Sunday, July 3, 2016

ለመሆኑ ጦርነቱ የማን ነዉ?!

July 3,2016
ከሠራዊቱ ድምፅ ራዲዮ
የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያዉቀዉ ላለፉት 25 አመታት ኢትዮጵያን በነፍጥ እየገዛ ያለዉ የትግሬ ነፃ አዉጭ ነኝ ብሎ ራሱን የሚጠራዉ የሚሊሽያ ዘረኛ ቡድን መሆኑን ነዉ። የሚገርመዉ ግን ለአገዛዙ እዉቅና የሠጡት ከኢትዮጵያ ሕዝብ ይልቅ የአሜሪካ የእንግሊዝ የቻይናና አንዳንድ የአዉሮፖ አገሮች ናቸዉ። ኢትዮጵያ ዉስጥ ስለተዘረጋዉ ዲሞክራሲ እኩልነትና ሰላም የሚነግሩንም እነዚሁ ፈረንጆች ናቸዉ።
እነዚህ ባእዳን አገሮች አረካ አርባጉጉና አሠቦት ላይ የፈሰሰዉ ደም ፧በቅርቡ በኦሮሞ ማህበረሠብ ወገኖቻችን እንቢተኝነት ምክንያት በአገዛዙ ቅልብ ነፍሰገዳይ ወታደሮች የወደቀዉ የ400 ንፁሀን ነፍስ ፧በወልቃይትና በአጠቃላይ በአማራዉ ማህበረሠብ ላይ የሚካሄደዉ መፈናቀልና የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ ፧በአንዳንድ ከተሞች የሚደረጉ የኖርያ ቤቾችን የማፍረስ ዘመቻ ፤በጋምቤላና በኦጋዴን በተከታታይ የተፈፀመዉ የመሬት ዘረፋና የጅምላ ፍጅት ፧በጋዜጠኞችና በፖለቲካ ድርጅቶች ላይ እየተፈፀመ ያለዉ ግፈ ኦርዮን ፧በምንም ሁኔታ ሊሰማቸዉ አይችልም።ዛሬ አንዳንድ የአዉሮፓና የአሜሪካ ዲፕሎማቶችና ጋዜጠኞች ኢትዮጵያን የሚመለከቱት አራት ኪሎ ቤተመንግሥት ሲደርሱ የህወሃት ሃኪም በሚያዝላቸዉ መነፅር ነዉ ማለት ይቻላል።
አሁንም ድረስ  ሕዝቡ በጠመንጃ አፈሙዝ አስገዳጅነት እተገዛ መሆኑን አያምኑም፧ሊያምኑም አይፈልጉም። በተለያዩ አካባቢዎች ሰዎች በአገዛዙ ቅልብ ወታደሮች በጥይት በአደባባይ ተደብድበዉ የመሞታቸዉ ወሬ ሲደርሳቸዉ አገዛዙን በመሸሽ በብዙ መቶ ሽህ የሚቆጠሩ ዜጎች ድንበር ጥሰዉ ባህር አቋርጠዉ ሲሰደዱ የባህርና የዱር አዉሬ ሲበላቸዉ በሽብርተኛ ነፍሠገዳዮች አንገታቸዉ በካራ ሲቀላ፧ከነህይወታቸዉ በእሳት ሲቃጠሉና ከፎቅ ተወርዉረዉ ሲጣሉ ፧አሲድ ፊታቸዉ ላይ ሲከለስና ፧በሥርአተ አልበኛ ወታደሮች ሲደፈሩ እነዚህ አላጋጮች የዲሞክራሲ ሂደት ነዉ ይሉናል።
ስለ ኢትዮጵያ ታላቅነትና ገናናነት ፧የስልጣኔ ቅርስና የጥንታዊ ሰዉ መፍለቂያ አድርገዉ የሚያወሩላት አገር ዛሬ ያለችበት ደረጃ ለወሬም የማይመች ሳይሆንባቸዉ አይቀርም። ወደዘመነ መሳፍንት የመመለሳችን ሁኔታ ደግሞ ጨርሶ አይስተባበልም። አቶ ስብሃት ነጋን አቶ አባይ ፀሃዬን አቶ በረከት ስምኦንን አቶ አላሙዲንንና እነእንቶኔን እንደዘመነ መሣፍንት ገዥዎች ለመቁጠር በግድ ራስ ደጃዝማች ፍታዉራሪ ማለት አስፈላጊ አይደለም። የዘመነ መሳፍንት ይዘት ግን አለ! አየሩም መንፈሱም አለ ዘመነ ወያኔ!!!
አምላክ ኢትዮጵያን የሚታረቃት ለሱም ለሕዝቡም የሚስማማ መሪ ሲሰጣት ሊሆን ይችላል የሚሉ ብዙዎች ናቸዉ። መቼ እንዴት ይነሳል የሚለዉ ጥያቄ ግን መልስ አልተገኘለትም።
እንደሚታወቀዉ የህወሀት ዘረኞች እፍረትና ይሉኝታ የሚባል ነገር አልፈጠረባቸዉም። ጎስቋላ ሕዝብ ይበልጥ እያጎሳቆሉ የተምታታ ፖለቲካ ይበልጥ እያመሱ ፧ደሀ ኢኮኖሚ ይበልጥ እየገደሉ መንግሥት የሚባል ካባ ደርበዉ በመሪነት ሥልጣን ራሳቸዉን ኮፍሰዋል።
ድህነት የኩራት ምንጭ ባይሆንም ቢያንስ ቢያንስ በብሄራዊ ኩራት ሲሸፈን የሞራል ጥንካሬና የባለ አገርነት መንፈስ ያላብሳል። ትልቁ ኪሳራ የአላማ ድህነት፧የእዉቀት ድህነት፣ የአመራር ድህነት ነዉ። ላለፉት 25የህወሀት አገዛዝ በዚህ ረገድ ያለን ሃብት በሽበሽ ነዉ።
የኢትዮጵያን የሦስት ሽህ ዘመን ባለታሪክነት የማያዉቁና ማወቅም የማይፈልጉ ሰዎች  ታሪክ ሲያስተምሩን፧ ፖለቲካ የማያዉቁ ሰዎች እንደእዉር እንምራችሁ ሲሉን የአገርን ዳር ድንበር ምንነት የማያዉቁ ሰዎች በአገር አመራር ላይ ሲቀመጡ፧የኢኮኖሚ ሀሁ የማያዉቁ ሰዎች ኢኮኖሚ አደላዳዮች ሲሆኑ፧ሕግ ያልዳኛቸዉ ሰዎችና ከቶዉንም በተከሣሽ ሳጥን ዉስጥ መሆን የሚገባቸዉ ሰዎች የፍትህ አጋፋሪዎች የሰላም ዳኞች ሲሆኑ፥የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን እንኳ ያላጠናቀቀ የፕሮፊሰርነትና የሙሉ ጄኔራልነት ማዕረግ ሸልሞ የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኤታ ማጆር ሹም ቢሮ ሲቀመጥ ማየት፧ከዚህ የበለጠ አመራር የማጣት ማስረጃ አይገኝም።
ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያ ኢትዮጵያዊ አመራር በማጣትዋና በመጥፎ ታሪክ አጋጣሚ የሥልጣን ኮርቻ ላይ የተቀመጡት ፀረ ኢትዮጵያ የህወሀት ቡድኖች ለሕዝቡ ታማኝ ባለመሆናቸዉ ህብረተሰቡ ቀዉስ በቀዉስ ሆኗል።
በመከላከያ ሠራዊቱም ውስጥ ከላይ ጀምሮ እስከ ታች ድረስ ያሉት አዛዦችና ካድሬዎች የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪና የዘረኛዉ የህወሀት አባላት ብቻ ናቸዉ። ቀደም ሲል የነበረዉን የረጅም አመታት የዳበረ የወታደራዊ ሳይንስ እዉቀትና ልምድ ያለዉን ከኢትዮጵያና ከኢትዮጵያዊነት ዉጭ ሌላ አላማ የሌለዉን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በትኖ በክልል የተሸነሸነና በጎጥ የተማከለ ሠራዊት በምትኩ አቋቁሟል። ይህ በጎጥ የተደራጀ ሠራዊት ብቃት በሌላቸዉ ከአንድ ጎሳ የፈለሱ ከጫካዉ የጎሬላ ዉጊያ በስተቀር ምንም የወታደራዊ አመራር ሥልጠና የሌላቸዉና የተሸከሙትን ማዕረግ የማይመጥኑ ማፈሪያዎች ናቸዉ። ዉትድርና ጥበብ ነዉ። በየደረጃዉ ያለዉን ወታደራዊ ማዕረግ ለመልበስ በልዩ ልዩ ሥልጠና ዉስጥ ማለፍን ይጠይቃል። በህወሀት ሠራዊት ዉስጥ እንደሚታየዉ ግን ማእረግ የሚታደለዉ አንደገና ዳቦ በስጦታ ነዉ።
በስራቸዉ ያለዉ ተራዉ ወታደር እንደጭቁኑ ሕዝብ ሁሉ ከፍተኛ ጭቆና አለበት። በህወሀት የስለላ መረብ ተተብትቧል። ከትግሬ ዘር በተለይም ደግሞ ከህወሀት አባላት ዉጭ በመሆኑ ብቻ በጥርጣሬ ይታያል አይታመንም።በግምገማ ይዋከባል። በአስቸጋሪ ዉጊያ ወቅት ግንባር መስመር ተሰልፎ የጥይት ማብረጃ ይሆናል። የዉጭ አገር ስልጠና እድልናና ገንዘብ የሚያስገኝ ግዳጅ ሲሆን ደግሞ ከወርቆቹ ጎሳ ተመርጦ ይላካል። አማራ ከሆነ ግንቦት 7 ኦሮሞ ከሆነ ኦነግ እየተባለ ይፈረጃል።በየጥቃቅኑ ምክንያት ዘብጥያ ይጣላል። የሌላዉ ጎሳ አባላት ሰብሰብ ብለዉ ቆመዉ ማዉራት አይፈቀድላቸዉም ለአድማ ነዉ አስብሎ ግምገማ እንደሚያስቀርብ ሥርአቱን ከድተዉ የወጡት የሠራዊቱ አባሎች ገሃድ ያወጡት እዉነታ ነዉ።
ይህ ሠራዊት በማንኛዉም ወቅት መሳርያዉን በአለቆቹ ላይ ሊያዞር እንደሚችል መናገር ነብይ አያሰኝም።
ዛሬም አገዛዙ ጦርነት እየፈበረከ ነዉ። አሸናፊና ተሸናፊ ለሌለዉ ኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ከ100ሽህ በላይ ዜጎች አልቀዋል። የጦርነቱ ዉጤት የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከማዉደሙም ሌላ ኪሳራና የዉርደት ጠባሳ ጥሎ አልፏል።በዚያ ፍልሚያ ጥቂት የማይባሉ የቀድሞ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት ጄኔራሎች ሳይቀሩ በዉዴታ ግዴታ ተሰልፈዉ መሳተፋቸዉ ይታወሳል።በጦርነቱ ፍፃሜ ላይ ግን የወያኔ መሪዎች የመሬትና የገንዘብ ሽልማት እያገኙ ወደሰላማዊ ንሮአቸዉ ሲመለሱ የቀድሞ የኢትዮጵያ ወታደሮች ብዙዎቹ መስዋእት ሆነዉ የተረፉት ባዶ እጃቸዉን ተባረዋል። ከጦርነቱ በኋላ በወቅቱ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት ስዮም መስፍን ባድመ ለኛ ሆናለች ብለዉ በአደባባይ ሰልፍ በጠሩ ማግሥት ግዙፉ እዉሸታቸዉን በአለም አቀፉ መድረክ በተገላቢጦሽ ሰማነዉ።
ሰሞኑን ከ16 አመት በኋላ ሌላ የጦርነት ከበሮ እየደለቁ ነዉ። ሌላ እልቂት። ሌላ የጦር መሣርያ የቅብብሎሽ ንግድ ፧ሌላ ዉሸት። ትናንት ከማይረባ ሽሮ ይሻላል ወደሽራሮ ያለዉ የበይ ተመልካች ወገኔ ዛሬ በነሱ መልማይ ካድሬዎች የተጣለ የሆቴል ትርፍራፊ ከምትበላና በረሀብ እዚህ ከምትሞት ወትድርና ግባና በልተህ ሙት እያሉት ነዉ።
ይህ ከ16 አመት በኋላ ያገረሸ የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ምክንያቱ ምን ይሆን?! ጦርነቱ የማንና የማን ጦርነት ነዉ?! በጦርነቱ ተጠቃሚዉ አካል ማነዉ?! የሚሉትና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ዛሬ ይበልጥ አነጋጋሪ ጉዳዮች ናቸዉ። ለመሆኑ ካለፈዉ የሁለቱ አገራት ጦርነት ሠፊዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ምን ተማረ?! የእዉነት ጦርነት ቢጀመር የኢትዮጵያ ሕዝብ ምላሽ ምን ይሆን?!

No comments: