የሠራሁበት አመቺ ስፍራ እንደመሆኑ፣ መረጃዎችን ማግኘት ቀላል ስለሆነልኝ መጽሐፉን ለማዘጋጀት በእግዚአብሔር ፍቃድ ሥራዬ እንደማይከብደኝ አምናለሁ።
ከአብዮት ፍንዳታ እስከ ወታደራዊ ደርግ ምሥረታ
አብዮቱ ሊከሰት መዳረሻ ላይ ሕዝባዊው ንቅናቄ እየጎለበተ በመሄዱ መንግሥት ተጨነቀ። ሁኔታውን ለማቀዘቀዝ የአድማ መሪዎች ከጦሩ ውስጥ ጃንሆይ ፊት ቀርበው ይቅርታ እንዲለምኑ መንግሥት መላ መታ። የጨነቀው እርጉዝ ያገባል እንደሚባለው!
ሴራው ግን አልሰራም። ከአየር ኃይል ከኔ ጭምር በርካታ መኮንኖችና ባለሌላ ማዕረጎች፣ እስከዛሬ ግልጽ በልሆነልኝ መመዛኛ ተመርጠን ኢዩቤልዩ ቤተመንግሥት ሄደን ለግርማዊነታቸው ታማኝነታችንን እንድንገልፅና በየቦታው የተፈጠረውን አለመረጋጋት እንድናወግዝ የተሰጠንን መመሪያ ለመተግበር፣ በአውቶቡስ ተሳፍረን ወደ አዲሰ አበባ (ሸገር) ጉዞ ጀመርን። ተልዕኳችን ለሚዲያ ፍጆታ የታለመ ተንኮል በመሆኑና እኛ መጠቀሚያ በመደረጋችን ነገሩ በጣም አናደደን። ወደ አዲስ አበባ እሩ መንገድ እንደተጓዝን፣ በታቀደው ጊዜ ቤተ መንግሥት ላለመድረስ፣ እቃ ረስተናል፣ ዩኒፎርም መቀየር አለብን በሚል ሰበብ ሹፌሩ ወደ ደብረዘይት መኮንንኖች ሠፈር እንዲመለስ በፈጠርነው ዘዴ ጊዜ ለማባከን ተቻለ። ዘግይተን ከቤተመንግሥቱ ስንደረስ፣ አዛዣችን ሜጀር ጄኔራል አበራ ወልደማርያም በንዴት ጦፈው ዋናው በር ላይ ጠበቁን። ሌሎች ሰዓታቸውን ጠብቀው የመጡት የምድር ጦር፣ የብሔራዊ ጦር፣ እና የፖሊስ ሠራዊት ተወካዮች የተፈለገውን የታማኝነትና የአድመኞችን ኩነና መግለጫ ካሰሙ በሗላ ዓፄው ስለአሰናበቷቸው፣ አዛዣችን ምርጫ ስላልነበራቸው በብስጭት ተቆጥተው ወደ ቤተመንግሥቱ ግቢ ሳንገባ ከውጪው አሰናበቱን።
የተፈለገውን ታማኝነት ባላመግለፃችን ረክተን ተመልሰን ደብረ ዘይት ከተማ ስንደርስ፣ ያልጠበቅነው ሁኔታ አጋጠመን። የአየር ኃይልና የአየር ወለድ መለዮ ያጠለቁ ባለሌላ ማዕረጎችና ወታደሮች ተሰባጥረው ባንክ ቤቱን አዘግተው ጥበቃውን ተቆጣጥረውታል። ትላልቅ ሱቆች ተዘግተዋል። ወደቤቴ ሄጄ ምሳዬን ከበላሁ በሗላ በግል መኪናዬ ወደቢሮዬ ሄድኩ።
ማስተር ቴክኒሽያን ግርማ ዘለቀ፣ የአየር ኃይል መሣሪያ ግምጃ ቤት ሀላፊ እንደመሆኑ የመጋዘኑን በር ከፍቶ በውስጡ የሚገኙትን የነብስ ወከፍ መሣሪየዎች ለባለሌላ ማዕረጎች (ቴክኒሽያኖች) ካስታጠቀ በሗላ፣ በርሱ መሪነት በሕቡእ ይንቀሳቀስ የነበረው ቡድን ይፋ ወጣና ደብረ ዘይት የምንገኝ የንጉሠ ነገሥቱ አየር ኃይል ከፍተኛ የአመራር ባለሥልጣናት ታግተን በተለያዩ ስፍራዎች የካቲት 18 ቀን 1966 ዓ.ም ታጎርን፡፡ የጦር ሠፈሩም ባሳሪዎቻችን ቁጥጥር ስር ዋለ። ከሻለቃ ማዕረግ በታች ያሉ መኮንንኖች ያልታገቱ ቢሆንም ምንም ዓይነት መሣሪያ ሳይታጠቁ በግቢው (ካምፕ) ውስጥና ውጪ ይንቀሳቀሱ ነበር።
ከላይ ከተጠቀሰው እገታ በሗላ፣ አጋቾች ዐቢይ የፖለቲካ ለውጥ እንዲደረግ በርካታ ጥያቄዎችን ለመንግሥት አቀረቡ። በዚህ ሂደት ውስጥ ማስተር ቴክኒሽያን ግርማ አልፎ አልፎ ከግርማዊነታቸው ጋር በስልክ እየተገናኘ ለሚያቀረቡለት ጥያቄዎች መልስ በመስጠት ይደራደር ነበር። ለምሳሌ እናንተ በአድማ ላይ እያላችሁ ሱማሊያ የኢትዮጵያን ድምበር አልፋ ብትወር ምን ይደረጋል ብለው ጃንሆይ ሲጠይቁት፣ አድማችንን በቅጽበት አቁመን ወራሪዉን በመግረፍ ይህንን የጋለ ቁጣችንን በጠላት ላይ እናበርዳለን ሲል ማስተር ቴክኒሽያን ግርማ ዘለቀ እንደመለሰላቸው ከእገታ በሰላም ከተለቀቅን በሗላ ለማወቅ ችያለሁ። እውነትም ማ/ቴክኒሽያን ግርማ እንዳለው፤ አብራሪዎች እና ቴክኒሲያኖች ስለአልታገቱ ተዘጋጅተው በተጠንቀቅ ላይ ስለነበሩ ተዋጊ አውሮፕላኖች ከደብረ ዘይት፣ ከድሬዳዋና ከአስመራ አየር ጣቢያዎች በመነሳት፣ ከሶሰተኛው ክፍለ ጦር ጋር በመተባበር ባጭር ጊዜ ውስጥ ውጊያ ለመግጠምና ጠላትን ለማዳሸቅ ይቻል ነበር።
በቁጥጥር ስር የዋልነው ከፍተኛ መኮንኖች በታሰርን በሶስተኛወ ቀን ከያለንበት ተወስደን በባለ ሌላ ማእረጎች ክበብ ምግብ ቤት ምሳ ከበላን በሗላ በአቅራቢያው ከሚገኝ አንድ ሰፊ አዳራሽ ውስጥ እንድንሰበሰብ ተደረገ። ሁለት ባለሌላ ማዕረግ ቴክኒሽያኖች፣ አንዱ ሽጉጥ ሌላው ኦቶማቲክ (ኡዚ) የያዘ ከፊታችን ቆሙ። ዙሪያውን ስመለከት ጥቁር ቱታ የለበሱ ፊታቸው ላይ ቁጣ የሚታይባችው ኦቶማቲክ መሳሪያ የታጠቁ ቴክኒሲያኖች ቆመዋል። ሽጉጥ የያዘው ቴክኒሽያን፣ እምባ እየተናነቀው አስተምራችሁ አሳደጋችሁናል፣ በማህበራዊ ኑሮም ተሳስረናል፣ አበልጆችም የሆን አለን በማለት እርምጃ ለመውሰድ የተገደዱበትን በመግለፅ ላይ እያለ ንግግሩን ሳይጨርስ፣ ከአጠገቡ የቆመው ጓደኛው ከመቅጽበት ሽጉጡን ከጁ ነጠቀውና ድራማው አበቃ። የገረመኝ ነገር ይህ ሁሉ ሲሆን ታጋች መኮንኖች ሁኔታውን ከቁብ አልቆጠነውም፡፡
ድራማው ቢያበቃም እስከዛሬ ያልተመለሱ ጥያቄዎችን አጭሮ አልፏል። ዕውን ሊረሽኑን ኖሯል? ወይስ መንግሥት የአጋቾችን የፖለቲካ ጥያቄ በአስቸኳይ እንዲመልስ ለማስገደድ? የክብር ዘበኛ አዛዠ ሌተና ጄኔራል አበበ ገመዳ የአየር ኃይልን ጦር ሠፈር በመድፍ ኢላማ ወስጥ አስገብቼዋለሁና ጃንሆይ ከፈቀዱልኝ ልምታው ብለው ፈቃድ ጠይቀው ስለተነፈጉ፣ አጋቾቻችን ሕይዎት ለማጥፋት እርምጃ ከመወሰድ ተቆጥበው ይሆን?
 ጃንሆይ ምህረት የማድረጋቸውን ዜና ለማሰማት፣ ምክትል የእልፍኝ አስከልካያቸው ሜጀር ጄኔራል አሰፋ ለማ፣ የመጡ መሆኑን አጋቾቻችን አበሰሩን። ከዚያም ከአየር ኃይል ካምፕ ውጪ ጋራ በሩ ተብሎ በሚጠራው ተራራ አቅጣጫ በሚገኝ ጥቅጥቅ ባለ ቁጥቋጦ በተከበበ ገላጣ ሜዳ ላይ ታጋጆች ከፍተኛ የአየር ኃይል መኮንንኖች ብቻ እንድንኮለኮል ተደረገ። ቀደም ሲል ከኛ ጋር ታግተው የነበሩት የአየር ወለድ ጥቂት መኮንንኖች አልነበሩም። ለምን እንደሆነ እስከ አሁን ይገርመኛል።
ምን ሊመጣ ነው ብለን ስንጠባበቅ፣ የአየር ወለድ አዛዥ ኮሎኔል የዓለምዘውድ ተሰማ፣ በጥይት የተሞላውን ዝናር በወገቡ ዙሪያና ከጀርባው በትከሻው ላይ እስከ ጉልበቱ ድረስ አንዠርንጎ መትረየሱን አንግቦ ከጥቂት አጃቢዎቹ ጋር ከቁጥቋጦ ውስጥ ወጥቶ ኩስትር ብሎ ከታጋቾች ፊት ለፊት ቆመ። ነገሩ ያልጠበቅነው እንደመሆኑ ይህ ወራሪ ከጎረቤታቸን በማን ታዞ ነው የመጣብን ሳንል አልቀረንም።
የኮሎኔል የዓለም ዘውድ ወገናዊነት ከማን ጋር እንደሆነ ገና ንግግሩን ሲጀምር ግልፅ ሆነ። ግርማዊነታቸው ይቅርታ ያደረጉልን መሆኑን አበሰረን። ለሠራዊቱም በወር ሰባት (7) ብር ደሞዝ በዓፄው መልካም ፍቃድና ትእዛዝ ለመከላከያ ሠራዊት የተጨመረ መሆኑን አስታወቀን። ዝምታን ያዘለ ተቃውሞ ለጥቂት ጊዜ ሠፈነ። ከዚያ እጄን አወጣሁና ለመሆኑ ደሀው ገበሬ ከየት አምጥቶ ነው የተባለውን የደሞዝ ጭማሪ የሚከፈለን ብዬ ላነሳሁት ጥያቄ መልሱ በደፈናው ገንዘቡ አለ ከየትም ይገኛል ሆነ። ያሳፍራል! ቀጥሎም ከታገትነው ውስጥ አንዱ ኮሎኔል (ጌታሁን እጀጉ) እኛ ታሳሪ፣ እናንተ አሳሪና መሐሪ የተሆነበት ምክንያት እንቆቅልሽ እንደሆነበት አምርሮ ተናገረ። ለዚህ ጠንካራ ተቃውሞ ኮሎኔል የዘውድዓለም ምላሽ አልሰጠም፤ ታጋቾች ኮሎኔሉን በትዝብትና በንቀት ዓይን ይመለከቱት ነበር። ስብሰባውም በዚህ አበቃና ወደ ሌላ ቦታ ተወሰድን። ምንስ አጥፍተን ነው የጃንሆይ ‘ምህረት’ በአየር ወለድ አዛዠ የሚበሰርልን የሚለው ጥያቄ እስከዘሬ ድረስ በአዕመሮዬ ውስጥ ይመላለሳል።
ከኮሎኔል የዓለምዘውድ አሳፋሪ ድራማ ተላቀን ወደ ካምፓችን እንድንመለስ ተደረገና በአየር ኃይል ሠልጣኞች ክበብ አዳራሽ ውስጥ ተሰበሰብን። መልከ መልካሙ አጅሬ ግርማ ዘለቀ ብቅ ብሎ እፊታችን ቆመ። ማራኪው ቁማናው እንዳለ ሆኖ የሚያማምሩት ትላልቅ ዓይኖቹ እንቅልፍ ከማጣት ምክንያት ይመስለኛል ቀልተዋል። ግርማ፣ ከፊትለፊቱ ለተቀመጥነው ከሻለቃ እስከ ብ/ጄኔራል ማዕረግ ላይ ለምንገኝ ከፍተኛ መኮንኖች፣ ስለታሰርንበት ምክንያት እጅግ የሚመስጥ አጭር ንግግር አደረገ። ከአንድ መሪ የሚጠበቅ በሳልና ድንቅ ንግግሩንም፣ “እኛ በያዘችሁት ሥልጣን ስሩበት ብለን ተነሳን እንጂ ልንነጥቃችሁ አይደለም” በማለት ዘግቶ በሰላም አሰናበተን። ጥሪውና መልእክቱ ወቅታዊውን ሁኔታ ያካተቱ ጥርት ያሉ በመሆናቸው፣ ታጋቾች ትንፍሽ ሳንል አንዳች ጥያቄም ሆነ አስተያየት ሳንሰጥ ወደየቤታችን ሄድን። ተዳክሞ የነበረው የመንግሥት አስተዳደር ባስከተለው በደል ተነሳስተው፣ የምናዛቸው ባለሌላ ማዕረጎች የፖለቲካ ለውጥ ጥያቄ እስኪያነሱ ድረስ እኛስ ከፍተኛ መኮንኖች ምን እንጠብቅ ነበር? በበኩሌ መንፈሳዊ ቅናት ተሰምቶኝ እንደነበር አልክድም። ለውጡንም ሰላማዊ እስከሆነ ድረስ ከልብ ለመደገፍ ወሰንኩ።
መሪ ይወለዳል ወይስ በሥልጠና ይታነፃል? በኔ እምነት ግርማ ዘለቀ ከመሪነት ባሕርዩ ጋር የተወለደ ነው። በየካቲት 1966 አብዮት ያሳየው አመራረና ብስለት ካስገኘው ውጤት ጋር ሲገመገም፣ የመንግሥት ካቤኔ በሰላም ሥልጣኑን ሲለቅ በኢትዮያ ታሪክ የመጀመሪያው ነው።ይህ በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የታየ ዐቢይ ሰላማዊ ለውጥ ነው ለማለት እደፍራለሁ። ለዚህም ድንቅ ክንውን ማስተር ቴከኒሽን ግርማና አብዮታዊ ግብረ-አበሮቹ የሚመሰገኑ ናቸው። ለዚህ አንፀባራቂ ድል፣ ታሪክ ክሬዲቱን  ለግርማና ለትግል ጓደኞቹ እንደሚሰጥ ጽኑ ተስፋ አለኝ።
የካቲት 20 ቀን 1966 ዓ.ም፣ የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ኃብተወልድ ካቢኔ የሥልጣን መልቀቂያ ደብዳቤ ለንጉሠ ነገሥቱ  በይፋ ያቀረበው ጥያቄ ከፀደቀ በሗላ፣ የዘውድ ምክር ቤት ሌ/ጄኔራል ዐቢይ አበበ እንዲተኩ ቢያሳሰብም እርሳቸው ፈቃደኛ ሁነው ባለመገኘታቸው፣ ልጅ እንዳልካቸው መኮንን ተሹመው የአክሊሉ ካቢኔ በሰላም ሊተካ ቻለ። የቀድሞው ካቢኔ በሰላም ከሥልጣን መውረድ በምእራባውያን ዲፐሎማቶች ዘንድ እንደ ሰላማዊና ደም ያላፋሰሰ ለውጥ የተወደሰና የተደነቀ መሆኑን አንድ የፈረንሳይ ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ለሥራ ጉዳይ ደብረ ዘይት መጥተው ስለነበር እግረመንገዳቸውን ቢሮዬ ጎራ ብለው እንደነገሩኝ አስታውሳለሁ። ምን ጊዜም ምትክ የማይገኝላቸው፣ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ፣ ደም እንዳይፋሰስ በማሰብ ላሳዩት በሳል አመራርና ሥልጣን ለመልቀቅ ላደረጉት ውሳኔ የላቀ ምሥጋና ይገባቸዋል እላለሁ።
ከእገታ ከተለቀቅን በሗላ፣ ሥነሥርዓትና ወታደራዊ ዲሲፕሊን በማስፈን አመራር መስጠት አንገብጋቢ ጥያቄ ሆነ። የዓፄው ሥርዓት የከፋፍለህ ግዛው ፖሊሲውን መተግበር ቀጥሎበታል። ስለሆነም ከጎረቤታችን ከአየር ወለድ ጦር ጋር መቃቃር ቀጥሏል። ሕዝባዊ እንቅስቃሴውም እያየለ ቀጥሏል። ስለዚህ ተወዳጁ አዛዣችን ብ/ጄኔራል አሰፋ ገብረእግዚ ሠራዊቱን  ሰበስበው ምን መደረግ እንዳለብት በእሳቸው መሪነት ሰፊ ውይይት ተካሄደ። እጄን አወጣሁና፣ የሀገር መውደድ የሚለካው በክንዳችን ላይ በለጠፍነው ወይም በትከሻችን ላይ በተሸከምነው ማዕረግ ሳይሆን ከእያንዳንዳችን ልብ ውስጥ ከሚመነጭ ፍቅር ነውና፣ ሕዝባዊ እንቅስቃሴውን በሕቡዕ የምትመሩት ባለሌላ ማዕረጎች በዚህ አንገብጋቢ ጉዳይ ተመካክራችሁበት አቋማችሁን በፍጥነት ወስናችሁ ውጤቱን ለአዛዣችን አስታውቁ ብዬ ሀሳብ ሰጠሁ። ታዳሚው ባንድ ድምፅ በሀሳቡ ተስማማና ያንኑ ሌሊት መልካም ዜና የሚያበስር ወረቀት ተበትኖ አደረ። ሙሉ ወታደራዊ ዲሲፕሊን ሰፍኖ፣ አዛዥና ታዛዠ ተከባበሮ፣ ሠራዊቱ በአንድነት የአየር ኃይሉን ግዳጅ በስነሥርዓት እንዲወጣ በተበተነው ወረቀት ውስጥ መጻፉ በእረግጥም አስደሰታች ነበር። መለዮ ለባሹ የተነሳለትን አብዮታዊ ዓላማ ሳይዘነጋ፣ እንደተለመደው ጢሙን ተላጭቶ፣ አጎፍሮ የነበረውን ፀጉሩን አሳጥሮ ተስተካክሎ፣ እና ንፁህ የደንብ ልብሱን ለብሶ ግዳጁን ለመወጣት ዝግጁነቱነን በተግባር አረጋገጠ።
ወደ ሌላ አርዕስት ከመሸጋገሬ በፊት ከእገታ ከወጣን በሗላ ስለተወዳጀሁት ጀግና ስለ ግርማ ዘለቀ ጥቂት ልበል።
ከእገታ ከወጣን በሗላ ግርማ ዘለቀ ልክ የታገትን እለት ማታ መኖሬያ ቤቴ ድረስ መጥቶ ቤተሰቤን  ለሠፈሩ ጥበቃ እንደተደረገ አረጋግጦላቸው እንደነበር ስለተነገረኝ አድመኞቹ በኔ ላይ ምንም ቅሬታ እንዳልነበራቸው ተሰማኝና ወዳጅነታችን ቀጠለ።
የደርግ አመራር ብቃት ማነስና የሚከተለው የሶሽሊሰት ፍልስፍና ግርማን አላስደሰተውም፡፡ ፍልስፍናው፣ ኢትዮጵያ ለምትገኝበት የፊዉዳል ሥርዓት ፈፅሞ አይሠራም እያለ አጥብቆ ይከራር ስለነበር ከትግል ጓደኞቹም ጋር ሳይቀር ከሶሽያሊስት ርዕዮት አቀንቃኞች ጋር ልዩነት ተፈጠረ።
ደርግ ግርማን የማረሚያ ቤት ሀላፊ አድርጎ በመሾም ከፖለቲካ አርቆት ነበር። አጅሬ ግን ስድቡን አልተቀበለውም፤ ወደ ሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ ሄዶ ከፀረ-ደርግ ሐይሎች ጋር ለመቀላቀል ሲጓዝ ጎጃም ውስጥ ዳንግላ ሲደርስ ላስቆሙት ወታደሮች እጁን ላለመስጠት በመታኮስ ገሎ በተኩሱ ልውውጥ  እሱም ሞተ። በኔ እምነት፣ አትዮጵያም ጀግና ልጇን አጣች!!!
ፋሺስትን-አርዕድ ሸጋው አርበኛ የብቸናው ተወላጅ ደጃዝማች በላይ ዘለቀ አራዳ ጨርቅ ተራ አራተኛ ፖሊስ ጣቢያ አጠገብ ሲሰቀል፣ አንቺ ኢትዮጵያ ወንድ አይብቀልብሽ ብሎ መራገሙ ይታወቃል። የጎጃሙን ተወላጅ ጀግናውን ግርማ ዘለቀን ያ እርግማን ደርሶበት ይሆን? ጀግኖችን ከማክበሬ የተነሳ ደጃች በላይ ዘለቀን በተለይ በይፋ በጣም ስለማደንቅ፣ ባለቤቴ የፖለቲካ ሰለባ ይሆናል እያለች ትጨነቅ ነበር። ግርማ ዘለቀ ሲሞት እጅግ በጣም አዘንኩ።
ወያኔን በለስ ቀንቶት፣ በአሜሪካ ሁለንታዊ አጋዥነት፣ በጋዳፊ የጦር መሣሪያዎችን በገፍ አስታጣቂነት፣ በዓረብ ሀገሮች አመርቂ ገንዘብ ለጋሽነት፣ በመንግሥቱ ኃይለማርያም ኮብላይነት ታግዞ እናት ኢትዮጵያን ላለፉት 23 ዓመታት ለመቆጣጠርና በታሪኳ ተመጣጣኝ የማይገኝላቸው ዘግናኝ ሰቆቃዎችን በሕዝቦቿ ላይ በጭካኔ ሊፈፅም ቻለ። ይህን በተመለከተ፣ ሰኔ አንድ ቀን 2006 ዓ.ም ደብረ ማርቆስ ከተማ የተደረገው ጀግንነትና ፖለቲካዊ ብስለትን የተላበሰ አፍቃሬ-ለውጥ ደማቅ ሰልፍ፣ ለጎጃም ሕዝብ ያለኝን አክብሮት አሻቅቦታል። ጀግናው ግርማ ዘለቀና፣ በወያኔ ፓርላማ በተቃዋሚነት ተሰይሞ ለኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ሲሟገት የነበረው አርበኛው ታላቅ ወንደሙ አድማሴ ዘለቀ (እስር ቤት ተዋወቅነናል)፣ ሁለቱም ካሉበት ሆነው ደማቁን ሰልፈ ሲመለከቱ ከፍተኛ ኩራት እንደሚሰማቸው አይጠረጠርም
ማጠቃለያ
የወያኔ መከላከያና የፀጥታ ሠራዊት፣ የማስተር ቴክኒሽያን ግርማ ዘለቀን ምሳሌ ተከትሎ፣ በሙስና የተጨማለቁትንና በቁልፍ የአዛዥነት ቦታ ላይ የተመደቡትን የአንድ አናሳ ብሄረሰብ ከበርቴ ጄኔራሎችንና ኮሎኔሎችን በቁጥጥሩ ስር በማዋል፣ ወገናዊነቱን ግፍ ለደረሰበት የኢትዮጵያ ሕዝብ በማሳየት፣ ታሪክ የመሥራት እድል ሳያመልጠው በፍጥነት ቆራጥ እርምጃ መውሰድ የሚያስመሰግነው ይሆናል።
የክቡር አክሊሉ ኃብተወልድን ምሳሌ በመከተል፣ ክርስቲያኑ የኢሀዴግ ጠቅላይ ሚ/ር፣ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ በሕዝባዊ አመፅ የሚጥለቀለቁበትን አይቀሬውን ቀን በማሳብ፣ ሕይዎት ሳይጠፋ፣ ደም ሳይፈስ፣ እና ንብረት ሳይባክን ከተቃዋሚዎች ጋር ቢደራደሩ፣ የፖለቲካና የህሊና እስረኞችን አለምንም ቅድመ ሁኔታ ቢፈቱና የፖለቲካውን ምህዳር ቢያሰፉ፣ ከአስከፊ ውርደት ይድናሉ። ኢትዮጵያ ሀገራችንን ግን መለኮታዊ ጥበቃ ከውድቀት ያድናታል።
ወያኔ ላለፉት 23 ዓመታት ሲግተን የነበረው የግፍ ጽዋ፣ በቆራጡ አርበኛ በአንዳረጋቸው ፅጌ ታፍኖ መታሰር ሞልቶ መፍሰስ ጀምሯልና የኢትዮጵያ ሕዝብ ከእንግዲህ ትግዕግሥቱ ተሟጦ አልቋል።ሳይዘገይ መታረም ምርጫው የእሀዴግ ብቻ ነው!!!
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
rababya@gmail.com

“በኢትዮጵያዊነት ማንም ከኦሮሞዎች አይበልጥም፤ ኦርጅናል ኢትዮጵያውያን ነን” – አቶ ቡልቻ ደመቅሳ

July27/2014
አቶ ቡልቻ ደመቅሳ ለረጂም ዓመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ተሳትፏቸው ይታወቃሉ፤ በተለይም የኦሮሞን ህዝብ መብት እናስከብራለን ብለው የፖለቲካ ፓርቲ መስርተው ከታገሉት ሰዎች መካከል ከፊተኞቹ አንዱ ናቸው፡፡ አቶ ቡልቻ አሁን ስላሉበት የፖለቲካ ተሳትፏቸውና ስለተለያዩ አንኳር ሀገራዊ ጉዳዮች ከጋዜጠኛ በላይ ማናዬ ጋር ቆይታ አድርገዋል፤ እንዲህ ይቀርባል፡-
Ato Bulcha
ነገረ ኢትዮጵያ፡- አቶ ቡልቻ በተለያዩ መድረኮች ላይ በፖለቲካ ተሳትፎዎ ነው የሚታወቁት፤ ነገር ግን አሁን ላይ ከፓርቲ ፖለቲካ ተሳትፎ የራቁ ይመስለኛል፡፡ በዚህ ወቅት ስላልዎት የፖለቲካ ተሳትፎዎ በአጭሩ ቢነግሩኝ?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ ከመድረክ የገባሁት የኦፌኮ መሪ ሆኜ ነው፡፡ አሁን የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረንስ (ኦፌኮ) እስኪ ወጣቶቹ ይስሩ፣ እነሱ ሲሰሩ የሚቻለኝን እርዳታ አደርጋለሁ ብዬ በራሴ ፈቃድ ከፓርቲ ፖለቲካ ወጥቻለሁ፡፡ ‹‹Retire››  አድርጌያለሁ፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን ጤናማ ነኝ፡፡ በእድሜየ በኩል 83 አመቴ ነው፡፡ በትምህርትም ሆነ በተፈጥሮ ስጦታ ትልቅ አቅም ያላቸው ልጆች ስላሉ እኔ በዚህ እድሜዬ መድከም የለብኝም ብዬ ነው የለቀቅኩት፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ስለዚህ አሁን የቱንም የፖለቲካ ድርጅት አይወክሉም ማለት ነው?
አቶ ቡልቻ፡- ልክ ነው! በግሌ ነው የምንቀሳቀሰው፡፡ አሁን ምንም አልወክልም፡፡ አስተያየትም የምሰጠው፣ ንግግርም የማደርገው በግሌ ነው፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- መድረክ በቅርቡ አዲስ አበባ ውስጥ ሰላማዊ ሰልፍ ባደረገበት ወቅት ንግግር ሲያደርጉ በቦታው ነበርኩ፡፡ ‹‹በጋራ መምጣት ከፈለግን አንድ መሆን አለብን›› የሚል ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ምን ለማለት ፈልገው እንደሆነ ሊያብራሩልኝ ይችላሉ?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ ማለት የፈለኩት፤ የኢትዮጵያ ብሄሮች (ብሄሮች አሉ፡፡ የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ብሄሮች እንደለሉ መናገር ችግር የለውም የሚሉ ቢኖሩም ተሳስተዋል፡፡ እኛ አይደለም የምንፈጥራቸው፡፡ እነሱ አሉ፡፡) መኖራቸውን አውቆ ከእነሱ ወኪሎች ጋር መነጋገር ነው፡፡ ኢትዮጵያ መነጋገሯ
አይደለም፡፡ የብሄሮች ወኪሎች ተነጋገሩ ማለት ኢትዮጵያ ተነጋገረች ማለት ነው በውስጧ፡፡ የተለያዩ የፖለቲካ መስመር የሚከተሉ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ማለት የአንድ ማህበረሰብ ሰዎች አንድ አይነት ፖለቲካ ይከተሉ ማለት አይደለም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በጎሳ ወይም በብሄር የተደራጁት አካላት ትክክል አይደሉም የሚሉ ሰዎች አሉ፤ ብሄር ማለት ሀገር ማለት ነውና ከቃሉ ጀምሮ ትክክል አይደለም ይላሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ…ለእርስዎ ብሄር ማን ነው? ብሄረሰብስ የትኞቹ ናቸው?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ ‹‹ብሄር›› የሚባለውን ቃል የሰማሁት የ19ና 20 አመት ሆኜ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት፡፡ አንድ አራት ኪሎ ይገኝ የነበር ተስፋ ገብረስላሴ የተባለ ሰው ማተሚያ ቤት ነበር፡፡ ያ ማተሚያ ቤት ‹‹ተስፋ ገብረስላሴ ዘ ብሄረ ቡልጋ›› ይል ነበር፡፡ ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጠይቄ አሁን የምረዳውን ተረዳሁ፡፡ ብሄር ማለት አሁንም እንደምንሰማው የአንድ ብዙ ወይንም አነስ ያለ ህዝብ አንድነት፣ ወይንም ማንነት ማለት ነው፡፡ ምንም አያስቸግረኝም፣ አስቸግሮኝ አያውቅም፡፡ ብሄር ማለት የህዝብ መገለጫ ማለት ነው፡፡
bulcha_demeksa
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ህዝብ የተለያየና አንጻራዊ መገለጫዎች ይኖሩታል፡፡ በዚህ መሰረት እንደ ኢትዮጵያ የጋራ መገለጫ አይኖረንም? ‹ብሄር› የሚባሉት ቡድኖች መገለጫቸው ድንበር ሲያጣ ይታያል፡፡ ስለዚህ በጋራ የምንጋራቸውን ማንነቶችስ ምን ልንላቸው ነው?
አቶ ቡልቻ፡- ኢትዮጵያ ብቻ አይደለችም በዓለም ላይ ብዙ ሀገራት አሉ፡፡ በተባበሩት መንግስታት ላይ ያየኸው እንደሆነ 198 ነው ሀገራት አሉ፡፡ ኢትዮጵያ ከእነዚህ ሀገራት አንዷ ናት፡፡ እኔ ከእነዚያ መካከል አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ ዜጋ ነኝ፡፡ ልክ አንድ ቤተሰብ ብዙ ሰው እንደሚኖረው እኛም ሀገራችን ውስጥ ስንገባ ብዙ አይነት ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እገሌ ብሄር፣ እገሌ ደግሞ ብሄረሰብ ነው ብለው በምሳሌ ሊያስረዱኝ ይችላሉ?
አቶ ቡልቻ፡- እኔ እንደሚገባኝ ነው የምሰጥህ፡፡ ኦሮሞ ማለት ኦሮምኛ የሚናገር፣ በምስራቅ፣ መካከለኛውና ምዕራብ ኢትዮጵያ የሚኖር፣ አብዛኛውን ጊዜ ግብርና መኖሪያቸው የሆነ መልካቸው (ከሌላው ኢትዮጵያውያን ይለያል አልልም) ጥቁርም አይደሉም፣ ቀይም አይደሉም፡፡ ብዙው የኢትዮጵያ ህዝብ እንደዚህ ነው፡፡ ኦሮሞ እንዲህ አይነት ህዝብ ነው፡፡ ውስጥ የገባህ እንደሆነ ስነ ልቦና፣ የጋራ አመለካከት የመሳሰሉ የእያንዳንዱ ሰው ፍርድ አለ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- አንዳንድ ፖለቲከኞች ‹‹ብሄር›› የሚባሉትን ጎሳ፣ እንዲሁም ድርጅቶችን ‹‹የጎሳ ድርጅት›› ይሏቸዋል፡፡ እርስዎ ይስማማሉ?
አቶ ቡልቻ፡- አልስማማም! ጎሳ ሌላ ነው፡፡ እኔ የአማርኛ ሊቅ ባልሆንም መናገር እችላለሁ፡፡ ጎሳ የሚባል ቃል፤ እኔ እንጃ?! ኦሮሞ ጎሳ ነው እንዴ? ኦሮሞ ጎሳ አይደለም! አንድ ህዝብ ነው፣ ጎሳ አይደለም፡፡ ምን አልባት የሚዛመዱትን ከሆነ ኦሮሞ ውስጥ ብዙ እርስ በእርሳቸው የሚዛመዱ አሉ፡፡ እኔ በተወለድኩበት ወለጋ ውስጥ በራሱ ብዙ ብዙ ጎሳዎች አሉ፡፡ ጎሳ እንኳ ብዙም ትርጉም የለውም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እንደ ሩዋንዳ ያሉ ሀገራት አንድን ህዝብ ቋንቋን ወይም ጎሳን መሰረት አድርጎ በፖለቲካ ማደራጀት በህግ ከልክለዋል፡፡ በጎሳ መደራጀት በተለይ በፖለቲካ ፓርቲ ደረጃ ምን ያህል ያስኬዳል? ለሀገር አንድነትስ ተጽዕኖ አይኖረውም?
bulcha_demeksaአቶ ቡልቻ፡- እኔ እንደሚመስለኝ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ዘጠና ሚሊዮን ህዝብ ነው የሚኖረው፡፡ እግዚአብሄር ይመስገን መታወቂያ ስለሰጠን እንጂ ካለዚያማ ማን ምን እንደሆነም አይታወቅም፡፡ አሁን ግን አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግሬ.. በጣም ደስ የሚል መግለጫ፡፡ እሱማ ባይኖር ማን ነበር የምንባለው? የትግሬ ህዝብ በራሱ መሪዎቹን መርጦ ወደ ዋናው ከተማ ይመጣል፡፡ ኦሮሞ በራሱ ክልል የራሱን መሪዎች መርጦ ወደ አዲስ አበባ ይመጣል፡፡ እነዚህ መሪዎች ኢትዮጵያን እንዴት እንምራት ብለው ሊስማሙ ይችላሉ፡፡ ሊነጋገሩ ይችላሉ፡፡ አንድ ህዝብ በስሙ መጠራቱ ምን ከፋ? ችግሩ እኛ ኢትዮጵያውያን አይደለንም ሲባል ነው፡፡ ህወሓት፣ ኦነግና አሁን ኢህአዴግ ውስጥ ያለው የአማራ ድርጅት ኢትዮጵያዊ አይደለንም ይሉ ነበር፡፡ ችግሩ የሚመጣው እንዲህ ሲሆን ነው፡፡ ይህ ሳይሆን በስሙ ተጠርቶ፣ ከሌሎች የኢትዮጵያ ዜጎች ጋር ተዋዶና ተፋቅሮ፣ እየተረዳዳ፣ እየሰራ ቢኖር ምን
ችግር አለው?
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እርስዎ በፓርቲ ደረጃና በግል እንደሚታገሉለት የሚናገሩለት የኦሮሞ ህዝብ ሰፊ መሰረት ያለው መሆኑ ይታወቃል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ሰፊ መሰረት ያለው ሆኖ እያለ በቋንቋ በመደራጀት መብቱን አስከብራለሁ ማለት ለክብሩ የሚመጥን አይደለም የሚሉ አካላት አሉ፡፡ የኦሮሞ ህዝብ በቋንቋ ከመደራጀት ይልቅ በህብረ ብሄራዊነት ተደራጅቶ በኢትዮጵያ የተሻለ ለውጥ ማምጣት አይችልም? በአንድ ክልል፣ በአንድ ማዕቀፍ ብቻ ተወስኖ መደራጀት ለክብሩ የሚመጥን ነው ብለው ያስባሉ?
አቶ ቡልቻ፡- የኦሮሞ ህዝብ ከ37 እስከ 40 ሚሊዮን የሚሆን ህዝብ ነው፡፡ ግን አዋቂዎችና የተማሩት የሚሉትን ልንገርህ፡፡ እኛ የኢትዮጵያ አካል ነን፡፡ የትም መሄድ አንፈልግም፡፡ ኦሮምኛ እንናገራለን፡፡ ግን ኢትዮጵያውያኖች ነን፡፡ በኢትዮጵያዊነት ማንም ከእኛ አይበልጥም፡፡ እኩል ነን፡፡ እገዛችኋለሁ፣ እበልጣችኋለሁ፣ ቋንቋችሁን አፍናለሁ፣ የሚሉ ካሉ እንታገላቸዋለን፡፡ እንጂ የትም አንሄድም፡፡ አገራችንን ትተን የት እንሄዳለን? ዛፍ እንኳ ስታየው ቅርንጫፉ ነው የሚወድቀው፡፡ ዋናው ግንድ ይቆማል፡፡ ኦሮሞ ግንድ ነው፡፡ ማንም ሰው ለኦሮሞ አንተ እንዲህ ነህ፣ አንተ እንዲህ ነህ ብሎ ሊነግረው አይችልም፡፡ ኦሮሞ ምን እንደሆነ ራሱን ያውቃል፡፡ እንዲያውም ኦሮሞ ይህ ሀገር የእኔ ነው፣ ከሌሎች ጋር ተጋርቼ እኖራለሁ ብሎ ነው የሚያምነው፡፡ ስለዚህ ነው እንገነጠላለን የሚሉ ሰዎች ያልተሳካላቸው፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ታዲያ ኦሮሞ ግንድ ሆኖ እያለ እንደ ቅርንጫፍ ነጥሎና ጠበብ አድርጎ መደራጀት ለምን አስፈለገ?
አቶ ቡልቻ፡- ኦሮሞዎች፣ እኛ ኦርጅናል ኢትዮጵያውያን ነን፡፡ ኢትዮጵያውያን ሆነን ግን ለፖለቲካና ማህበራዊ ህይወት እንደራጃለን፡፡ ቋንቋችን ስንናገር ነው የምንግባባው፡፡ አማርኛም እንናገራለን፣ ነገር ግን አማርኛም የማያውቅ አለ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ለምን ኦሮሞ፣ ትግሬ፣ አማራ፣ ጉራጌ ተብሎ ይጠራል
ብለው የሚከራከሩት አብዛኛውን ጊዜ የቀድሞ የሹማምንት ልጆች ናቸው፡፡ የግራአዝማቹ፣ የቀኝአዝማቹ፣ የራሱ የቀኝአዝማቹ ዝምድና ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነሱ የሚመኙት ወደ ድሮው፣ ወደመሪነት፣ ወደማዘዝ ቦታ ነው የሚመኙት፡፡ የፌደራል ጉዳይ ደግሞ ይነሳል፡፡ ለምንድን ነው ሁላችንም አንድ አዳራሽ ውስጥ የማንኖረው? ለምንድን ነው እያንዳንዱ ሰው ከሌላው ተወዳድሮ ቆንጆ ቤት ሰርቶ ለብቻው የሚኖረው? ፌደሬሽን የሚጠሉ ሰዎች ምንድን ነው የሚፈልጉት? በ1983 ዓ.ም ፌደራሊዝም ከመገንጠል ይሻላል ተብሎ እኮ ነው የመረጥነው፡፡ ያኔ ሁሉም፤ ኦነግም፣ ህወሓትም፣ አማራም፣ ሲዳማም… ሁሉም ብሄር ፌደራሊዝምን የመረጥነው እንገነጠላለን የሚሉትን ሰዎች ለማሸነፍ ነው፡፡ እኔ ኢትዮጵያ ከፌደራሊዝም ውጭ ተስፋ አላት ብዬ አላምንም፡፡
bulcha
ነገረ ኢትዮጵያ፡- አሁንም ቢሆን ከፌደራሊዝም ውጭ አማራጭ ይዞ የመጣ የፖለቲካ ፓርቲ ያለ አይመስለኝም፡፡ ልዩነቱ በቋንቋ/ጎሳ/ብሄር ከሚሆን ይልቅ አስተዳደራዊ አመችነትና ሌሎች መስፈርቶች መታየት አለባቸው የሚል ነው፡፡ እርስዎ አሁን እንደሚናገሩት ግን ኢህአዴግ የሚጠቀምበት ቋንቋን መሰረት ያደረገ አወቃቀር እንዲቀጥል የፈለጉ ይመስለኛል?
አቶ ቡልቻ፡- አዎ! አማራጭም የለውም፡፡ ታዲያ በምን የተመሰረተ ድርጅት ሊሆን ነው? በቋንቋው፣ በባህሉ፣ በሚኖርበት አካባቢ የፖለቲካ ድርጅት ቢያቋቁም ምን ይጎዳል? ለምንድን ነው የሚጠላው? አሁን እነሱ የሚሉት በዘር ሳይሆን በወንዝ፣ በተራራ፣ አንዳንድ ዳርቻዎችን በመጥቀስ ነው፡፡ ለምሳሌ በአጼ ኃይለስላሴ ጊዜ ሸዋ አማራም፣ ኦሮሞም ነበረበት፡፡ በዛን ጊዜ ሀገረ ገዥው ራስ መስፍን ነበሩ፡፡ እኔ አውቃቸዋለሁ፡፡ በጣም ጥሩ ሰው ነበሩ፡፡ በጣም ትሁት፣ ሩህሩህና ፍትህ የሚያውቁ ሰው ነበሩ፡፡ እሳቸው አማራ ነበሩ፡፡ ኦሮሞዎቹ እንደልባቸው ራስ መስፍን ጋር አይመሩም፣ ራስ መስፍንን አያማክሩም፡፡ አማራ የሆኑት የሸዋ ሰዎች ግን ራስ መስፍንን እንደራሳቸው መሪ፣ እንደራሳቸው ሀገረ ገዥ፣ እንደራሳቸው እንደራሴ አድርገው ነበር የሚያዩት፡፡ ይህ ራሴ በህይወቴ ያየሁት ገጠመኝ ነው፡፡ ህዝብ የሚፈልገውን ያውቃል፡፡ ከፌደራሊዝም ውጭ አማራጭ የለንም፡፡ ፌደራሊዝምን በደንብ መምራት የመንግስት ፋንታ ነው፡፡ ፌደራሊዝም በሚመራበት ወቅት የኦሮሞ ህዝብ ‹ራስ መስፍን የእኛ አይደሉም› እንዳሉት እንዳይሆን መደረግ አለበት፡፡ የአዲስ አበባ መንግስት ሁሉንም ሰው በእኩልነትና በፍርድ የያዘ እንደሆነ ፌደራሊዝም ጥሩ አማራጭ ይሆናል፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ፌደራሊዝሙ በቋንቋ መዋቀሩ እንደ ችግር ተብሎ የሚነሳው ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ‹‹ሀገራችሁ አይደለም ውጡ›› እንደሚባሉ በመጥቀስ ነው፡፡ በደቡብና ቤንሻንጉል እየታየ ያለውንም እንደማሳያ ይጠቅሳሉ፤ እና…
አቶ ቡልቻ፡- እሱን በጭራሽ አልደግፍም፡፡ እሱን በመመካከር፣ በአስተዳደር፣ በፖለቲካ፣ አንድም ነገር ሳይደበቅ መነጋገርና መወያየት ያስፈልጋል፡፡ ግልጹን ማውጣት ነው የሚጠቅመው፡፡ ለምሳሌ ከወለጋ አማራዎችን አንስተዋቸዋል ይባላል፡፡ ውሸት መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ግድ የለም አስነሷቸው እንበል፡፡ ታዲያ ለምንድን ነው የምታስነሷቸው ብሎ መጠየቅ ነው? ኢትዮጵያውያን የትም ሄደው መስራትና መኖር አለባቸው፡፡ በመሆኑም ማፈናቀል ካለ ለወደፊት ወንጀል ተደርጎ መወሰድ አለበት፡፡ አንድ ብሄር ሌላኛውን ይህ ያንተ አይደለም፤ ከሌላ ነው የመጣኸው ብሎ ሲያፈናቅል የሚቀጣበትን አግባብ መፈለግ ነው ያለብን፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በአንቦና በሌሎች አካባቢዎች ግጭት ለመነሳቱ ቀዳሚው ምክንያት የኦሮሚያ መሬት ሊወስድ ነው፣ አርሶ አደሮች ሊፈናቀሉ ነው በሚል ነበር ይታወል፡፡ በአንድ በኩል አዲስ አበባ የኦሮሞ ነች እየተባለ በሌላ መልኩ ደግሞ የኦሮምያ መሬት ለአዲስ አበባ ሊሰጥ ነው ማለት እርስ በእርሱ አይጋጭም?
አቶ ቡልቻ፡- እንደ እኔ ይህንን ጣጣ ያመጡት በፌደራል መንግስቱ ውስጥ የሚሰሩ አንዳንድ ባለስልጣናት ናቸው፡፡ እርግጥ ነው ኦሮሞ መሬቱ በአዲስ አበባ እንዲወሰድ አይፈለግም፡፡ ምክንያቱም የጋራ ጥቅም ነው፡፡ አሜሪካም ውስጥ እንዲህ አይነት ጭቅጭቅ አለ፡፡ ትልልቅ የመንግስት ስራዎች ሲሰሩ አንዱ ስቴት ይመረጣል፡፡ ለመንግስት ስራ የተመረጠው ስቴት የስራ አጥነትና ሌሎች ችግሮች እንደሚፈጠሩ በመግለጽ ይከራከራሉ፡፡ ታዲያ ምን አለ የኦሮሞ ወጣቶች እኛ ሳንጠየቅ ይህን ያህል መሬት ለምን ይወሰድብናል? ቢሉ ምን ችግር አለው፡፡ አሜሪካ ዋና ከተማው ዋሽንግተን ዲሲ ነው፡፡ ዋሽንግተን የቨርጂኒያና የሜሪላንድን መሬት ዝም ብሎ ይከልላል? የማይታሰብና የማይደረግ ነገር ነው፡፡ ለማንም ሳይናገሩ ልዩ ዞኖችን እንደወሰዱት አይደለም፡፡ ይህ እኮ ሰውን መናቅ ነው፡፡ ከህዝቡ ጋር ተማክረዋል? መንግስት የህዝብ ወኪል ከሆነ ህዝብን መናቅ አይችልም፡፡ በሰለጠነ መንገድ ቢደረግ ኖሮ ማን ይቃወም ነበር?
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በቅርቡ ‹‹ሰማያዊ ፓርቲ አይገባኝም!›› ማለትዎትን አንብቤያለሁ፡፡ ሰማያዊ አይገባኝም ሲሉ ምን ማለትዎት ነው?
አቶ ቡልቻ፡- አንድነትን አውቀዋለሁ፡፡ መኢአድን አውቀዋለሁ፡፡ ሰማያዊን ግን አላውቀው ማለቴ ነው፡፡ ይህ ግልጽ ነው አላውቃቸውም ማለት ነው፡፡ እነሱም አላማቸውን ለማሳወቅ ፓምፕሌት አይበትኑም፡፡ እኔ ለምሳሌ ኦፌኮ በነበርኩበት ጊዜ ስለ አላማችን በርካታ ፓምፕሌቶችን እያሳተምኩ እበትን ነበር፡፡ ህዝብ አላማችን እንዲያውቅ እናደርግ ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ይህንን ሲያደርግ አላየሁም፡፡ እና ሰማያዊ ከአንድነት ምን ያህል ልዩነት ኖሮት ነው ሰላማዊ ሰልፍ የተፈቀደለትና አንድነት ሰላማዊ ሰልፍ የተከለከለው? አይገባንም፡፡ እውነቴን ነው ፖለቲካም እውነት ሊሆን ይችላል አንዳንዴ፡፡ ይህን አላውቅም የምለው ከልቤ ነው፡፡ አንድነት ከኦሮሞ የሚለይበትን አንዳንድ ምክንያቶች አውቃለሁ፡፡ ይህ ከቅን ልቦና የማደርገው ንግግር ነው፡፡ ቢፈልጉ ፓምፕሌት ይላኩልኝ አንብቤ እረዳዋለሁ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እርስዎስ በግልዎ ለማወቅ ጥረዋል?
አቶ ቡልቻ፡- አዎ! ጠየኩ! ቢሮ ውስጥ እባካችሁ የሰማያዊ ፓርቲ ፓምፕሌት፣ መግለጫ ካላችሁ ብዬ ጠይቄያለሁ፡፡ አሁንም እጠይቃለሁ፡፡ ለምሳሌ ከአንድነት ልዩነታቸው ምንድን ነው? አንድነት አማራ፣ ኦሮሞ፣ ትግራይ ሳይሆን ኢትዮጵያ መባል እንዳለበት እንደሚፈልጉ አውቃለሁ፡፡ የሰማያዊ ምን እንደሆነ አላውቅም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ሰማያዊ አቋሞቹን፣ መግለጫዎቹንና ሌሎቹንም በዚህ ጋዜጣ ያሳውቃል፡፡ ለምሳሌ ነገረ ኢትዮጵያን አንብበው ያውቃሉ?
አቶ ቡልቻ፡- እስካሁን አላየሁም፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- ለ2007 ሀገራዊ ምርጫ እየተቃረብን ነውና ከምርጫው ምን ይጠብቃሉ?
አቶ ቡልቻ፡- በአሁኑ ጊዜ የህዝቡን የኢኮኖሚ ችግር፣ የኑሮ ውድነት፣ የስራ አጥነት፣ በተለይም የምግብ ዋጋ መናር አለ፡፡ ይህን ሁሉ ህዝቡ ያውቃል፡፡ ታዲያ ህዝቡ ይህን እያወቀ ኢህአዴግን እንመርጣለን ይላል? እንግዲህ እያንዳንዱ ሰው መፍረድ አለበት፡፡ ይህ ሁሉ ችግር እያለ በማን አገር ነው አንድ ፓርቲ 20ና 30 አመት ስልጣን ላይ የሚቆየው? ቻይና ብቻ ነው አይደለም?! እንደ ቻይና ኮሚኒስት እንሁን ብሎ የኢትዮጵያ ፓርላማ ፈቅዷል? ያለ ፓርላማ ፈቃድ የኢትዮጵያ መንግስት እንደፈለገ የሚንቀሳቀስ፣ የፈለገውን ገንዘብ የሚያወጣ፣ የፈለገውን የሚገዛ፣ የፈለገውን የሚሸጥ፣ ዴሞክራሲ እንደሌለ አድረጎ ነው የሚያስተዳድረው፡፡ እንደ ፖለቲከኛ ሳይሆን እንደ ዜጋ ሳየው ተቃዋሚዎች በሚቀጥለው ምርጫ ትልቅ እድል አላቸው፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- እርስዎ የሚገልጹት ብሶት መኖሩን ነው፡፡ ግን ተቃዋሚዎች የሚሉትን እድል ለመጠቀም የቤት ስራቸውን እየሰሩ ነው ብለው ያምናሉ?
አቶ ቡልቻ፡- ተቃዋሚዎች የማይፈታ ችግር አለባቸው፡፡ አሁን በቀደም በጋዜጣ ላይ ሳነብ ኢህአዴግ በደግነቱ ለተቃዋሚዎች ገንዘብ ሰጠ የሚል አይቼ በጣም ተደነኩ፡፡ ጋዜጣው ላይ ቃል በቃል ‹‹ለግሷል!›› ይላል፡፡ ይህ እኮ ድንቁርና ወይንም ክፋት ነው፡፡ በየትኛውም ሀገር ምርጫ ሲደርስ መንግስት ለተቃዋሚዎች ገንዘብ መስጠት ግዴታው ነው፡፡ ዋናው የመንግስት ስራ እኮ ነው፡፡ በጀት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ካለ በጀት ምንም ነገር አይሰሩም፡፡ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች አንድ ቦታ ላይ ለመድረስ የኢትዮጵያ በጀት እንዲደርሳቸው ያስፈልጋል፡፡ ይህ ደግነት አይደለም፡፡ የማንም ሀገር ተቃዋሚ በመንግስት በጀት ይንቀሳቀሳል፡፡ ተቃዋሚ አስተያየቱን በግልጽ በጋዜጣ፣ በቴሊቪዥንና በመሳሰሉት ካልገለጸ ማን ይመርጠዋል? እሱ እኮ ነው ኢትዮጵያ ውስጥ የተዘጋው በር፡፡ በሩ ከተዘጋ ተቃዋሚዎች እንዴት ይንቀሳቀሳሉ? በሬድዮና ቴሌቪዥን አትናገሩ ከተባለ፣ ሰላማዊ ሰልፍን ለህዝብ በቴሌቪዥን እንዳይታይ ከተደረገ ተቃዋሚዎች እንዴት ይንቀሳቀሳሉ? እንደዛም ሆኖ ግን ተቃዋሚዎች አሁንም ትልቅ እድል አላቸው ባይ ነኝ፡፡
ነገረ ኢትዮጵያ፡- በመጨረሻ መናገር እፈልጋለሁ የሚሉት መልዕክት ካለ?
አቶ ቡልቻ፡- እንዴት የኢትዮጵያ ህዝብ ዝም ብሎ አንድ ጥያቄ ሳይጠይቅ ይኖራል? ተቃዋሚዎችን በራዲዮና በቴሌቪዥን ያሰሙን ብሎ በሰልፍ አይጠይቅም? እንደዚሁም ደግሞ መንግስት መረጃ አልሰጥም እያለ ሲያስቸግር ህዝቡ አይጠይቅም? የመንግስትን ንብረት አጠቃለሁ፣ የሚገዙበት፣ የሚዙት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ብቻ ናቸው፡፡ የመንግስት ኩባንያዎች ሁሉ በኢህአዴግ ስር ነው የሚተዳደሩት፡፡ ድሮ በአጼ ኃይለስላሴ ጊዜ እንደዚህ ነበር፡፡ ነገር ግን በእርሳቸው ጊዜ እንደዛ የሆነው የግል ባለሀብት ስለጠፋ ነው፡፡ ዛሬ የግል ባለሀብት እንደ ልብ ነው፡፡ ለምንድን ነው የኢትዮጵያ መንግስት ይህን ሁሉ ንብረት የሚቆጣጠረው? የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ቴሌ፣ አየር መንገድን ሁሉ ለምንድን ነው በስሩ ያደረገው? እኛ ኮሚኒስት ነን እንዴ? ፓርላማ ኢትዮጵያ ኮሚኒስት ነች ብሏል፡፡ ይህ የኢህአዴግ የራሱና የውስጥ አሰራር ነው፡፡ ይህን ለህዝብ መናገር እፈልጋለሁ፡፡
ምንጭ፡ ነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ከአዲስ አበባ

ሰማያዊ ፓርቲ ምሁራን ተሳትፈውበታል ያለውን የቃል ኪዳን ሰነድ ይፋ አደረገ

July26/2014
ሰማያዊ ፓርቲ ምሁራን ተሳትፈውበታል ያለውን የቃል ኪዳን ሰነድ ይፋ አደረገ
-ፓርቲዎች በድርጅታዊ ፕሮግራሞቻቸው ውስጥ እንዲያካትቱት ጠይቋል

ሰማያዊ ፓርቲ በአገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ በርካታ ምሁራን ተወያይተውበት ብዙ ጥናትና ምርምር አድርገውበታል ያለውንና ‹‹የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ ለዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ›› በሚል መጠሪያ ያዘጋጀውን ሐምሌ 18 ቀን 2006 ዓ.ም. ይፋ አደረገ፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ይፋ ያደረገው የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ ዜጎች በጋራ አንድ ሆነው ሊስማሙባቸው የሚችሉ፣ አጠቃላይ በአገራቸው ሁኔታ ላይ የሚግባቡባቸው ጉዳዮችን የያዘ የጋራ ሰነድ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ከፕሮግራም፣ ከፖለቲካ ሐሳብ፣ ከአስተሳሰብና ለወቅታዊ ችግሮች መፍትሔ ከመስጠት ልዩነት ባሻገር፣ ኢትዮጵያዊያን እንደ አገር የሚግባቡበት አንድ የጋራ ሰነድ አስፈላጊ መሆኑን ፓርቲው ገልጿል፡፡ ይህም ሰነድ ፓርቲው ብቃት ባላቸው ምሁራን ተጠንቶና ውይይት ተደርጎበት፣ ሕዝብ ውይይት አድርጎበት አንድ የሚሆንበትና ‹ሕገ መሠረት› (የሕገ መንግሥት ማርቀቂያ መነሻ መሠረት) ሲል የጠራው ሰነድ መሆኑን የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር) ገልጸዋል፡፡

እንደ አቶ ይልቃል ገለጻ፣ ሰነዱ ውይይት ተደርጎበትና የኅብረተሰቡን ይሁንታ ካገኘ፣ ወደፊት ለሚረቀቀው ሕገ መንግሥት ወይም በሰማያዊ ፓርቲ አጠራር ‹ርዕሰ ሕግ›፣ በሰነዱ የቀረቡት ምሰሶ (ፒላር) የሆኑ ነገሮች ሆነው እንዲካተቱ ይደረጋል፡፡

የዜጎች ቃል ኪዳን ሰነድ (ሕገ መሠረት) በሚል ፓርቲው ይፋ ያደረገው ሰነድ አዘጋጅ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ እምልአሉ አሰፋ እንደገለጹት፣ ሕገ መንግሥት የሚለውን ‹‹ርዕሰ ሕግ›› ቢባል የተሻለ ትርጓሜ ሊኖረው ይገባል የሚል እምነት ፓርቲው ስላለው ርዕሰ ሕግ ብሎታል፡፡ ርዕሰ ሕጉን የሚያቋቁሙበት መሠረታዊ ምሰሶዎች (ፒላርስ) ደግሞ ሕገ መሠረት መባል እንዳለባቸው የሰማያዊ ፓርቲ እምነት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ ርዕሰ መንግሥትን (ሕገ መንግሥትን) በባለቤትነት የሚያቅፈው ዘላቂ ሰላምን፣ የሕግ የበላይነትንና ፍትሕን አራማጅ ሆኖ ሲያገኘው መሆኑን የገለጹት ምክትል ሰብሳቢው፣ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ አዲሱ ርዕሰ ሕግ የሚረቀቅ ከሆነ ካለፉት ዘመናት ከተደረጉት ጥረቶችና ልምዶች የተገኙ ትምህርቶችን ያካተተና በሕገ መሠረቶች ላይ የተመሠረተ መሆን እንዳለበት፣ የቃል ኪዳን ሰነዱ እምነትም መሆኑን አቶ እምልአሉ ገልጸዋል፡፡

ፓርቲው ይፋ ያደገው የዜጎች ቃል ኪዳን ሰነድ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና ግዛት ማስከበር፣ የግለሰብ መብቶች ቀደምትነት፣ ለህልውና መሠረታዊ ፍላጎቶችን የማግኘት ዋስትና፣ በአገሪቱ ብሔራዊ ቋንቋ(ዎች) እንዲኖሩ ማድረግ፣ የመሬት ባለቤትነት መብትና ዋስትና፣ ያልተማከለ መንግሥታዊ ሥርዓት፣ ሁሉን ወካይ የፍትሕ፣ የወታደርና የሲቪል አገልግሎቶች፣ ነፃና ፍትሐዊ የገበያ ሥርዓት፣ ነፃና ተጠያቂ የሲቪክ ማኅበራትና የፖለቲካ ፓርቲ ተቋማት የሚባሉት መሠረታዊ መመርያዎች ላይ ኅብረተሰቡ እንደሚወያይባቸው አስረድተዋል፡፡

መሠረታዊና ለርዕሰ ሕጉ ምሰሶ (ፒላርስ) ናቸው ባሏቸው ከላይ በተዘረዘሩት ዘጠኝ ነጥቦች ላይ ሕዝቡን በማወያየት አንድ ነጥብ ላይ እንደሚደረስ የሰማያዊ ፓርቲ እምነት መሆኑን የገለጹት አቶ እምልአሉ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብን ያሳተፈና ዘመን ተሻጋሪ ርዕሰ ሕግ ይኖራል የሚል እምነት እንዳላቸው አስረድተዋል፡፡

ርዕሰ መንግሥት ማለትም ሆነ ሕገ መንግሥት የተለያየ ስም ከመስጠት ያለፈ ፋይዳ ስለሌለው ይህንን ማድረጉ ለምን እንዳስፈለገ፣ ብሔርን ማዕከል ያደረገ የፌዴራል ሥርዓት አወቃቀሩ የብሔር ብሔረሰቦችን እኩልነት አረጋግጦ ሳለ፣ ብሔራዊ ቋንቋ እንዲኖረው በማለት ወደ አንድ መጠቅለሉ የዜጎችን መብት ማጣበብ ከመሆኑም በላይ አንዱን የበላይ አንዱን የበታች ማድረግ ስለመሆኑና  የግለሰቦችን መብት አክብሮ የቡድን መብትን መደፍጠጥ በሰነዱ ላይ ስለተገለጸበት ሁኔታ ማብራሪያ እንዲሰጥበት ለአቶ እምልአሉ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል፡፡

አቶ እምልአሉ እንደገለጹት፣ የቃል ኪዳን ሰነዱ ሕገ መንግሥት ማለት አይደለም፡፡ ሕገ መንግሥት ወይም እንደ ሰማያዊ ፓርቲ እምነት ርዕሰ መንግሥት ለማርቀቅ እንደ ምሰሶ ሆነው የሚያገለግሉ ዋና ዋና የሁሉም ኅብረተሰቦች መሠረታዊ መመርያዎችንና የመወያያ ርዕሶችን የያዘ ሰነድ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ስሙን ርዕሰ መንግሥት ማለት የተፈለገው የተሻለ ትርጉም ስለሚሰጥ መሆኑንም አክለዋል፡፡

ቋንቋን በሚመለከት ማብራሪያ የሰጡት የፓርቲው ምክትል ሊቀመንበርና የቃል ኪዳን ሰነዱ አዘጋጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ስለሺ ፈይሳ ሲሆኑ፣ ሰማያዊ ፓርቲ የሁሉንም ብሔረሰቦች ቋንቋ እንደሚያከብር አስረድተው፣ ኢትዮጵያ እንደ አገር ግን አንድ፣ ሁለትና ሦስት ብሔራዊ ቋንቋዎች እንደሚያስፈልጓት ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከሌሎች አገሮች የተለየችና ብቸኛዋ ብሔራዊ ቋንቋ የሌላት አገር በመሆኗ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ እምነት ብሔራዊ ቋንቋ ሊኖራት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ የክልል ወይም የጎሳ ቋንቋ መኖርንም ፓርቲያቸው እንደሚያከብር ገልጸው፣ ሁሉም ሊግባባበት በሚችለው ቋንቋ አይጠቀም የሚል አቋም እንደሌላቸው አስረድተዋል፡፡

የቃል ኪዳን ሰነዱ ሁሉንም የሚያግባባ የጋራ ነጥቦችን የያዘ ሰነድ መሆኑንና ብሔርን መሠረት ያደረገ መሆኑን በማከል፣ ስለብሔር ትርጉም የተናገሩት አቶ እምልአሉ፣ ‹‹ብሔር ማለት ትርጉሙ አገር ወይም ቦታ ማለት ነው፡፡ በ1960ዎቹ የሶሻሊስት ሥርዓት ሲመጣ፣ ስታሊን ‹ኔሽንስ ራይት› ብሎ ስለተነሳ ምሁራን ተሰባስቡና ሲተረጉሙ ብሔር አሉት፡፡ የቡሄ ለት ያበደ ዘላለም ‹ሆ› እንዳለ ይኖራል እንዲሉ እስካሁን ‹ኔሽንስ› የሚለውን ብሔር እያልን እንተረጉማለን፤›› ብለው ትርጉሙ ሌላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ትርጉሙ ሊስተካከል እንደሚገባና አንድነትን የሚያጠናክር፣ የባህል፣ የእምነትና ሌሎች ግንኙነቶችን የሚያጠናክር ነገር መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ የቃል ኪዳን ሰነዱ የያዛቸውን የርዕሰ ሕግ ምሰሶዎች ሕዝቡ ተወያይቶበት ወደ አንድነት መምጣት ሲቻል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

የመሬት ባለቤትነትን በሚመለከት በቃል ኪዳን ሰነዱ ላይ ስለተጠቀሰው ጉዳይ፣ መሬት የሀብት ሁሉ መሠረት ወይም ምንጭ በመሆኑ እንዴት የባለቤትነትና የመብት ዋስትና ሊከበር ይገባል ሊባል እንደቻለ ተጠይቀው፣ የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥትም ‹‹መሬት የሕዝብና የመንግሥት ነው ይላል፤›› ካሉ በኋላ፣ ‹‹መንግሥት መሠረቱ ሕዝብ ነው፡፡ ለምን ሕዝብን አያምንም? የራሱን ነጥሎ በመያዝ የሕዝቡን ለምን ለራሱ ለሕዝቡ አይተውም?›› በማለት ጥያቄ አንስተዋል፡፡ መንግሥት ከራሱ ሕዝብ የበለጠ የውጭ ኢንቨስተሮችን እንደሚያምን የገለጹት አቶ እምልአሉ፣ ኢንቨስተር ግን አምርቶ ዶላሩን ይዞ ሲወጣ እንጂ ሌላ የታየ ነገር እንደሌለ ጠቁመዋል፡፡ የሙስና ዋናው መንገድ መሬት በመንግሥት መያዙ መሆኑንም አክለው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ነዳጅ ቢወጣ መሬት የኢኮኖሚ መሠረት መሆኑ እንደሚያከትምና ጥያቄ መሆኑ እንደሚያበቃ ያልተረዱ፣ ዜጋን የመሬት ባለቤት እንዳይሆን እንዳደረጉት አብራርተዋል፡፡

በሰማያዊ ፓርቲ የተዘጋጀው የዜጎች የቃል ኪዳን ሰነድ የተለፋበትና እነ ዶ/ር ብርሃኑ አበጋዝ፣ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ፣ ፕሮፌሰር አክሎግ ቢራራና ሌሎች ምሁራን የተሳተፉበት መሆኑን የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ይልቃል አስረድተዋል፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችና የሲቪክ ማኅበራት የቃል ኪዳን ሰነዱን አጥንተውና ተወያይተውበት በፕሮግራሞቻቸው ውስጥ እንዲያካትቱት ሰማያዊ ፓርቲ ጥሪ አቅርቧል፡፡ 

Saturday, July 26, 2014

ወያኔን የሚሸነቁጥ ሕዝባዊ አመጽ

July 26, 2014
ዳኛቸው ቢያድግልኝ
Photo: ለ24 ሰዓታት የዱንያ ግንኙነታችንን የማቋረጥና በዱዓ የመጠመድ ጥሪ!!!
#Ethiopia #EthioMuslims #BlackTerror #SwitchOffYourPhone #ምንሊክሳልሳዊ

ሞባይሎቻችንን ከዛሬ ሐሙስ መግሪብ እስከ ጁሙዓ መግሪብ (ለ24 ሰዓታት) እንዝጋ!

እኛ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች አላህን የምንለምንባቸው ብዙ ጉዳዮች አሉን፡፡ ከምንም በላይ እምነታችን ላይ በመንግስት ጥቃት መሰንዘር ከጀመረ አመታት ተቆጠረዋል፡፡ ጀግኖቻችን በእስር ቤት ታጉረዋል፡፡ ተደብድበናል፤ ተዘርፈናል፤ ታስረናል፤ ተሰደናል፤ ተገድለናል፤ ሌላም ሌላም ብዙ በደል ተፈጽሞብናል፡፡ ባለፈው ጁሙዓ መንግስት ሰላማዊ ትግሉን አስቆማለሁ በሚል ቀቢጸ ተስፋ የ‹‹ጥቁር ሽብር›› እርምጃ በሺዎች በሚቆጠሩ ሙስሊሞች ላይ ወስዷል፡፡ የእምነት ቤታችን ተደፍሯል፤ የእምነት አልባሳቶቻችን ተቃጥለዋል፤ አካላችን ተጎድቷል፤ በዚህ ሁሉ በደል መካከል በ27ኛዋ ሌሊት አላህን መማጸን እና ችግራችንን ለእርሱ ማቅረብ መተኪያ የማይገኝለት ታላቅ እድል ነው፡፡

በመሆኑም ይህንን የ27ኛ የረመዳን ሌሊት እና የቀኑን ጾም ታላቅ የዱዓ ጊዜ ለማድረግና አላህን በሙሉ ልባችን ለመለመን ከዱንያ ጋር ሙሉ ለሙሉ የምንቆራረጥበት የ24 ሰዓት ጊዜ ማወጅ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ከዱንያ ሙሉ ለሙሉ የምንቆራረጠው ከነገ ሐሙስ መግሪብ ሰላት ጀምሮ እስከ ጁሙዓ መግሪብ ሰላት ባለው የ27ኛ ረመዳን የሌሊትና የቀን ጊዜ (24 ሰዓታት) ስልካችንን ሙሉ ለሙሉ ስዊች ኦፍ አድርገን በማጥፋት ሲሆን አንገብጋቢ ለሆነ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀርም ስልካችንን በሌሊቱም ሆነ በቀኑ ክፍለ ጊዜ የማንከፍት ይሆናል፡፡ በዚህች የዱንያ ግንኙነታችንን ለመግታት ስልካችንን በምናጠፋባት የ24 ሰዓት ጊዜ አላህ ዱዓችንን እንዲቀበለን እና ያለንበትንም ፈተና እንዲያነሳልን እንመኛለን!
ድምፃችን ይሰማ
“ሰብሰብ ብሎ የጋራ አቋም መያዝና አንድ እርምጃ ወደፊት የመራመድ ምኞት” በሚል ርዕስ ይህንን ጽሁፍ ጀምሬው የዛሬው ዜና ቸር ወሬ ሲያሰማኝ ርዕሱን መቀየር መረጥኩ። የእስልምና ሀይማኖት ተከታዮች የወሰዱት ስልክ ያለመጠቀም እርምጃ እጅግ አበረታች ሆኖ በማግኘቴ አድናቆቴን መገለጽም ፈለኩ። ምንም እንኳ ይህንን አይነት እርምጃ ከፖለቲካ ድርጅቶች የጠበቅሁ ቢሆንም ሌላው ዘርፍ ጀምሮታልና በዚህ ጎዳና መሄዱ መልካም ነው። ያልተቀጠቀጠ የለምና ለምን እንደ ድጋፍ ድምጽ ስልክ ያለመጠቀሙን እንደ ትብብር መግለጫ ይሆን ዘንድ ለአንዲት ቀን ለምን አናደርገውም? የፖለቲካ ድርጅቶች የአገዛዙን ክፋት አስመልከተው መግለጫ እንደሚያወጡት ሁሉ አሁን ደግሞ ሙስሊሞች ‘ጥቁሩን ሽብር’ ለመቃውም ለጀመሩት ሰላማዊ አመጽ የጋራ ጥሪና ትብብር ቢደረግ መልካም ነው።

አሁን ወያኔ የሽብር ጥቃቱን በአንድ ደረጃ ከፍ በማድረግ ብቅ ያለውን ሁሉ እስር ቤት መጨመር ቀና ያለውን ሁሉ በየመንገዱ መቀጥቀጥ፣ ጠያቂ እንኳን እንዲጠፋ ዘመድ አዝማድ እያሳደዱ ከስራ ማባረር፣ ከሀገርና ከመንደር ማፈናቀል አፍነው መውሰድና ደብዛ ማጥፋትን ከሁለተኛና ሶስተኛ አገር አፍኖ መውሰድን በፊት ለፊት ይዘውታል። ያልተነካ አንድም የፖለቲካ ፓርቲና ማህበራዊም ሆነ የእምነት ተቋም የለም። በሰላማዊ መንገድ ጥያቄያችንን እናሰማለን፣ መብታችንንም እናስከብራለን ያሉ የእስልምናና የክርስትና ሀይማኖት ተከታዮች እየተቀጠቀጡ ነው። የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላት በተለይም ወጣቶቹ ልዩ ኢላማ ውስጥ ገብተው ስቃይ እያዩ ነው። በዘርና በመንደር የተነጣጠሩ ጥቃቶች ከመቼውም በላይ አድገው ይገኛሉ።

በተለመደው የትግል መንገድ መገስገስ በተራ ለማለቅና ቅስም ለመሰባበር መንገድ ያበጃል። ምንም እንኳ የነጻነትን ትግል ገድሎ መቅበር ባይቻልም። ‘ታጋይ ይሞታል እንጂ ትግል አይሞትም’ የሚለው መፈክር መበረታቻ እንጂ ተራ በተራ እስርቤት መውረጃ ሊሆን አይገባውም። ታጋይ በተለይም መሪ እንኳን ሞቶ ታስሮም አሳምሮ ይጎዳል። መሪ የሌለው ይበተናል ወይም እስኪደራጅና እንደገና እስኪያንሰራራ ድረስ ኪሳራው አለውና ያንን መቀነስ መቻል አስፈላጊ ነው። የታሰሩ ጋዜጠኞች ብዛትና አፈናው በነፃው የመገናኛ ብዙሃን ላይ ተጽዕኖው ትንሽ አይደለም። የአንዱአለም መታሰር ተከታትሎም ተተኪ ሆነው የወጡ ወጣት ታጋዮች መታገት ይጎዳል። የአብርሃ ደስታ መታሰር ትግራይን ድምጽ አልባ እስከማድረግ ይደርሳል። አንደበተ ርቱዕ የሆኑት ሃብታሙ አያሌውና ዳንኤል ሺበሺ በጣም ያጎድላሉ። የዞን ዘጠኝ ‘ብሎገሮች’ መታሰር ነጻ ብዕር የያዙ ሚዛናዊና አስተዋይ ወጣቶችን ከሜዳው ውጪ ያደርጋል። ወያኔ እርሻ እንዳማረለት ገበሬ የበሰለ የበሰለውን መቀንጠስ ከቻለ የልቡን እየሰራ ሌላውን የጫጫታ ቤት ያደርገዋል። ወይንሸትን ፈንክቶና እጇን ሰባብሮ የሚያስር የውርጋጥ ስብስብ እንጂ መንግስት ሊባል አይቻለውም።

በአንድ ረዥም ምላስና በብዙ ጠመንጃ ሁለት አሥርት አመታት ታግተን ኖረናል። በደንባራ በቅሎ ቃጭል ተጨምሮ እንዲሉ ያ ረዥም ምላስ ከተቆረጠ በሁዋላ በቀረቻቸው ጠመንጃና ምላሱ በሚያደናቅፈው ጠቅላይ ሽቅብ ቁልቁል የሚሉት ወያኔዎች አሁን የለየለት ተዳፋት ላይ ናቸው። ወያኔ ከፋፍሎና ነጣጥሎ የሚመታበት የብልጥ ጊዜ አብቅቷል ምክንያቱም በጣም ጠግቧል በዚያው መጠንም ደድቧል። የጠገበ ደደብ የሚያስከትለው አደጋ ትንሽ አይሆንምና ተነጣጥሎ መመከት የሞኝ መንገድ ይሆናል። ስለዚህ ሁሉም የጥቃት ሰለባ ከሆነ ቢያንስ የሚያስማማ ነገር አለና ወደ ሕዝባዊ አመጽ የሚያመራውን መንገድ በጋራ ለማምጣት ቀጣይ እርምጃዎች ቢኖሩ እንዴት መልካም ነበር ብዬ አስባለሁ። አደባባይ ያልወጣ እየተሰራ ያለ ነገር ስለመኖሩ ባላውቅም የጋራ ጉባዔ የሚጠራበት ወይም ሳይነጋገሩ የሚግባቡበትና በሰላማዊ ትግል መርህ ውስጥ የሚካተት እርምጃ የሚወሰድበት ጊዜ አሁን ነው።

ምናልባትም ከሙስሊም ወገኖች ጋር ለማበርና ድጋፍም ለመስጠት እነሱ የወሰዱትን የእምቢተኛነት መንገድ በመደገፍ የስልክ ተጠቃሚነቱን ለአንድ ቀን ማቋረጥ የትግሉን መጠናከር ማሳያ መንገድም ይሆናል። ለበረቱት ጉልበት በመስጠት ሌላውም እንዲበረታታ ያደርጋል። የክርስትና ሀይማኖት ተከታዮችም የሚደርስባቸው በደል የለየለት ነውና በዚህ ከሙስሊም ወገኖች ጋር የጋራ ትብብር ወይም ድጋፋቸውን ቢገልጹ የሕዝባችንን አንድነት ማሳያ ይሆናል። በሌሎች ተቋማትም ላይ የተመጣጠነ እርምጃ መውሰዱ ወያኔን በሚገባ የሚያስደነግጠው ይመስለኛል። ቢያንስ ሁሉም የሚስማማበት ደግሞ ኢቲቪን አለመመልከት ጋዜጣ አለመግዛትና ራድዮ አለመስማት ሊሆን ይችላል። ያኔ እየተዘጋጀ ያለው ገለባ ፕሮፓጋንዳ መውደቂያ ያጣል። ቢራ አለመጠጣት እንኳን ትልቅ ቁንጥጫ ሊሆን ይችላል።

በተለይ አብዛኛው የንግድ አገልግሎትና ተቋም ከሕዝብ በተዘረፈ ገንዘብ ጥቂት ዘረኞች የያዙት በመሆኑ እርምጃው አርስበርስ የሚያፋጥጣችው ይሆናል። እንደ ወትሮው ሁሉ እያንዳንዱ ፓርቲ የራስ የራሱን የትግል ጥሪ እየያዘ እየመጣ እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ፉክክር ውስጥ እንዳይገባና ሕዝቡንም ግራ እንዳያጋባ ግን ምኞቴ ነው። ሕዝቡ ምን እናድርግ ትግሉን እንዴት እናቀጣጥለው እያለ በሚገኝበት ሁኔታ ውስጥ የፖለቲካ ፓርቲዎች የመሪነት አቅም የሚፈተሽበት ጊዜ ነውና ለሁላችንም ብርታት፣ ጥንካሬና ብልህነትን ከዚህም ጋር የሚመጣ ድልን እመኛለሁ።
biyadegelgne@hotmail.com

“መሰበር” የማይቀር ነው

July 26/214
(ርዕሰ አንቀጽ)
pieces


የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ “በድርብ አኻዝ አድጓል፤ እያደገም ይሄዳል፣ ይቀጥላል፣ ይመነደጋል” እየተባለ “በተዘመረበት” ዓመታት ሁሉ በአንጻሩ በገሃድ ያለውን እውነታ ቁልጭ ባለ መልኩ የሚያሳዩ ዘገባዎች ሲወጡ ቆይተዋል፤ እየወጡም ይገኛል፡፡ ሆኖም እነዚህ ዘገባዎች በሥልጣን ላይ ያሉትን ሁለቴ እንዲያስቡ ሊያደርጋቸው እንደሚገባ ቢነገርም ምላሹ የተለመደው “የልማት ጸሮች” ያወጡት፣ “የአሸባሪዎች እጅ ያለበት”፣ “የኒዎ-ሊበራል አቀንቃኞች ዘገባ”፣ “የኪራይ ሰብሳቢዎች ምኞት”፣ ወዘተ ከሚል አልፎ አያውቅም።
በተደጋጋሚ የሚወጡ ዓለምአቀፋዊ መረጃዎች አገራችን በመክሸፍ ወይም በመሰበር አደጋ ላይ እንደምትገኝ ይናገራሉ። እነዚህ ጥናቶች በአብዛኛው የሚወጡት በምዕራቡ ዓለም በሚገኙ የጥናት ተቋማት በመሆናቸው ከላይ እንዳልነው “የወገኑ ናቸው”፣ “የልማታችንና የህዳሴያችን ተቃዋሚዎች ናቸው”፣ “ሚዛናዊ አይደሉም”፣ “የምዕራባዊያን ምኞት ማስፈጸሚያ”፣… ሲባልባቸው ቆይቷል። ኢህአዴግ ለዚህ ዓይነቱ ፍረጃ ቀዳሚነቱን በመውሰድ ከድቃይ የሚዲያ ተቋማቱ በተጨማሪ በተለይ “በአዲስ ራዕይ” ሲያብጠለጥላቸው በየደረጃው ያለው ካድሬ ደግሞ እንደ ገደል ማሚቶ ማስተጋባቱን ይቀጥላል።
የሚሰማው ኖረም አልኖረ የማስጠንቀቂያው ዘገባ አያቆምም ማስጠንቀቁን ይቀጥላል! ጥቂቶቹ ይህንን ይመስላሉ፡-
የዛሬ አንድ ዓመት ተኩል አካባቢ “የአሜሪካ የብሔራዊ የደኅንነት ምክርቤት እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር በ2030 የሚከሽፉ 15 መንግሥታትን (failed states) ዝርዝር” አውጥቶ ነበር። “በግጭት መብዛትና በአካባቢ ጥበቃ ቀውስ ምክንያት” ይከሽፋሉ ተብለው ከተተነበዩት የአፍሪካ፣ የእስያና የመካከለኛው ምስራቅ አገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗን ተናግሮ ነበር። (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባእዚህ ላይ ይገኛል)።
የዛሬ ዓመት አካባቢ “ዓለምአቀፉ የግልጽነት ድርጅት (Transparency International) በርካታ የአፍሪካ አገራት በሙስና “መበስበሳቸውን” ከእነዚህም መካከል ኢትዮጵያ ከቀዳሚዎቹ አገራት መካከል እንደምትገኝ” ዘግቦ ነበር። “በዚህ ዘገባ መሠረት በሙስና የተዘፈቁትን አገራት በመከፋፈል ባስቀመጠው ባለዘጠኝ መዘርዝር ውስጥ ኢትዮጵያ ከመጨረሻ ሁለተኛ መሆኗን በመግለጽ ከፍተኛ የሙስና አደጋ ውስጥ ከሚገኙ አገራት ዋንኛዋ አድርጓታል። ለዘገባው ግብዓት እንዲሆን ከቀረቡ ጥያቄዎች መካከል “ጉቦ ሰጥተዋል ወይ (ያውቃል)?” በማለት ለአንድ ሺህ ሰዎች ለቀረበው የናሙና ጥያቄ 44በመቶ ኢትዮጵያውያን “አዎን” በማለት መልሰዋል። ይህ የምዕራባዊ ድርጅት ዘገባ ቢሆንም “ውርሳቸውን እናስጠበቃለን” የሚባሉት ሟቹ መለስ፤ በረሃ በነጻአውጪነት፤ ከዚያም “በመንግሥትነት” ራሳቸው ስለመሩት ድርጅት የተናገሩትን የሚያረጋግጥ ነው። እንዲህ ነበር ያሉት “ከእንጥላችን ገምተናል”! (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)።
የዛሬ ስድስት ወር ገደማ የመፈንቅለ መንግሥት ስጋት ከሚታይባቸው 40 አገራት መካከል ኢትዮጵያ በ25ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ትንበያ ተሰጥቶ ነበር። ለዚህ ትንበያ የተወሰዱት ነጥቦች “የጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ፣ የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ የእርስበርስ ግጭት፣ የነጻ ምርጫ ሁኔታ፣ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ በየቀጣናው ያለ የመፈንቅለ መንግሥት እንቅስቃሴ፣ ወዘተ” መሆናቸው ተጠቅሶ ነበር። ይኸው ዘገባ “ከሚከሽፉ መንግሥታት” ሪፖርት ጋር በመሆን በዚህ መልኩ ተዘግቦ ነበር።
እንዲህ ዓይነቶቹን መረጃዎች በሥርዓት የሚመለከቱና የሚያጠኑ ፖሊሲ አውጪዎችና ተመራማሪዎች ወራት ጠብቀው የኢህአዴግን ፈር የለቀቀ አካሄድ ከመኮነን በማለፍ “የአፍሪካ ቀንድ ስጋት” ነው በማለት በግልጽ እስከመናገር ደርሰዋል። “በኢትዮጵያ አንድ ችግር ቢፈጠር ለማረጋጋት አስቸጋሪ እንደሚሆን፣ ህዝቡ በተለይ በህወሃቶች ላይ የሚያሳየው ጥላቻ እየተካረረ መምጣቱ፣ በአገሪቱ የሚፈጸመው ያልተመጣጠነ የሃብት ስርጭት፣ አፈናውና ሌሎች የህወሃት/ኢህአዴግ ተግባራት ተዳምረው ህዝቡን ክፉኛ ማስቀየሙ ያልታሰበ ችግር ሊቀሰቅስ እንደሚችል” ጎልጉል አንድ አሜሪካዊ ዲፕሎማት ጠቅሶ የዛሬ አራት ወር አካባቢ ዘግቦ ነበር። ዲፕሎማቱ እንደሚሉት “ህወሃቶች የቀጠናው የሰላም ምንጮች ስለመሆናቸው ለራሳቸው ምስክርነት ለመስጠት ቢሞክሩም በተግባር የሚታየው ግልባጩ ነው” ማለታቸውን በዚሁ የዜና ዘገባ ተገልጾዋል። (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)።
የዛሬ ወር አካባቢ በኢኮኖሚው መስክ “በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የዓለምአቀፍ ልማት ትምህርት ክፍል ሥር የኢኮኖሚ ጥናት የሚያካሂደው የኦክስፎርድ የድህነትና የሰብዕ ልማት ማዕከል (The Oxford Poverty and Human Development Initiative (OPHI)) ያወጣው የ2014 የጥናት መረጃ ደሃ ከሚባሉት 108 አገራት ዝርዝር ኢትዮጵያ ከመጨረሻው ሁለተኛ መሆኗን” ዳጎስ ያለ ጥናት ማቅረቡ ተዘግቦ ነበር። “ትምህርት፣ ጤና እና የኑሮ ሁኔታ ማለትም ኤሌክትሪክ፣ ጽዳት፣ የሚጠጣ ውሃ፣ የንብረት ባለቤትነት፣ ወዘተ” እንደ ጠቋሚ መረጃ በመውሰድ እዚህ ድምዳሜ ላይ መድረሱን ማዕከሉ አስታውቋል። ሪፖርቱ እንዳብራራው ከሆነ በኢትዮጵያ “ከ100 ሰዎች መካከል 87ቱ ድሃ ተብለው የሚጠሩ ሲሆን 58ቱ ሰዎች ግን መናጢ ደሃ ተብለው የሚጠሩ” መሆናቸውን ጠቅሶ ድህነቱ “በተለይ በገጠር እጅግ የከፋ እንደሆነ በመጠቆም ከ100 ሰዎች ውስጥ 96ቱ ደሃዎች” መሆናቸውን በግልጽ ተናገሯል። (ጎልጉል ያጠናከረው ሙሉ ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)።
እነዚህ ለአብነት የጠቀስናቸው ከብዙዎቹ መካከል የተወሰኑት ናቸው፡፡ በምዕራባዊ ተቋማት በመውጣታቸው ብቻ ዘገባውን ጸረ-ኢህአዴጋዊ አያደርገውም፡፡ ምክንያቱም የምዕራብ ተቋማት የሚያወጡትን መረጃ በጭፍን የሚያጥላላው ኢህአዴግ ለራሱ ድርጅታዊ አሠራር የሚፈልገው ዓይነት ዘገባ በምዕራባዊ ድርጅቶች እያስወጣና እያሰራ ለፖለቲካው ድርሰት ሲጠቀምበትና ካድሬዎቹንም ይህንኑ ሲያዘምር በተደጋጋሚ ተሰምቷል።
በኮምፒውተር ፕሮግራም ቋንቋ “garbage in garbage out” የሚባል አነጋገር አለ፤ ፕሮግራም የሚያደርገው ሰው የሚጨምረው ኮድ “ጥራጊ” (ትርጉም አልባ) ከሆነ የፕሮግራሙ ውጤት “ጥራጊ” (ትርጉም አልባ) ይሆናል። “ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ” በግልባጩ እንደማለት ነው።
ከላይ የተጠቀሱትን ጥናቶች የሚያካሂዱት ተቋማት የራሳቸው አጀንዳ አላቸው ቢባልም ለዘገባቸው ግብዓት የሚጠቀሙት መረጃ ግን የሚገኘው በተግባር ከሚፈጸመውና ሕዝብ በየዕለቱ ከሚጋፈጠው የኑሮ ውጣውረድ በቀጥታ የተወሰደ ነው። እየሆነ ያለውን ነገር በየትኛውም ዓይነት ፕሮፓጋንዳ ቢሸፍኑትና ቢያጥላሉት ዕውነታውን እንዲስት ግን ማድረግ አይቻልም። የሕዝብ ሰቆቃ፣ ምሬት፣ ሃዘን፣ … ለኢህአዴግና ካድሬዎቹ ጆሮገብ ባይሆኑም የኢትዮጵያን ሰማይ ግን ጥሶ አልፎ ሄዷል። እንደፈለጉ ቢያንቋሽሹትና ቢያጥላሉትም በየጊዜው የሚወጣው ዘገባ የሕዝብን ምሬት ቁልጭ አድርጎ የሚመሰክር ነው። ኢህአዴግ ግን አሁንም “አልሰማም” በሚል ዕብሪት እንደተነፋ ነው!
ኢህአዴግ እንዲሰማ በተደጋጋሚ ከአገር ውስጥም ቢሆን ከውጭ፤ ከኢትዮጵያውያንም ይሁን ከሌሎች፤ ከተቃዋሚዎችም ሆነ ከራሱ ደጋፊዎች፤ … ቢነገረውም በተቃራኒው በሚፈጽመው ድርጊት “አልሰማም” የሚል የዕብሪት ምላሽ እየሰጠ ነው። ከውድቀት በፊት ዕብሪት እንደሚቀድም የዘነጋው ወይም እርሱንም ጭምር “አልቀበልም” ያለ ይመስላል!
አላቆም ያለው ሰቆቃ፣ እስራት፣ ግድያ፣ እንግልት፣ … የውሸት ክስ፣ የውሸት ውንጀላ፣ የውሸት ፍርድቤት፣ የውሸት ብያኔ፣ … ኅሊናን የሸጠ ዲስኩር፣ መግለጫ፣ ቃለምልልስ፣ … ጥቂቶች “አይሰማም” ቢሉም ሕዝብን እያስለቀሰ፣ እያስመረረ፣ እያንገፈገፈ፣ … ሄዷል። በሕዝብ ደምና እምባ ጸንቶ መቆም አይቻልም፤ ለዚህ ታሪክ ምስክር ነው። “ከተማን በደም ለሚሠራ ወዮለት” እንደሚል ያልተዘራ አይታጨድምና፤ “ንፋስን የዘራ ሁሉ አውሎ ንፋስን ያጭዳል”! አሁን ባይመስልም ሁሉም ወቅቱን ጠብቆ ይሆናል። እኛ የምንመኘው ወይም ከመመኘት የምንታቀብበት ቢሆንም ባይሆን “መሰበር” ግን አይቀርም! እጅግ የሚያሳስበን ግን ከዚያ በኋላ ያለው ጨለማ ነው! ሳይመሽ ጆሮ ያለው ቢሰማ መልካም ነው እንላለን!

Friday, July 25, 2014

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ደብረዘይት አየር ሃይል ግቢ ታስረው ከፍተኛ ስቃይ እየደረሰባቸው ነው

July25/2014
ሐምሌ ፲፰ (አስራ ስምንት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የግንቦት7 ዋና ጸሃፊ የሆኑት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ከሰኔ 18 ቀን 2006 ዓም ጀምሮ ደብረዘይት በሚገኘው የአየር ሃይል ግቢ ውስጥበአንድ አነስተኛ ክፍል ውስጥ ታስረው ከፍተኛ ስቃይ እየደረሰባቸው እንደሚገኝ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።

ኢሳት የተለያዩ ምንጮችን አነጋግሮ ባሰባሰበው መረጃ አቶ አንዳርጋቸው በመጀመሪያዎቹ 10 ቀናት ከፍተኛ ድብደባ ከተፈጸመባቸው በሁዋላ ድበደባው ቆሞ፣ የማሰቃያ መርፌዎችን እየተወጉና በኤልክትሪክ ሾክ እየተሰቃዩ መረጃ እንዲያወጡ እየተገደዱ ነው።

መርማሪዎች ከአቶ አንዳርጋቸው የሚፈልጉት መረጃ ከግንቦት7 ጋር በጋራ የሚሰሩ  አሁን በስልጣን ላይ ያሉ የኢህአዴግን አመራሮችን እንዲሁም በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ ያሉ አዛዦችን ስሞች ሲሆን፣ አቶ አንዳርጋቸው ግን እስካሁን ምንም አይነት መረጃ ባለመስጠታቸው ፣ መርማሪዎች ሲበሳጩ መታየታቸውን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል። ለወትሮው አንድ መረጃ ሲያገኙ በታላቅ ደስታ የሚፈነጩት መርማሪዎች፣ ምርመራቸውን ጨርሰው ሲወጡ የሚያሳዩት ብስጭት፣ እስካሁን ድረስ የሚፈልጉትን እንዳላገኙ የሚያሳይ መሆኑን ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ምንጮች ገልጸዋል።

አቶ አንዳርጋቸው እንዳስፈላጊነቱ በቀን ሶስት ጊዜ ምርመራ እንደሚካሄድባቸው የሚናገሩት ምንጮች፣ ምርመራውን የሚያካሂዱት የተመረጡ የህወሃት የደህንነት ሰራተኞች መሆናቸውንና በግቢው ለበረራ የሚሰለጥኑ የሌሎች ብሄር ተወላጆች ወይም የደህንነት ሰራተኞች ወደ አካባቢው እንደማይሄዱ ገልጸዋል። ምሽት አካባቢ የሚሰማው የጣር ድምጽ የሚረብሻቸው የእለት ተረኛ ጠባቂ መኮንኖች በሁኔታው እያዘኑ አንዳንዶች ስሜታቸውን መቆጣጠር እንደማይችሉ ምንጮች አክለው ገልጸዋል።

ስለ አቶ አንዳርጋቸው የእለት ውሎ ማወቂያ ብቸኛው ዘዴ የመርማሪዎች ፊት ነው የሚሉት ምንጮች፣ እስካሁን ድረስ ምርመራ በሚያካሂዱ የህወሃት አመራሮች  ዘንድ የደስታ ፊት እንደማይነበብ ገልጸዋል።

የኢህአዴግ መንግስት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የታሰሩበትን ቦታ ይፋ ለማድረግ እስካሁን ፈቃደኛ አልሆነም። የእንግሊዝ ባለስልጣናት ለአቶ አንዳርጋቸው የኮንሱላር የማማከር አገልግሎት ለመስጠት ጥያቄ ቢያቀርቡም ኢህአዴግ ባለስልጣናት ፈቃደኛ አልሆኑም።

ከዚህ በተቃራኒ ኢህአዴግ በአቶ አንዳርጋቸው እና በግንቦት7 ላይ ለሚሰራው ድራማ ግብአት ይሆን ዘነድ የተለያዩ ሰዎችን ማሰማራቱን ምንጮች ገልጸዋል። ቀደም ብለው በአገዛዙ ለስለላ ወደ ኤርትራ ተልከው እና ለተወሰኑ ወራት ግንቦት7 ትን ተቀላቅለው በመጨረሻ የኢህአዴግ የስለላ አባላት መሆናቸው ሲታወቅ የጠፉ እንዲሁም ፈንጅ ሊያፈነዱ ሲሉ ተያዙ የተባሉ እና በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎችን ለመጠቀም እንቅስቃሴ መጀመሩን ለማወቅ ተችሎአል።

የኢትዮጵያ ህዝብ በአቶ አንዳርጋቸው መያዝ ያሳየው ቁጣ ያስደነገጣቸው ደህንነቶች ለማንኛውም በሚል በደንበር አካባቢ ጥበቃቸውን እያጠናከሩ ነው። የአቶ አንዳርጋቸውን መያዝ ተከትሎ ግንቦት7ትን የሚቀላቀሉ ሰዎች መጨመራቸውንም ከድርጅቱ የወጣው መረጃ ያመለክታል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በቤልጂየም ብራሰልስ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ኢህአዴግ አቶ አንዳርጋቸውን ለመያዝ የሄደበትን እርቀት ከማውገዝ በተጨማሪ የእንግሊዝ መንግስት የአቶ አንዳርጋቸውን ጉዳይ አጥብቆ እንዲከታተል ጠይቀዋል። ኢትዮጵያውያኑ ዛሬ በአውሮፓ ህብረት ቆንስላ ጽ/ቤት ፊት ለፊት የተቃውሞ ድምጻቸውን በከፍተኛ ቁጣ ከማሰማት በተጨማሪ፣ ያዘጋጁትን ደብዳቤ ለአውሮፓ ህብረት ባለስልጣናትና ለእንግሊዝ መንግስት ኮንስላ ጽ/ቤት ሃላፊዎች አስረክበዋል።

መኢአድ የሕዝበ ሙስሊሙን ጥያቄዎች መንግሥት በአስቸኳይ እና በተገቢው ሁኔታ መልስ እንዲሰጣቸው ጠየቀ

July 25/2014
ከመላው ኢዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የተሰጠ መግለጫ
(ፎቶ ከፋይል)
(ፎቶ ከፋይል)

ለረዥም ጊዜ በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ ጥያቄዎቻቸውን ሲያቀርቡ በነበሩ የእስልምና እምነት ተከታዮች ላይ ህውሓት/ኢህአዴግ የወሰደውን የኃይል እርምጃ አጥብቀን እናወግዛለን ፡፡ እንደ መኢአድ እምነት ለጥያቄዎቻቸው ተገቢውን መልስ መስጠት ሲገባ በግልባጩ መላው የኢትዮጵያን ሕዝብ ያሳዘነና ያስቆጣ የኃይል እርምጃ መወሰዱ የህውሓት/ኢህአዴግን ማንነት በተግባር ያሳየ ድርጊት ነው፡፡
ሐምሌ 11 ቀን 2006 ዓ.ም የእስልምና እምነት ተከታዮች በአንዋር መስጊድ በፀሎት ሥነ-ሥርዓታቸው ላይ ለጥያቄዎቻቸው መልስ እንዲሰጣቸው በመጠየቃቸው ጥያቄዎቻቸውን ወደጐን በመተው የኃይል እርምጃ በመወሰዱ ችግሩ ይፈታል ብለን አናምንም፡፡ ሆኖም በእለቱ በእምነቱ ተከታዮች ላይ እና በአካባቢው በነበሩ ሰላማዊ ሰዎች ላይ የፀጥታ ሃይሎች የወሰድትን የሀይል እርምጃ አጥብቀን እናወግዛለን፡፡ አሁንም ቢሆን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ጥያቄዎቻቸው በሰላማዊና ኢትዮጵያዊ ጨዋነት መፈታት አለበት ብለን እናምናለን፡፡ የህውሓት/ኢህአዴግ አባገነን ሥርዓት በእምነት ተቋማት ላይ እጁን አስረዝሞ የሚያደርገውን የአፈና ተግባር ማቆም አለበት፡፡
መኢአድ ለእስልምና እምነት ተከታዩችም የሚያስተላለፈው መልዕክት ከአሁን ቀደም በሰላማዊ መንገድ ጥያቄዎቻችሁን እንዳቀረባችሁት ሁሉ መፍትሔ እስክታገኙ ድረስ በሰላማዊ መንገድ መቀጠል እንዳለባችሁ ያሳስባል፡፡ በመጨረሻም መኢአድ የሚያምነው ችግሩ ስር ነቀል መፍትሔ የሚያገኘው የህውሓት/ኢህአዴግ አባገነን ሥርዓት በዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ሲተካ ብቻ ነው፡፡ በመሆኑም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እና የሙስሊሙ ማህበረሰብ መኢአድ የሚያደርገውን ሰላማዊ ትግል በመቀላቀልና በመደገፍ የበኩላችሁን አስተዋፅኦ እንድታደርጉ ጥሪያችንን እናስተላልፉለን፣፣
አንዲት ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!
ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም

የተዓማኒነት ጉድለት ያለበት መንግስት… ከግርማ ሰይፉ ማሩ

July 25/2014
መንግሰት የሚባለው ነገር ምን እንደሆነ ግራ ገብቶኋቸው ግራ የሚያጋቡን የመንግሰት ኃላፊዎች ያሉበት ሀገር ውስጥ ነው የምንገኘው፡፡ በሃላፊነታቸው ደረጃ የሚመጥን ማስተካከያ ለመውሰድ አቅምም ፍላጎትም የላቸውም፡፡ የተሸከሙት ሃላፊነት መንግሰት ብለው ለሚያስቡት አንድ ግዑዝ ነገር ለአገልጋይነት እንጂ፤ እነርሱ የመንግሰት አካል እንደሆኑ አይረዱትም፡፡ ይህን እንድንል የሚያደርገን መንግሰታችን ብለን በኩራት ግብር የምንከፍለው፤ መንግሰታችን ዜጎች በሰላም ወጥተው በሰላም አንዲገቡ የሚያደርግልን ተቋም ነው፤ ሀገራችን በልማት በልፅጋ ዜጎች የልማቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ስርዓት ነው፣ ይህ ሁሉ ሆኖም ችግር ቢገጥመን በገለልተኝነት በፍትህ ስርዓት ዳኝነት የምናገኝበት ነው፤ ብለን ማመን ቢቸግረን ነው፡፡ እነዚህ የመንግሰት ሃላፊ ተብዬዎች እነርሱ የተጣለባቸውን ኃላፊነት መወጣት ሲያቅታቸው እኛ በእንድ ወይም በሌላ መንገድ ችግራቸውን በጠቆምናቸው ወደ ትክክለኛ ደረጃ ማደግ ትተው እኛ ወደ እነርሱ እንድንወርድ፣ እንድንዋረድ፣ ለሆዳችን እንድናድር ወደ ገደል ይጎትቱናል፡፡
እውነቱን ለመናገር የኢትዮጵያ መንግሰት የሚባለውን አካል ለመደገፍ፤ በህግ የተሰጠውን ተግባር አንዲወጣ ማገዝ እንደ ዜጋ መብቴ ነው ብቻ ሳይሆን እንደ ግዴታም የምመለከተው ነው፡፡ አሁንም የማደርገው ነገር ሁሉ የማድረገው በዚሁ መንፈስ ግዴታዬን ለመወጣት ነው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ የሚደረግለትን ድጋፍ መቀበል የማይችል መንግሰት ሆኖዋል፣ ልክ ጥሩ ምግብ ሲያጎርሱት እንደሚያስመልሰው በከፍተኛ ደዌ እንደተያዘ በሽተኛ፣ ወይም ቤት እንዲጠብቅ ጠላት ሲመጣ እንዲያነቃን ያሳደግነው ውሻ በተቃራኒው ቤተኛውን በሙሉ መናከስ እንደጀመረ ውሻ ሆኖዋል፡፡ መንግስት ምክር አይሰማም ብቻ ሳይሆን በተቃራኒው ምክር የሚሰጡትን ለማጥፋት በከፍተኛ ትጋትና ከፍተኛ በጀት መድቦ እየተንቀሳቀሰ እንደሆነ ነው እየተሰማን ያለው፡፡ ይህ ድርጊቱ በቀጣይ ዜጎች ከመካሪነት ወጥተው ሀገርን ወደማይጠቅም አውዳሚ አማራጭ መስመር እንዲገፉ እንደሚያደርግ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ እሰከ አሁን የተገፉትን ሳይጨምር፡፡
ዛሬ የመረጥኩትን ርዕስ እንድመርጥ ያደረገኝ መንግሰት ሰሞኑን እያሳየ ያለው ባሕሪ ነው፡፡ መቼም መንግሰት የሚገለፀው በመንግሰት ሃላፊዎች ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ መንግሰትን የሚመሩት ግለሰቦችም ሆኑ አካላት በመንግሰት ሃላፊነት ላይ የሚመድቧቸውን ሰዎች በህዝብ ፊት እንዲቀሉ ማድረግ ያለባቸው አይመስለኝም፡፡ እነዚህ ግለሰቦች እንዲቀሉ ሲያደርጉ የሚቀሉት አበረው መሆኑን እንዲሁም መንግስት የሚባለውን ሰርዓት የሚመራው አካል ጭምር ነው፡፡ እራሱ የሾመውን አካል ጭምር ማለት ነው፡፡
ይህን ሀሳብ ያነሳሁት አቶ ጌታቸው ረዳ የተባሉ የጠቅላይ ሚኒሰትሩ ቃል አቀባይ “መንግሰት አቶ አንዳርጋቸውን አልተረከበም” ብለው በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ለህዝብ ይፋ አደረጉ፡፡ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል በመግለጫው “የየመን መንግሰት እንዲይዛቸው አደረግን የዚያኑ ዕለት ተረከብናቸው” አለ፡፡ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይሉ ጅግንነቱን ለመግለፅ የመንግሰት ቃል አቀባዩን ማዋረድ ለምን አስፈለገ? ከዚህ ቀደም እንደልምድ ሆኖ የመንግሰት ኮሚኒኬሽን ፅ/ቤት ከፍተኛ ሹም የሆኑት አቶ ሽመልስ ከማል ሆን ተብሎ በሚመስል ሁኔታ እንዲህ ዓይነት ተቃርኖ ያለበት አሰተያየት እንደሚሰጡ ይታወቃል፡፡ በዚህ የተነሳም እኝህን ከፍተኛ የመንግሰት ሹም የሚያምን ለማግኘት እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ ይህ ግለሰቦችን የማዋረድ ድርጊት መንግሰትን የሚጠቅመው እንዳልሆነ ግን ግልፅ መሆን አለበት፡፡ የመንግሰትን አቋም እንዲነግሩን የተመደቡ ሰዎች “አይታመኑም” ማለት አጭር እና ግልፅ በሆነ ቋንቋ “መንግስት አይታመንም” ማለት ነው፡፡ የተዓማኒነት ጉድለት ያለበት መንግሰት ሲመራን ደስ አይለንም፤ ለዚህም ነው መንግስት አንዲታመን የምንወተውተው፡፡ ይህ የምንሰጠው አሰተያየት በምንም መልኩ የሀገርን ገፅታ ማበላሸት ሳይሆን፤ ሀገራቸንን ወክለው የሚዋሹትን የመንግሰት ሹማምንት በመምከር ለሀገር ገፅታ ግንባታ መትጋት ነው፡፡ ብንዋሽም ለሀገር ገፅ ግንባታ ሲባል ዝም በሉን ከሆነ መርዕ አልባነት ስለሚሆን መስማት ቢቻልም መስማማት አይቻልም፡፡ ያለምግባባታችን ምንጩ በመርዕ ጉዳይ ያለመስማማት ነው፡፡
የመንግስ ተዓማኒነት የሚጎዱ ብዙ ድርጊቶች ማንሳት ቢቻልም፤ አሁን ደግሞ የፓርቲያችን አባል የሆነውን ሀብታሙ አያሌውን በምንም ምክንያት ቢይዙት መንግሰትን ለመማን በፍፁም ዝግጁ አይደለንም፡፡ መንግሰት ሁሌም እንደሚለው ክምር ማስረጃ አይደለም አንድ ገፅ ማስረጃ ያቀርባል ብለን አንጠብቅም፡፡ ይህን ለማለት የሚያሰደፍር በቂ ተሞክሮ አለን፡፡ ከብዞዎቹ አንዱ አንዱዓለም አራጌን ለእስር ያበቁበት መረጃ ነው፡፡ በህይወቴ ከደነገጥኩበት ቀን አንዱ አንዱዓለም አራጌ የታሳረ ዕለት ነው፡፡ ምከንያቱም የቀረበበት ክስ “ከግንቦት ሰባት” ከሚባለው “ሁሉን አቀፍ” የሚበል የትግል ስልት ከሚከተል በውጭ ሀገር ከሚገኝ ፓርቲ ጋር ግንኙነት አለው የሚል ስለ ነበር ነው፡፡ በወቅቱ አንዱዓለም አራጌ ላይ የሚያቀርቡትን መረጃዎች በጉጉት ነበር ስጠብቅ የነበረው፡፡ ነገር ግን አንድም ማስረጃ ሳይቀርብበት፣ አዳፍኔ ምስክሮችም እንደሰለጠኑት አሟልተው ሳይመሰክሩ የሰላማዊ ትግል ጓዳችን “በአሸባሪነት” ጥፋተኛ ነው ተብሎ እድሜ ልክ ተፈረደበት፡፡ ከዚያን ቀን ወዲህ ማንም ላይ ማስረጃ አለኝ ቢሉ ለማመን እቸገራለሁ፡፡ መንግሰት በሚፈፅማቻው ተግባራት ምክንያት ተዓማኒነቱን እየጎዳው ይገኛል፡፡ ቀበሮ መጣ እንደሚለው ውሽታም እረኛ ማለት ነው፡፡
በእኔ እምነት ከሳሾቹም ሆነ ፈራጆቹ የሰጡት ውሳኔ “ክምር ማስረጃ” አለን ያሉትን የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ቃል ለማክበርና ለማስደሰት እንደነበር መጠራጠር አያሰፈልግም፡፡ እርሳቸውም ደስታቸውን ሳያጣጥሙት በተፈጥሮ ህግ ተለይተውናል፡፡ የቀረበውን ክምር ማስረጃ ታሪክ መዝግቦ ይዞታል ከሳሹችም ሆኑ ፈራጅች በታሪክ ፍርድ ፊት እንደሚቆሙበት ቅንጣት ያህል ጥርጥር የለኝም፡፡ ይህንን ጉዳይ አስመልክቶ አሁን በምንፅፈው፣ በምንናገረውም ሆነ ከዚህ በፊት በያዝነው አቋም ሁላችንም የታሪኩ አካል ነን፡፡ ሊፈርድብን ወይም ሊፈርድልን፡፡
የዛሬ ዓመት አካባቢ በደሴ ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ ለማስተባበር ከተመደበ ቡድን ጋር ተንቀሳቅሼ ነበር፡፡ ወቅቱ ደግሞ አንድ የሙስሊም የሀይማኖት አባት የተገደሉበት ነበር፡፡ በወቅቱ በደሴ ከተማ የተገነዘብኩት ነገር ቢኖር አብዛኛው የከተማ ነዋሪ “የሀይማኖት አባቱን የገደላች መንግሰት ነው” የሚል መደምደሚያ ላይ ደርሶ ነበር፡፡ በሰልፍ ላይ የተገኙ ሰዎችም “እየገደሉ ገደሉ አሉን” የሚል መፈክር በከፍተኛ ሰሜት እያሰሙ ቅሬታቸውን ሲገልፁ ነበር፡፡ በግሌ መንግሰት በዚህ ደረጃ ወርዶ በግለሰቦች ግድያ መጠርጠሩ ምቾት አልሰጠኝም፡፡ በተለያየ አጋጣሚ ያገኘኋቸውን የመንግሰት ሹሞች በዚህ ደረጃ መንግሰት መጠርጠሩ እንደሚያሳዝን አሁንም ቢሆን መስራት ያለባቸው የተቃዋሚዎች ስራ ነው እያሉ በአላስፈላጊ ፕሮፓጋንዳ ከሚጠመዱ፤ መንግሰትን በዚህ ደረጃ ለመጠርጠር ገፊ የሆነው ችግር ምንጭ ምን እንደሆነ እንዲመረምሩ አሳቤን አካፍያቸው ነበር፡፡ ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆኖ እኔንም ከአሽባሪና አክራሪነት ጋር ደምረው ልወደድ ባይ ጋዜጠኞች ዶክመንተሪ ፊልም ሰሩብኝ፡፡ ሀይ የሚል አልነበረውም ይልቁንም በተለያየ አጋጣሚ የማገኛቸው ኢህዴጎች የኢቲቪን ድራማ እያዩ እኔን መኮንን ነው የያዙት፡፡ እኔን በዚህ ደረጃ ከመጠርጠር እራሳቸውን መጠርጠር የሚቀላቸው ይመስለኛል፡፡ የእኔ ጥያቄ መንግስት ለምን በዚህ ደረጃ ይጠረጠራል? የመንግሰት ተዓማኒነት መጎደልን ለማሳየት ከዚህ የተሻለ ማስረጃ ማቅረብ ይከብዳል፡፡ እንዴት መንግሰት በግለሰብ ግድያ ይጠረጠራል? ሹሞቹ ግን ይህ አላሳፈራቸውም ቅድሚያ የሰጡት ለፕሮፓጋንዳው ነው፡፡
የተለያዩ ሀገሮቸን ለመጎብኝት እድል አጋጥሞኛል መንግስት ሊገድልህ፤ ሊያስገድልህ፤ በማጅራት መቺ ሊያስመታህ ይችላል ተብሎ የሚታመንባቸው ሀገሮች እጅግ ጥቂቶች ናቸው፡፡ የወደቁ ወይም በመውደቅ ላይ ያሉ መንግሰታት ናቸው፡፡ የሀገሬ መንግሰት እንዲህ እንዲሆን አልፈልግም፡፡ እንዲህ ዓይነት ግምት የሚሰጡ ሪፖርቶች ሲወጡ መንግትን ስለማልደግፍ ጮቤ አልረግጥም፡፡ ይልቁንም አዝናለሁ፡፡ በቅርቡ አንዲት ሴት መኖሪያ ቤቴ ድረስ መጥታ በከፍተኛ የመንግሰት ሹም ፆታዊ በደል እንደደረሰባት ነገረችኝ፡፡ ለነገሩ ጉዳዩ የግል ግንኙነት ከመሆኑ አንፃር ብዙም ፍርድ ቤት የሚያስኬድ ባሕሪ እንዳለው ባይገባኝም፤ የተነፈገ መብት አለኝ ካለች ፍርድ ቤት እንድትሄድ ነገርኳት፡፡ “ፍርድ ቤት ብሄድም ትርጉም የለውም፤ ይህን ማድረጌን ከሰሙ ያስገድሉኛል፤ አንተ በደንብ አታውቃቸውም አለቸኝ፡፡” ደነገጥኩ!! እውነት ነው ከሷ በላይ አላውቃቸውም፤ በግልፅ አንሶላ ተጋፋ ውስኪ ተራጭታ የሚያደርጉትን ታውቃለች፡፡ በመጨረሻም ከእኔ የምትፈልገው ነገር እኔ ላድርግላት እንደማልችል፤ እኔም ከመስመር አልፎዋል ያሉ ቀን ሊገድሉኝ፣ ሊያስገድሉኝ ካዘኑልኝ ደግሞ እስር ቤት ሊወረውሩኝ እንደሚችሉ አምኜ በድፍረት እንደምንቀሳቀስ ነገርኳት፡፡ ይህን ታሪክ ያነሳሁት መንግስት ከለላ የሚሰጠን ጠባቂያችን ሳይሆን ሊገድለን፣ አደጋ ሊያደርስብን የሚችል ነው ብለን ተዓማኒነት እንድንነፍገው ለምን ሆነ? ብዬ ለመጠየቅ ነው፡፡ የመንግሰት ተቃዋሚ ሆኖ አይደለም፤ መንግሰትን ከሚወክሉት ሹሞች ጋር ሲዳሩ መክረም እንደ ውለታ ተቆጥሮ ዋስትና አይሆንም፡፡ የፈለጉ ቀን ከህግ ሰርዓት ውጭ ማሰገደል የሚችሉ ናቸው፡፡ መንግሰትን የሚወክሉት ሹሞች፡፡ ግን ለምን አንዲህ ሆነ?
መንግሰት ለሚያደርጋቸው ነገሮች፣ ለሚወሰደው እርምጃ ተገማችነት አለመኖር ለተጠርጣሪነት እና ተዓማኒነት ጉድለት እንደሚያጋልጠው እርግጥ ነው፡፡ ይህን መከላከል ሲገባ ደግሞ ይህን የሚያጠናክሩ ድርጊቶችን በተደጋጋሚ ማየት መንግሰት ተዓማኒ አይደለም ብቻ አይደለም አንድ አንድ ሰዎች በድፍረት እንደሚሉት “መንግሰታዊ ውንብድና” ነው፡፡ ያሰገድሉናል የሚባል አቋም ሲያዝ ፍርድ ቤት አቅርበው አንዳለሆነ ግልፅ ነው፡፡ በአህአዴግ መንግሰት ከሁለት ሰዎች በላይ በህግ ውሳኔ በሞት የተቀጣ እንደሌለ እናውቃለን፡፡
ይህንን “የመንግሰትን ተዓማኒነት ጉድለት” የሚመለከት ፅሁፍ እያዘጋጀሁ ሳለ የግሌ አስተያየት እንዳይሆን የፌስ ቡክ ጓደኞቼ አስተያየት እንዲያዋጡ መጠየቅ ፈለጉህ፡፡ እንዲህም ብዬ በፌስ ቡክ ላይ ለጠፍኩ “እባካችሁ የመንግሰትን ተዓማኒነት ጉድለት የሚያሳይ አሳብ አዋጡ!! ከሌላችሁ በእውሽት ላይ የተመሰረተ ክስ ወይም ጠቅላላ አስተያየት ተቀባይነት የለውም፡፡ አመሰግናለሁ ……” የሚል ነበር፡፡ ተቀባይነት የሌላቸው አጠቃላይ አሰተያየቶችን ጨምሮ እጅግ ብዙ አስተያየት በአጭር ጊዜ ቀረበልኝ፡፡ በመሰረታዊነት ህገ መንግስቱን እና ህገ መንግሰታዊ ሰርዓቱን እንዲያከብሩ የሚጠይቅ ሲሆን፤ በግልፅ ምሳሌ ተደርገው ከተጠቀሱት ዋና ዋናዎቹ ከኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ማግስት ባድመን አሰመልክቶ የተሰጠው መግለጫ፣ ዜጎች መንግሰት ላይ እምነት ቢኖራቸው በሚሊዮን ለምን ይሰደዳሉ?፣ ኢቲቪን ተመልከት፣ ፍርድ ቤቶች ምን እየሰሩ ነው፣ የደህንነት ተቋም ለማን ነው የሚሰራው? ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ ነው ብለህ ታምናለህ? የሚሉና ከነአካቴው መንግሰት አለ ወይ? የሚሉት ይገኙበታል፡፡ አሰተያየቶቹ ሁሉንም የመንግስት አካላት የዳሰሱ ናቸው፡፡ መንግሰት ዜጎች በዚህ ደረጃ ተዓማኒነት እንዲነሱት ለምን ይተጋል ብለን መጠየቅ የለብንም ትላላችሁ?
ምኞቴ መንግሰታቸን ብለን የምናከብረው መንግሰት አንዲኖረ ነው፡፡ ግልፅ ነው በአሁኑ ስዓት የለንም እያልኩ ነው፡፡ ይህ ደግሞ የሚገለፀው መንግሰትን ወክለው በሚታዩት ሹማምንቶች ባህሪና ተግባር ነው፡፡ የሀገርን ገፅታ ለመግንባት ከሊቅ እስከ ደቂቅ ኃላፊነት እንዳለብን እና ግዴታችን እንደሆነ ባምንም ይህን ከፍተኛ ኃላፊነት ግን ያለምንም ማወላወል በተግባር ሊያውል የሚገባው እና ሞዴል ሊሆነን የሚገባው መንግሰት ነው፡፡ መንግሰት ደግሞ በኃላፊዎቹ ይወከላል፡፡ የእኛ ተግባር ትክክለኛ ስራ ሲሰሩ ሞዴሎቻችን አድርገን መውስድና ትክክለኛ ተግባራቸውን ማስፋት፤ ካልሆነ ደግሞ ያልሆኑትን ናቸው ብለን መቀለድ ሳይሆን አትመጥኑንም ብለን መንገር ነው፡፡ ጆሮ ያለው ይስማ!!!!!
ቸር ይግጠመን