Wednesday, September 26, 2018

የነአቶ በቀለ ገርባ መግለጫ አድራሻው ለማን ነው?

September 26, 2018
ከቀሲስ መልአኩ ባወቀ ( ሎስ አንጀለስ)

እነ አቶ በቀለ ገርባ የሰጡትን መግለጫ አነበብኩ፤ የአንዳንዶችንም አስተያየት ሰማሁ። ምንም እንኳ አላማው ያነጣጠረው በኢሳትና በግንቦት ሰባት ላይ ቢሆንም እነርሱ የፈሩት፥ ግንቦት ሰባትን ወይም ኢሳትን አይደለም። የፍርሃታቸው አድራሻ ለምኒልክ ቤተ መንግሥት ለነ ዶክተር ዓቢይ ነው ።

እነ አቶ በቀለ ገርባ የፈሩት ካልጠበቁት አቅጣጫ የወጣውን የኢትዮጵያዊነት እሳት ነው። ይህ አዲሱ የለውጥ አየር፥ ለብዙ ዓመታት የተለፋበትን የዘር ፖለቲካን የዶግ አመድ እያደረገው ነው። ( የዘር ፖለቲካ የሕዝቦችን ማንነት የሚያስከብር ሳይሆን አንድን ዘር ከሌላው እያስበለጠ ጥላቻን የሚሰብክ እንደሆነ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሃያ ሰባት ዓመት አይቶታል።)

ተቃውሞው ለግንቦት ሰባት ይምሰል እንጂ፥ ተቃውሞው ለነዶ/ር ዓቢይ ነው ብለናል። የኢትዮጵያን ሕዝብ ተቃውሞ ስለፈሩ ለጊዜው ዋናውን ዒላማ ወደጎን ትተውታል። የሚቀጥለው የአመጽ አጀንዳቸው ይህ እንደሆነ በግልጥ ካሳዩን ግን ቀናት ተቆጥሯል። ለምን? መልሱ ግልጥ ነው።

ኢትዮጵያዊነት ሥር እየሰደደ ነው። ኢትዮጵያዊነት፥ የኦሮሞ ልጆች በሆኑት በነ ዓቢይ አህመድና ለማ መገርሳ መሪነት በመላው ኢትዮጵያዊ ልብ ውስጥ እየሠረጸ ነው። ሕዝባችን ባለፉት ወራት፥ እንጨት እንጨት የሚለውን የማርክሲስም ዲስኩር አሽቀንጥሮ የጣለ፥ ከጥላቻ የጸዳ፥ የቆሰለውን ልባችንን የሚያክም የይቅርታና የአንድነት ቃላት ከመሪዎቹ አድምጦአል። ንግግራቸውን በእንባ አድምጦአል። ብሔራቸውን ሳይጠይቅ በአንድ ልብ ደግፎአቸዋል። ዓቢይ፥ዓቢይ፥ ዓቢይ፥ ለማ፥ ለማ፥ ለማ ብሎ ጮዃል።

ይህ ሲባል ግን ለውጡ ፈተና የለውም ማለት አይደለም። በጎሣ ጥላቻ ላይ የፖለቲካ ቀሳቸውን የተከሉ ኃይላት፥ በመውተርተር የንጹሐን ወግኖቻችንን ደም በየአቅጣጫው በሶማሌ፥ በኦሮሚያ፥ በቤኒሻንጉል፥ በአዋሳ፥ ወዘተ . . . የኦሮሞን የአማራን፥ የጋሞን፥የወላይታን እና የሌሎችንም ወገኖቻችንን ደም አፍስሰዋል። ሚሊየኖች ከሶማሌ እና ከሌሎችም ክልሎች ተፈናቅለዋል። ወደ ሁለት ሚሊየን የሚጠጉትን የኦሮሞና የጌዴዎ ወገኖቻችንን በምሳሌነት ማንሳት ይቻላል።

ይህም ሆኖ ሳለ፥ የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን « ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው» በሚሉት መሪዎቹ ባየው የፍቅር መልእክት ውስጥ፥ የሞቱትን ወገኖቹን እየቀበረ፥ የተፈናቀሉትን እየረዳና እንባውን እየጠረገ፥ ከመሪዎቹ ባገኘው የመደመርና የአንድነት መንፈስ ተስፋን ሰንቋል።

ኢትዮጵያዊነት ኦሮሞነትን ወይም አማራነትን መደምሰስ አይደለም። ሁሉም ሕዝብ ክቡር ነው ። አንዱ በአንዱ አይደለዝም፥ አይሰረዝም። ኢትዮጵያዊነት ግን ኢትዮጵያዊነት፥ ተከባብሮ፥ ተሳስቦ መኖር ነው። ከመግደል ይልቅ መወያየት፥ ከመጣል ይል ማንሳትን መለማመድ ነው። ይህን የለውጥ ኃይሎቹ አሳይተውናል። ነጻ ሚዲያ፥ ነጻ አስተሳሰብ፥ ከሁሉ በላይ ፍቅር እና ይቅር ባይነትን ተመልክተናል።

ይህ ለእነ አቶ በቀለ ገርባ አልተዋጠላቸውም። ከምኒልክ ቤተ መንግሥት እየወጣ ያለው መልእክት፥ እነርሱ ከያዙት ጽንፈኛ ከሆነው የዘረኝነትና አሁን ማንሳት ከማልፈልገው አጀንዳ አንጻር፥ የትም የማያላውሳቸው ነው። ለውጡን የተደመሩት፥ የለውጡ ኃይል ወደ ምኒልክ ቤተ መንግሥት የሚወስደውን መንገድ ይጠርግልናል ብለው ነው። ታዲያ መሰናክል መስሎ የታያቸውን ኢትዮጵያዊነትንና ለኢትዮጵያዊነት አጋዥ ኃይል ሊሆኑ ይችላሉ የተባሉትን ሁሉ ከመንገድ ለማስወገድ ቆርጠው ተነሥተዋል።

የመንግሥትን ሥልጣን የያዘው ኃይል፥ ተቃዋሚዎቹን ተፎካካሪዎቼ ብሎ ሲጠራ አድምጠናል። የነአቶ በቀለ ገርባ ቡድን ግን የእስር ቤት ጓደኞቻቸውን፥ ለእርሳቸው መፈታት ድምጹን ከፍ አድርጎ የጮኸውን ሕዝብ ጠላቶቼ ብሎ መግለጫ አውጥቶአል። መግለጫው በግልባጭ የተላከው ለግንቦት ሰባት ይሁን እንጂ በዋናነት የተላከው ወደ ምንሊክ ቤተ መንግሥት ነው። የለውጡ ኃይል ምላሽ ምን ይሆን?

ለጊዜው ያየነውና እያየን ያለነው የሚያስፈራ እና የሚያሳፍር እየሆነ ነው። ስድብ እየተዛወር፥ ክስ እየተጣመመ ነው። የገደሉ ከመሪዎቻችን ጋር ጉባኤ ተቀምጠው ሳለ ፥ ምግብ ያቀበሉ እየታሠሩ ነው። በአደባባይ ሁለት መንግሥት እንዳለ የተናገሩት እንዳሻቸው እየሆኑ፥ ወጣቶች እየታፈሱ ነው። ገዳዮች እንደፈለጉት እየተምነሸነሹ፥ እየታሠሩ ያሉት ገዳዮችን አስቆጥተዋል የተባሉ ወጣቶች ናቸው። ሁኔታው ያስፈራል ያሳፍራልም ብለናል። የሚያስፈራው የለውጡ ኃይል ታግዷል፥ ሾፌሮቹ « ባለ ሁለት መንግሥቶቹ» ናቸው ወይ? የሚለው አሳብ በአእምሮአችን ውልብ ማለቱ ነው። የሚያሳፍረው ዓይን ያወጣውን ማስረጃ በአደባባይ ለማስተባበል የሚደረገው መንተባተብ ነው።

ይህ አንድም ከፍርሃት የመነጨ፥ ወይም ከአቅም ውሱንነት፥ ወይም ከተሳሳተ ስሌት የመነጨ ነው። ወይም ኃላፊነትን ኃላፊነት ለጎደላቸው delegate ከማድረግ የመጣ ነው።

በዚሁ ሁሉ ግን እኛ ኢትዮጵያውያን አንድ ነገር እናምናለን። ኢትዮጵያ እጆቿን ለእግዚአብሔር የዘረጋች ስለሆነች፥ እጣ ፈንታዋ በእርሱ እጅ ነው። ፕሮፌሰር ኃይሌ ገሪማ እንዳሉት፥ « ኢትዯጵያ በአንተ አልመጣችም። በአንተም አትጠፋም።» በመሆኑም የኢትዮጵያ እጣ ፈንታ በበቀለ ገርባም ወይም ከእርሳቸው ጀርባ ባለው ኃይል እጅ ውስጥ አይደለም። የኢትዮጵያ አምላክ ልዑል እግዚአብሔር ነው።

ለለውጡ ኃይል ግን አንድ ሁለት ቃላትን ልናገር። አንደኛ፥ ዘር ቀለም ጎሣ ያልወሰነው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጎናችሁ ነው። ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር ደግሞ በዙፋኑ ላይ ነው። ሕዝባችሁን ይዛችሁና እግዚአብሔርን ፈርታችሁ ለኢትዮጵያ የሚበጀውን ነገር አድርጉ። እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ።

No comments: