Wednesday, April 29, 2015

ኢህአዴግ ሰማያዊን ለማውገዝ በየ አካባቢው የአደባባይ ስብሰባ መጥራቱ ተሰማ

April 29,2015
ኢህአዴግ ሰማያዊ ፓርቲን ለማውገዝ ለነገ ሀሙስ አዲስ አበባ ውስጥ በየ ወረዳው በሚገኙ ሜዳዎች የአደባባይ ስብሰባዎችን መጥራቱን ምንጮች ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ህዝባዊ ንቅናቄ›› የተባሉት የአደባባይ ስብሰባዎች ባለፈው ሰልፍ ላይ ‹‹ሁከትና ብጥብጥ›› ፈጥረዋል በሚል በገዥው ፓርቲ እየተከሰሱ ያሉትን በተለይም ሰማያዊ ፓርቲን ለማውገዝ የተጠሩ ናቸው ተብሏል፡፡ በህዝባዊ ስብሰባዎቹ ከካድሬዎች ውጭ ተቃውሞ የሚያሰሙ ኢትዮጵያውያን እንዳይገኙ የኢህአዴግ አባላት ብቻ እንዲገኙ በደብዳቤ እንደተጠሩ ታውቋል፡፡
መንግስት አይ ኤስ አይ ኤስ በኢትዮጵያውያን ላይ የፈፀመውን አሰቃቂ እርምጃ ለማውገዝ በጠራው ሰልፍ ላይ ለጉዳዩ ትኩረት አልሰጠም በሚል ተቃውሞ ከገጠመው በኋላ ሰማያዊ ፓርቲ ከተቃውሞው በስተጀርባ እንዳለበት ከመክሰሱም ባሻገር በተለያዩ አካባቢዎች በጠራቸው ሰልፎች ሰማያዊን ሲያወግዝ ተስተውሏል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ በበኩሉ ኢህአዴግና የመግንስት ተቋማት ስሙን ከማጥፋት ካልተቆጠቡ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስደውና ከዚህም ባሻገር ሌሎች ተከታታይ እርምጃዎችን እንደሚወስድ በመግለጽ ህዝብ ከጎኑ እንዲቆም ጥሪ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

No comments: