Wednesday, May 8, 2013

ጋዚጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቤቱን እንዲለቅ ተገደደ

ሚያዚያ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ለጋዜጠኛው ቅርበት ያላቸው ወገኖች ለኢሳት በላኩት መረጃ እንደገለጹት ጋዜጠኛ ተመስገን ተከራይቶ በሚኖርበት ቀበና አካባቢ ያለው ቤቱን እንዲለቅ በአከራዩ የተነገረው አንድ የመስተዳድሩ ባለስልጣንና አንድ ማንነቱ ያልታወቀ ግለሰብ አከራዩ ቤቱን እንዲያስለቀቁት ማስጠንቀቂያ ከ...ሰጡዋቸው በሁዋላ ነው።

የቤት አከራዩ “ ሁለቱ ሰዎች መጥተው ለመሆኑ ተመስገን ምን እንደሚሰራ ያውቃሉ ወይ? ተመስገን ማን እንደሆነስ ጠንቅቀው ያውቃሉ ወይ? ለማንኛውም ዛሬ የምናሳውቅዎት እርሱ ለአካባቢው ሰላም ያሰጋል፣ ከዚህ በሁዋላ እንዳያስቀጥሉት ” ብለው እንዳስጠነቀቁዋቸው ለጋዜጠኛው በመንገር በአስቸኳይ ቤት እንዲፈልግ ተማጽነዋል። ጋዜጠኛ ተመስገንም ቤቱን በፍጥነት ለቆ ለመውጣት እንደሚቸገርና የአንድ ወር የቤት መፈለጊያ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል።

የፍትህ ጋዜጣ አዘጋጆች ለራሳቸው አሲምባ የሚል ስም በሰጡት የጋዜጠኛው መኖሪያ ቤት ውስጥ የኢዲቶሪያል ስብሰባዎችን እና ጽሁፎችን ያዘጋጁ እንደነበር ለማወቅ ተችሎአል።

ጋዜጠኛ ተመስገን የሚያዘጋጀው ፍትህ ጋዜጣ በመንግስት ጫና እንዲቋረጥ ከተደረገ በሁዋላ ጋዜጠኛው ህተመቱን ሊያስቀጥል የሚችልበትን ፈቃድ እስካሁን አላገኘም። ከ106 በላይ ክሶች ያሉበት ተመስገን ፣ አሁንም ጽሁፎችን በፌስቡክና በተለያዩ ድረገጾች በመጻፍ ላይ ይገኛል።

No comments: