Tuesday, December 4, 2012

የሙስሊም ወገኖቻችንን የመብት ጥያቄ ጥላሸት መቀባት በእሳት መጫወት ነው ።


በስደት የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አባላት አስተባባሪ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ
ሕዳር 24, 2005 ዓ.ም
የሙስሊም ወገኖቻችንን የመብት ጥያቄ ጥላሸት መቀባት በእሳት መጫወት ነው ።
“ይሉሽን በሰማሽ ገበያ ባልወጣሽ” እንዲሉ ወያኔ/ኢሕአዴግ በመንግስት ስም ሥልጣን ላይ ተቀምጦ በድርጅትም በግልም ነፃነቴ ይከበር ፣ ነፃነቴ አይደፈር ፣ ንብረቴ አይዘረፍ ፣ እትብቴ የተቀበረበት መሬት ለባዕድ አገር ከበርቴ አይሸጥብኝ፣ የዕምነቴን ሥርዓት በነፃነት ላከናውን….ወዘተርፈ የሚለውን ሁሉ ሽብርተኛ በሚል የሀሰት ውንጀላ ለስቃይና ለመከራ ሲዳርግ ቆይቷል። አሁንም ቀጥሎበታል። የኢትዮጵያ መምህራንና ማህበራቸው ኢመማ ይሕን ለመሰለው የወያኔ የሀሰት ክስና ውንጀላ ሥርዓት ፣የአዳፍኔ (የአባይ) ምስክርነት፣ የፍርደገምድል ዳኝነት፣ ከዚሁ ጋር ተያይዞም እስራትና ግድያም ሰለባ የሆኑት ገና በጧቱ ነበር። ያኔ ሕብረተሰቡ ውዥንብርና መጠራጠር ውስጥ ሊገባ የተገደደ መስሏል። ውሎ እያደረ ግን የወያኔ/ ኢሕአዲግ ማንነትና ምንነት በሂደት ቁልጭ ብሎ ታይቷል። የዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችንም ሆነ ራሱ በተግባር ለማዋል በሰነድነት ይዤዋለው የሚለውን ሕገ መንግሥት ተብዬ ሰነዱን ጎዝጉዞ ተቀምጦበታል። በአንዳንድ ወገኖቻችን እንደተጠቀሰው ሕገ መንግሥት ተብዬው የውሽት ሰነድ “ሕገ አራዊት” መሆኑ ማረጋገጫው ይህ ቡድን ለመብቴ እቆማለሁ ያሉትን ሰዎች እያደነ ማሰሩ፣ ማሰቃየቱ፣ ንብረት መዝረፉና ከዚያም በላይ ግድያ መፈጸሙ ነው።
የሩቁን ትተን በቅርቡ ያየነውና የሰማነው ለነፃ ሚዲያና ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት የቆሙ ጋዜጠኞች፣ ሕዝባዊ አስተዳደር እንዲሰፍን በሚታገሉ የፖለቲካ መሪዎች ላይ በኢ-አቃቤ ሕግ የተተወነው የአኬልዳማ ድራማና የሽብርተኝነት ክስ ካለፉት ዓመታት ተከታታይ የተውኔት ገቢር ከመሆኑ ሌላ እንግዳ ነገር አይደለም። ወያኔ/ኢሕአዴግ በአገር አማን ከመሬት ተነስቶ የሽብርተኝነት ሕግ አውጥቶ በይሰሙላ ፓርላማው ሲያስጸድቅ ራሱ የሽብሩ ተዋናይ ሆኖ እንደሚሠራው ሕዝቡ ከመነሻው በውል ተረድቷል። ይህን አፋኝ ሕግ ብዕራቸውን አንስተው የነቀፉትንና በአደባባይ የተቃወሙትን እንደተጠበቀው “ሽብርተኞች“ ብሎ ወህኒ አወረዳቸው። የመብት ጥያቄ ማቅረብና የወያኔን ሕገወጥነት መቃወም በሽብርተኝነት የሚያስፈርጅ ከኛ አገር ሌላ መኖሩ ያጠራጥራል። መምህራን ለችግራቸው ማስታገሻ የደመወዝ ጭማሪ እንዲደረግላቸው ቢጠይቁ ሰሚ በማጣታቸው በመጨረሻ በመጋቢት ወር 2004 ዓ.ም የሥራ ማቆም አድማ መትተው የመብት ጥያቄ በማቅረባቸው ከሽብርተኞች ጋር ያበሩ ተብለው በውርደት፣ በዘለፋ፣ በዘረፋ፣ በዘረኛው “ባለራዕዩ” ሰውዬ መሰደባቸውና እስካሁንም የሚደርስባቸው ዙሪያ ገብ ስቃይ አሸባሪው ማን እንደሆነ ለማወቅ አይከብድም።
በአሁኑ ወቅት የዙር ተራ የደረሰው በኢትዮጵያውያን ሙስሊም ወገኖቻችን ላይ ነው። ይህ ወንጃለኛ አምባገነን ቡድን በኃይማኖት ላይ መዝመት የጀመረው ቀደም ብሎ ነው።በአንዋር መስጊድና በአደባባይ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የፈፀመው በቂ መረጃ ነው። በተለይ በአንዋር መስጊድ ያካሄደው ግድያና በዚያ ሳቢያ የመጅሊሱን አመራር በካድሬዎቹ ለማስያዝ እንደስልት ተጠቅሞ በምዕምናኑ ተቀባይነት ያላቸውን ግለሰቦች ወንጅሎ ወህኒ ወረወራቸው።ለሦሥት ዓመታት በእስራት አንዲንገላቱ ካደረገ በኋላ በነፃ ተለቀቁ። ከዚህ ጎን ለጎን የመጅሊሱን አመራር
2
ያለዕምነቱ ተከታዮች ይሁንታ ምርኮኛ አድርጎ ሲጓዝ የሙስሊሙ ማሕበረሰብ ሁኔታዎችን በጥሞናና በትዕግሥት በመከታተል ይህን ሕገወጥ የወያኔ እርምጃ ለመለወጥ ሲታገሉ እንደቆዩ ከዕምነቱ ተከታዮች አንደበት ተሰምቷል። የኢትዮጵያ ሕዝብም የሚያውቀው ሐቅ ነው።
ይህ በእንዲህ እያለ የወያኔ/ኢሕአዴግ ባለሥልጣናት “አህባሽ” የሚል ባዕድ አምልኮና አስተምህሮት በሙስሊሞች ላይ እንዲጫን መሪውን ከሊባኖስ አምጥተው በማሰማራታቸው ሁኔታዎች በቅጽበት እንዲለዋወጡ አደረገ። ወያኔ በባህርዩ ከራሱ ቁጥጥርና አጀንዳ ውጪ የሙያ ማህበራትና ድርጅቶች ማለትም የመምህራን፣ የሠራተኛ፣ የሴቶች፣ የጋዜጠኞች፣ የተማሪዎች---ወዘተርፈ ማህበራት ነፃ ሆነው የሚንቀሳቀሱ ከሆነ ለህልውናዬ ያሰጉኛል የሚል መጥፎ አባዜ ስለተጠናወተው በኦርቶዶክስ ኃይማኖትም ሆነ በሙስሊሞች ለፈጸመውና እየፈጸመ ላለው ደባ መንስሔው ይሔው ነው። ያሁኑ የሙስሊም ወገኖቻችን ጥያቄ መሠረቱ የዕምነት ተቋማችን የሆነው መጅሊስ አማኞች በሚመርጧቸው ሰዎች ይመራ የሚለው መነሻ ሆኖ የአህባሽ አስተምህሮም በመንግሥት አጋፋሪነት በአማኞች ላይ ሊጫን ሕገ መንግሥታዊም ሆነ ዕምነታዊ (መለኮታዊ) ፈለግ አይደለም ነው የሚሉት።ይህ ደግም ጥርት ያለ ሐቅ ነው። ይህን ሐቅ ይዘውም አካሄዳቸው እጅግ ሰላማዊና ሕጋዊ መሆኑ ዓለምን ያስደመመ ታሪካዊ ገድል ሆኗል።
አንድ ዓመት ባስቆጠረው የሙስሊሞች የመብት ጥያቄ ማጠንጠኛ ማዕከል የሆነው የዕምነት ድርጅታችንን (መጅሊስ) እንዲመሩ የምንመርጥ እኛው ነን፣ የምርጫው ማዕከል የሚሆኑትም መስጂዶች ናቸው የሚል ሲሆን ወያኔ ደግሞ በራሱ የአስተዳደር አካላት በሆኑት ቀበሌዎች በካድሬዎች አማካይነት እንዲከናወን መፈለጉ ሂደቱን በማይገናኙ ትይዩ መስመሮች (Parallel lines) ላይ እንዲቆም ያደረገ አምባገነናዊ ተግባር እንደሆነ ያሳያል። ይህን በመንግሥት ስም የሚካሄድ ሕገወጥ አሠራር ማስተካከል እንዲቻል በማሰብ ሙስሊም ምዕመናን “መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ” አቋቁመው ከወያኔ/ኢሕአዴግ ጋር ተቀራርቦ በመወያየት እልባት እንዲገኝ አመቻችተዋል። በሰላማዊ መንገድ ተወያይቶ መፍትሔ በመፈለጉ ረገድ በመንግሥት ስም ከተቀመጠው ቡድን ሙስሊም ምዕመናንና ወኪሎቻቸው በልጠው ታይተዋል። “ድመት መንኩሳ አመሏን አትረሳ” እንዲሉ ሆኖበት ወያኔ ይህ የሠለጠነ አካሄድ አያምርብኝም ብሎ ባደገበትና በተካነበት አሠራር በአርሲ አሣሣ መስጊድ ግድያ ጀመረ፣ በአወልያ ት/ቤትም አማኞችን በጭካኔ ደበደበ ዘረፋም አካሄደ፤ ወሎም ዘልቆ በደጋንና አካባቢዋ ነዋሪዎች ላይ ጦሪነት አውጆ አማኞችን በአሰቃቂ ሁኔታ ጭዳ አደረጋቸው፣ ብዙዎችን አቆሰለ ፣ በሆስፒታል የሕክምና ዕርዳታ እንዳያገኙ አደረገ። በተመሳሳይ እርድ የሚጣሉ ፍለጋ ወልዲያ አካባቢ መስጊድ አቃጥሎ በትንኮሳው የተበሳጩ ሙስሊሞችን ለማጥመድ አቅዶ ከሸፈበት። ይባስ ብሎ አሸባሪዉ የወያኔ መንግሥት ሰላማዊ የሆኑትን የሙስሊም ማህበረሰብ መሪዎችን “አሸባሪዎች” ብሎ ቅራቅንቦ የሀሰት ማስረጃ ተብትቦ በመክሰስ ቃሊቲ ወህኒ ጥሏቸዋል። የኢትዮጵያ ሕዝብ እንደሚያውቀውና በዚህ ጽሑፍ በመጠኑም ቀንጨብ ተደርጎ እንደቀረበው የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ጥያቄና በአንድ ዓመት የተቃውሞ እንቅስቃሴም እንደታየው የሽብርተኝነት መንፈስ አለመኖሩን ነው።በአንፃሩ ግን ገሃድ የወጣውና አስከፊ ደረጃ ላይ የደረሰው የወያኔ መንግሥታዊ አሸባሪነት ነው።
የሙስሊም ወገኖቻችን ጥያቄ የመብት ጥያቄ ነው። የሠራተኛው፣ የመምህራን፣ የሴቶች፣ የገበሬዎች፣ የጋዜጠኞች፣ የተማሪዎች ---- የሌሎች የሕብረተሰብ ክፍል የመብት ጥያቄ አካል ነው። በነፃ የመደራጀት ጥያቄ ነው። የሙስሊም ወገኖቻችንን ጥያቄ ልዩ የሚያደርገው ነገር አለ ቢባል እየተገደሉ፣ እየታሠሩ፣ እየተገረፉና እየተዘረፉ በጽናትና በአንድነት ቆመው ባይበገሬነት ወደፊት መራመዳቸው ነው።ይህን የኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ትግል መደገፍ የሚገባን ያለምክንያት በስሜታዊነትና ግብታዊ በሆነ አካሄድ አይደለም።የወገኖቻችን ትግል የመደራጀት ጉዳይ፣
3
የዕምነት ነፃነት ጉዳይ፣ የርትዕና ፍትሕ፣ ሕግና ሕጋዊነት፣ ባጠቃላይ የሰብአዊ መብቶች መከበር ጥያቄ ላይ ተመስርቶ የሚካሄድ ነው።ይህን የኢትዮጵያ ሙስሊሞችን የመብት ጥያቄ በስደት የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አባላት አስተባባሪ ኮሚቴ ይደግፋል። መምህራንና ሌላውም የሕብረተሰብ ክፍል መደገፍ ይጠበቅባቸዋል።
ከሙስሊሙ ወገኖቻችን ጥያቄ በመነሳት በኦርቶዶክስ ዕምነት ተከታዮች የገዳማት ይዞታ የሆኑ መሬቶች በሕገወጥነት መነጠቅ ፣ አድባራት መዘረፋቸው፣ ሆን ተብሎ በወያኔ በተሎከስ ሰደድ እሳት በንብረትና በአገር ቅርስ ጥፋት መድረሱ፣ የቤተ ክርስቲያኑዋ ቀኖና መጣሱ፣ በክርስቲያኑም በሙስሊሙም ከመንግሥት የተቃጣው ጥቃት በጋራ ቆመው እንዲታገሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ተሟልተዋል። በመምህራንም ላይ እየደረሰ ያለው የማያባራ እንግልት፣ የሥራ ዋስትና ማጣት፣ በነፃ የመደራጀት መብት መገፈፍ፣ ---- ትግላቸውን ከሌሎች ተመሳሳይ ጭቆናና አፈና ከሚደርሰባቸው ክፍሎች ጋር ማቀናጀት የሚጠበቅባቸው የትግል ስልት ለመሆኑ ግልጽ ሆኗል። እንዲያውም ባላቸው የትግል ተመክሮ መምህራን የሙስሊም ዕምነት ተከታዮች ጥያቄዎችን ሆነ የኦርቶዶክስ ዕምነት ተከታዮች የመብት ጥያቄዎችን ማገዝ ይጠበቅባቸዋል። እንዲሁም በዘር ምንጫቸውና በቋንቋቸው ተነቅሰው ይኖሩበት ከነበረው የእርሻ መሬት ላይ መፈናቀል የደረሰባቸውን ገበሬዎች፣ ቤት ሠርተው ንብረት አፍርተው ይኖሩ የነበሩትን የከተማ ነዋሪዎች ቤትና ንብረታቸው በቡልዶዘር እየደረመሰ አውላላ ሜዳ ላይ ከነቤተሰቦቻቸው የጣላቸውን ዜጎች ሁሉ ማሰባሰብ የዚህን ግፈኛ ሥርዓት ቀበጥ ባለሥልጣናት አስወግዶ የሕዝብ የበላይነት፣ ተጠሪነትና ተጠያቂነት ያለው ሥርዓት እንዲመሰረት በጋራ መነሳትና ለመሰዋዕትነትም ዝግጁ መሆን ያሰፈልጋል።
በዚህ በኩል መምህራን የማስተባባር፣ የማደራጀትና የመምራት ብቃታቸውን መጠቀም ይኖርባቸዋል። በዚህ አኳያ እንኳንስ ሕዝባዊ አመጽ የመምህር የኔሰው ገብሬ በግሉ የከፈለው መስዋዕትነት መና አልቀረም። ይሄውና የሙት ዓመቱን የሚዘክሩለት ታይተዋል።የዚህ ጀግና መምህር መስዋዕትነት በሙያ ጓዶቹ በመምህራን እንዲታወስና እንዲወሳ ሁኔታዎች ባለመፍቀዳቸው እናዝነለን።ይህ እንዲሳካ የዘረኛው ሥርዓት ዕድሜ እንዲያጥር ሁላችንም የበኩላችንን እንድናበረክት ይጠበቃል። በስልት መደራጀት በስልት ማደራጀት ምን ጊዜም ትኩረት የሚያስፈልገው ጉዳይ ነው።
በመጨረሻም የኢትዮጵያ ሙስሊም ወገኖቻችን የጀመሩት ትግል ከዳር እንዲደርስ የመምህራን የትግል አጋርነት አስፈላጊ ነው። ሌላዉ የሕብረተሰብ ክፍልም ሊተባባር ያስፈልጋል። ስንት ጊዜ የጋራችን ጠላት የሆነው የወያኔ ቡድን በግል ያጠቃናል? በተለያዩ ወቅቶች አንድ ላይ ሆነን ባለመነሳታችን የከሸፉትን የትግል እንቅስቃሴዎችን እናስብ። ወያኔ/ኢሕአዴግ እንዳለፈው ሁሉ በሐሰት ውንጀላ የሕዝብን ጥያቄ አፍናለሁ የሚልበት ነፍጥ ቀለሃው ብቻቀርቷል። ባሩዱ ያለው በሕዝብ እጅ ስለሆነ የወያኔ አጉል መራወጥ በእሳት መጫወት ይሆናል፤ በጣዕር ላይ ያለ ሥርዓት ደግሞ በስተመጨረሻው እንዲህ በጥፋት የሚጠመድ መሆኑ በታሪክ የተመዘገበ ነው። የአምባገነኖች መገለጫም ነው። ሕዝብ አሸናፊ ነው፤ ቆርጠን እንታገል።
ከሙስሊም ወገኖቻችን ጋር እናብር!!
የሙስሊም መሪዎችን የሚሰይም አማኙ ነው!!
መጅሊስ የዕምነት ማራመጃ እንጂ የፖለቲካ ማስተናገጃ አይደለም!!
መንግስታዊ አሸባሪነት ይሰበር!!

No comments: