Thursday, March 3, 2016

ዛሬም እንደ አድዋው ጊዜ አብረን እንነሳ!!!

March 3,2016
በያዝነው ሳምንት አባቶቻችን የነበረውን የትጥቅ የበላይነት መከታ በማድረግ ሀገራችን ኢትዮጵያን ለመውረርና ህዝቧን በውርደትና በባርነት ለመግዛት የዘመተብንን የጣሊያን ጦር አለምን ማስደነቅ ብቻ ሳይሆን የታሪክን አቅጣጫ የቀየርውን ያድዋን ጦርነት ድል የመቱበት 120ኛ ዐመት ይከበራል። አድዋ ሲወሳ ፈጽሞ ልንረሳው የማንችለው ነገር በእግር በፈረስ ከሀገራችን ልዩ ልዩ ቦታዎች የብሔረሰብም ሆነ ሌላ ልዩነት ሳያግዳቸው እንደ አንድ ሰው የተነሱ አባቶቻችንን የህብረት ተጋድሏቸውን ነው።
የድላቸው ዋንኛ ምክንያትም ህብረትና አንድነታቸው እንደነበር ልንዘነጋው አይገባም። እድዋ የመላው ጥቁር ሕዝብ አንጸባራቂና አለም ያላሰበው ድል እንዲሆን ያደረገው አባቶቻችን ወርደትንና ባርነትን ከሞት በላይ ስለቆጠሩት ብቻ ሳይሆን በህብረትና ባንድነት መነሳታቸው እንደነበር ፈጽሞ ልንዘነጋው አይገባም። ተዋርዶና ተንበርክኮ መገዛትን ምንም ያህል ቢጠሉ እንደ አንድ ሰው ሆነው ባይነሱ ይህን እንጸባራቂ ድል ይቀዳጁ ነበር ብሎ ማሰብ ይከብዳል።
ዛሬ በተደጋጋሚ ሀገራችንን የወረሩ ጠላቶች ሁሉ ሊጠቀሙበት ሞክረው ያልቻሉትን የከፋፍለህ ግዛ ሴራ በመጠቀም እንደባዕድ ሊገዛን እየሞከረ ያለውና ሀገራችንን ካላንዳች ይሉኝታ በመዝረፍና ልጆቹዋን ካለርሕራሔ በመጨፍጨፍ ላይ የሚገኘውን የሁላችንም ጠላት የሆነውን ወያኔን ከላያችን ላይ አሽቀንጥረን የምንጥለውና ነጻነታችንን የምንቀዳጀው እንደ አድዋው ጊዜ እብረን የተነሳን እንደሆን ብቻ ነው። ወያኔ 25 ዓምት የፈነጨብንና ሀገራችንን ከባዕድ ባልተናነሰ ዛራፊነትና ጨፍጫፊነት ሊገዛ የቻለው የውበታችን ምልክት የሆነውን ብሔረሰባዊ ልዩነታችንን እየተጠቀመ ይሁን እንጂ ብዙዎቻችንም ተመሳሳይ ዓላማ ይዘን በህብረት ለመታገል ባለመወሰናችን ካባቶቻችን ያድዋ ትሪክ ባለመማራችን መሆኑን መካድ አይቻልም።
ብዙ ወገኖቻችን ሲሉ እንደሚሰማው የወያኔው ጉጅሌ ሀይል የራሱ ድርጅታዊ ጥንካሬ የፈጠረለት ሀይል ሳይሆን ከኛ መከፋፈል ያገኘው ነው። ዛሬ በኦሮሚያና ሌሎች አካባቢዎች የህዝቡን መሬት ካለይሉኝታ የሚዘርፈው ወያኔ፣ ሕጻን ሽማግሌ ሳይለይ በእብሪትና በድፍረት መደዳውን ኦሮሞ ወገኖቻችንን እየጨፈጭፈ ያለው ህዝቡ አይተባበርም በሚል ነው። የሀገራችንን ድንበር ቆርሶ ለመስጠት ከጀርባችን ሆኖ የሚደራደረው የተባበረና አንድ ድምጽ ያለው ህዝብ አይጠይቀኝም ከሚል በመነጨ ጥጋብ ነው። የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ ማንነቴን ከናንተ ይበልጥ የማውቀው ራሴ ነኝ ስላላቸው እየነቀሱ የሚያፍኑትና ይስንቱን ቤት ለዘላለሙ እንዲዘጋ ያደረጉት የሚተባበር ሕዝብ የለም በሚል ተስፋ ነው።
ወያኔ የብሔረሰብ ልዩነታችንን ብቻ ሳይሆን በትግል ዘዴ አመራረጣችንና በተለያዩ በክርክር ሊቋጩ የሚችሉ የፖለቲካ ልዩነታችን መሀል በመግባት ወደ አንድነት እንዳንመጣ ከለመታከት ይሰራል። በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ይህ እንዲሆን የፈቀድንለት ራሳችን በመሆናችን ላለመተባበራችን ሁላችንም የተወሰነ ወቀሳ መውሰድ ይኖርብናል።
አሁን ጊዜ የለንም። ወገኖቻችን በገፍ አየተጨፈጨፉ መፈጠራቸውን ሊጠሉ በቻሉበት ደረጃ ደርሰዋል። በየቦታው አመጾች በመቀጣጠል ላይ ናቸው። ወያኔ በተወሰነ ደረጃ የህዝቡ ቁጣ ስላስደነገጠው የሚያውቀውን የመጨፍጨፍና የመቀጥቀጥ ፖለቲካ በስፋት ተያይዞታል።አርበኞች ገንቦት 7 በሀገርም ከሐገር ውጭም ካሉ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሀይሎች ጋር ያድዋውን አይነት ህብረት እንዲፈጠር ይፈልጋል። ያለን መስፈሪያ ሀገራችንን ሉዓላዊ ሆና መቀጠሉዋና ወደፊት የምንመሰርተው መንግስት ዲሞክራሲያዊ መሆኑን ማረጋገጥ ብቻ ነው። እኛ በሰላምም በሐይል አማራጭም ከወያኔ ጋር የሚተናነቁትን ማንኛውንም የፖለቲካ ሀይሎች እንደግፋለን። ሕዝባችን ወይ ተባበሩ ወይ ተሰባበሩ እያለ ሲጮህ ብዙ ዘመን ሆነው። እናም እንተባበር።
አባቶቻችን የዛሬ መቶ ሀያ አመት የተጠቀሙበት ስልት ለኛ ለልጅ ልጆቻቸው የሚሳነን ሊሆን አይገባም። ሁል ጊዜ እንደሚባለው እንድነት ሀይል ነው። ወያኔ አንድ ላይ በቆምን ማግስት በኢትዮጵያ መሬት ላይ አይኖርም። አድዋ ላይ ጠላትን ተባብረው እንዳንበረከኩት አባቶቻችን፣ ራሳቸውንና እኛን ልጆቻቸውን ብቻ ሳይሆን መላውን ጥቁር ህዝብ እንዳኮሩትና የአለም ታሪክን አቅጣጫ እንደቀየሩት አባቶቻቸን ተባብረን እንድንነሳ አርበኞች ግንቦት 7 የትግል ጥሪውን ያቀርባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

No comments: